19/08/2026
የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን ከኮሜርሺያልኖሚኒስ ኃላ.የተ.የግ..ማህ ጋር የመግባቢያ ስምምነት ተፈራረመ
-----------------
(ኢምባኮ ነሀሴ 12/2018 ዓ.ም) የኢትዮጵያ የምድር ባቡር ኮርፖሬሽን እና ኮሜርሺያል ኖሚኒስ ኃላ.የተ.የግ..ማህ በጋር መስራት በሚቻልባቸው ጉዳዮች ላይ ነሀሴ 12 ቀን 2018 ዓ.ም በራዲሰን ብሉ ሆቴል የመግባቢያ ስምምነት ተፈራረሙ፡፡
የመግባቢያ ስምምነቱ የተለያዩ የኢንጂነሪንግ፣ የመሰረተ ልማት እና የቢዝነስ አገልግሎቶችን በጋራና በትብብር ለመስራት የሚያስችል ሲሆን ኮሜርሺያል ኖሚኒስ ሲያቀርባቸው የነበሩ አገልግሎቶችን ለማጠናከር እና በአዳዲስ የቢዝነስ መስኮች በጋራ ለመስራት መሆኑን የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኢንጂነር ህሊና በላቸው ገልፀዋል፡፡
የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽንና የኮሜርሺያል ኖሚኒስ ለረጅም ጊዜ አብረው ሲሰሩ የቆዩ ቢሆንም ኮርፖሬሽኑ በመንገድ፣ በህንፃ ግንባታና ማማከር ስራዎች እየሰራ በመሆኑና ኮሜርሺያል ኖሚኒስ በሪል ስቴት ዘርፍ ለመሰማራት የያዘውን ዕቅድ ተከትሎ በኮንስትራክሽን እና የማማከር መስኮች በጋራ ለመስራት ዕድል የሚፈጥር መሆኑን የገለጹት የኮሜርሺያል ኖሚኒስ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኮማንደር ጥላሁን ጸጋዬ የመግባቢያ ስምምነቱ በሁለቱ ተቋማት መካከል ያለውን ኃብት እና እውቀት በጋራ በመጠቀም ለሀገር ከፍተኛ አስተዋጽዖ የሚያበርክቱ ተግባራትን ለማከናወን የሚያስችል ነው ብለዋል፡፡
በመግባቢያ ስምምነቱ መሰረት የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን ከዲዛይን እስከ ግንባታ ያሉ የኢንጂነሪንግ እና የኮንስትራክሽን ሥራዎችን፣ የአዋጭነት ጥናቶች፣ የአቅም ግንባታ እና የቴክኒክ ስልጠናዎችን፣ የማማከር ሥራዎችን እና ሌሎች ተግባራትን የሚያከናውን ሲሆን በሌላ በኩል ኮሜርሺያል ኖሚኒስ የንብረት እና ኃብት አስተዳደር፣ የሰው ሀይል አቅርቦት፣ ስልጠና፣ የካሳ ክፍያዎችን እና ሌሎች አገልግሎቶችን ለኮርፖሬሽኑ ለማቅረብ የሚያስችለው ነው፡፡