06/10/2020
ለተከታታይ 4 ቀናት የሚሰጠው የፖሊዮ መከላከያ ክትባት ነገ ይጀምራል!
ለተከታታይ 4 ቀናት የሚሰጠውን የልጅነት ልምሻ (የፖሊዮ) መከላከያ ክትባትን አስመልክቶ በቦሌ ክፍለ ከተማ የወረዳ 13 ጤና ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ጌቱ ቂጣታ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡
የልጅነት ልምሻ መከላከያ ክትባት በሽታው በክልላችን በተከሰተባቸው አካባቢዎች ዕድሜያቸዉ ከ5 ዓመት በታች ለሆናቸዉ ህጻናት ከመስከረም 27-30/2013 ዓ.ም ለተከታታይ 4 ቀናት እንደሚሰጥ ተናግረዋል፡፡
በወረዳችን ውስጥ በሚገኙ 6ቱም ቀጠናዎች ተደራሽ ለማድረግ ግብዓቶችን የማሟላት ተግባራትን ጨምሮ አስፈላጊው ቅድመ ዝግጅት መጠናቀቁንም አስታውቀዋል፡፡
ዕድሜያቸው ከ5 አመት በታች ለሆኑ ህፃናት ቤት ለቤት በጤና ባለሙያዎች በሚሰጠው የክትባት ዘመቻ የማህፀን ጫፍ ካንሰርን ጨምሮ 10 ክትባቶችን መውሰዳቸውን የመረጋገጥ፣ ከ2.1 ሚለዮን በላይ የህፃናት የምግብ እጥረት ልየታን ለመቃኘት የሚያስችሉ ቡድኖችን የማንቀሳቀስ ስራዎች እንደሚከናወኑ ተናግረዋል፡፡
በዚህ የክትባት ዘመቻ የኮሮና ቫይረስ (ኮቪድ-19) ወረርሽኝን ለመከላከል የሚያስችሉ የጥንቃቄ እርምጃዎችን በተገቢው በመተግበር ህጻናትን ማስከተብ ልዩ ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡
በኢትዮጵያ ጎረቤት አገራት የፖሊዮ ቫይረስ መከሰቱን ተከትሎ ከመስከረም 27 ጀምሮ ለአራት ቀናት የሚቆይ አገር አቀፍ ክትባት እንደሚሰጥ የኢትዮጵያ ሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ማስታወቁ ይታወሳል፡፡