24/08/2026
የጣና ባዮስፌር ሪዘርቭ አሁናዊ ሁኔታ /Periodic Review / ማስጀመሪያ ወርክሾፕ ተካሄደ
የጣና ባዮስፌር ሪዘርቭ አሁናዊ ሁኔታ /Periodic Review / ማስጀመሪያ ወርክሾፕ ነሀሴ 18 ቀን 2018 ዓ.ም በባህርዳር ከተማ ተካሄደ፡፡
ኮማንደር መንገሻ አውራሪስ የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ተወካይ ባስተላለፉት የእንኳን ደህና መጣችሁ መልዕክት በሀገር አቀፍና በዓለም አቀፍ ደረጃ የላቀ ስነምህዳራዊ ፣ ከባቢያዊ እና ማህበረ-ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያለውን የጣና ሀይቅና አካባቢውን በሚመለከት አጀንዳ ላይ ለመምከር በመምጣታችሁ ምስጋናዬን አቀርባለሁ ካሉ በኋላ በምርምር የተደገፈ አሳማኝ ሰነድ ማዘጋጀት እንደሚገባ አስታውሰዋል፡፡
ዶ/ር አብዮት ብርሃኑ የኢትዮጵያ ብዝሀ ህይወት ኢንስቲትዩት ም/ዋና ዳይሬክተር ባደረጉት የመክፈቻ ንግግር የጣና ባዮስፌር ሪዘርቭ አሁናዊ ሁኔታ /Periodic Review / ማስጀመሪያ ሥነ-ሥርዓት እና የምክክሩን አስፈላጊነትን አስታውሰው ጣናን መሰል ጥብቅ ስፍራዎች የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ወሳኝ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ አያይዘውም የኢትዮጵያ ብዝሀ ህይወት ኢንስቲትዩት በቀጣይ በተባበሩት መንግስታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ድርጅት /UNESCO/ ሊያስመዘግባቸው የተዘጋጁትን ጥብቅ ስፍራዎች በዝርዝር አቅርበዋል፡፡
በተጨማሪም ጥብቅ ስፍራዎች የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ሊያረጋግጡ እንደሚገባ ጠቁመው ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ መድረክ ያላትን ታዋቂነት እንድታጎሉ አደራ እላለሁ ብለዋል፡፡
ፕሮፌሰር እንየው አድጎ የባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ የምርምርና ማህበረሰብ ተሳትፎ ምክትል ፕሬዝዳንት ባስተላለፉት መልዕክት የጣናን ጤንነት መጠበቅ ግዴታችን ነው ካሉ በኋላ በጣና ሀይቅ ዙሪያ ባለድርሻ አካላት ታሪካዊ ኃላፊነታችሁን እንድትወጡ አደራ እላለሁ ብለዋል፡፡
አቶ አበራ ስዩም በኢትዮጵያ ብዝሀ ህይወት ኢንስቲትዩት የደንና ግጦሽ መሬት እጽዋት ምርምር መሪ ሥራ አስፈጻሚ Ethiopian Biosphere Reserves: Concept & Practices እንዲሁም Periodic Review of Tana Biosphere Reserve (TOR) የተሰኙ ሰነዶችን ያቀረቡ ሲሆን ፕሮፌሰር አያሌው ወንዴ Tana Biosphere Reserve: Challenges and Opportunities የተሰኘ ሰነድ አቅርበዋል፡፡
በወርክሾፑ ማጠናቀቂያ ላይ ኮማንደር መንገሻ አውራሪስ የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ተወካይ እና ዶ/ር አብዮት ብርሃኑ የኢትዮጵያ ብዝሀ ህይወት ኢንስቲትዩት ም/ዋና ዳይሬክተር ለቴክኒክ ቡድን አባላት የስራ መመሪያ ሰጥተው መድረኩ ተጠናቋል፡፡