08/02/2026
ኤርትራ ሰራዊቷን በአስቸኳይ ከግዛቴ ታስወጣ ስትል ኢትዮጵያ ጠየቀች
---------
የኤርትራ ሰራዊት የኢትዮጵያን ሉአላዊ ግዛት በመጣስ በሰሜን ምስራቅ አቅጣጫ ግልጽ ወረራ ፈጽሞብኛል ሲል የኢፌዲሪ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ገለጸ።
በውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ጌዲዮን ጢሞቲዮስ (ዶ/ር) የተጻፈውና ለኤርትራው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኦስማን ሳላህ በተላከው በዚህ ደብዳቤ፣ የኤርትራ ሰራዊት የኢትዮጵያን ሉአላዊ ግዛት በመጣስ በሰሜን ምስራቅ አቅጣጫ ግልጽ ወረራ መፈጸሙንና እዛ ከሚገኙ በደብዳቤው ላይ በስም ካልተጠቀሱ ታጣቂዎች ጋር ወታደራዊ እንቅስቃሴ እያደረገ እንደሚገኝ በደብዳቤው ጠቅሷል።
"የሁለቱን ሀገራት የጋራ ብሔራዊ ጥቅምን ባስከበረ መልኩ በላቀ የመከባበር ስሜት ለመመካከር ዝግጁ ነን" ያለው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ደብዳቤ፣ አሁን በኤርትራ በኩል የተከፈተው ትንኮሳ ግን በምንም መመዘኛ ቅቡልነት የሌለው መሆኑን በማብራራት "ኤርትራ ሰራዊቷን በአስቸኳይ እንድታስወጣና ለሰላማዊ ድርድር ዝግጁ እንድትሆን በይፋ እንጠይቃለን" ሲል በአጽንኦት ይጠይቃል።
ለግማሽ ምዕተ አመት ያህል ሁለቱም አገራት በማያባራ ግጭት ላይ እንደኖሩ የሚያብራራው ደብዳቤው ይህ አይነቱ የግጭት አዙሪት በውይይትና በዲፕሎማሲያዊ ጥረት እልባት ሊያገኝ የሚችልበት እድል እንዳለ በመግለጽ በኤርትራ በኩል በጎ ምላሽ ከተገኘ የኢትዮጵያ መንግስት ልዩነቶችን በሰላማዊ ድርድር ለመፍታት ዝግጁ መሆኑን ያብራራል።
በኤርትራ መንግስት በኩል እስካሁን ለዚህ ደብዳቤ የተሰጠ ይፋዊ ምላሽ የለም።