12/05/2026
ሠላም ለኢትዮጵያ ጥምረት፡ “ጽንፈኝነትና የኃይል እርምጃ ለዘላቂ ሰላም እንቅፋት ናቸው” አለ
ዛጉዌ ሚዲያ -Zagwie Media ግንቦት2018
================
በሀገሪቱ እየተስፋፉ ያሉ ጽንፈኛ አመለካከቶችና በመሣሪያ ኃይል የሚካሄዱ እንቅስቃሴዎች ለኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላምና አንድነት ከባድ እንቅፋት እየሆኑ መጥተዋል ሲል ገለጸ።
ጥምረቱ ባወጣው መግለጫ፣ ኢትዮጵያ የታሪክ፣ የባህልና የብዝኃነት ሀገር እንደመሆኗ መጠን ይህንን እሴት ጠብቆ ለማቆየት ሰላም መሠረታዊ ፍላጎት መሆኑን ጠቅሶ፣ በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች የሚታዩ ግጭቶች የዜጎችን ሕይወት ከመቅጠፍ ባለፈ የሀገርን ህልውና አደጋ ላይ እየጣሉ መሆናቸውን አሳስቧል።
በተለይም በአዊ ብሔረሰብ አስተዳደር በአዮ ጓጉሳ ወረዳ አዘና ከተማ በሰላማዊ ዜጎች ላይ የተፈጸመውን ጥቃት በጥብቅ እንደሚያወግዝ ገልጾ፣ በድርጊቱ ውስጥ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ተሳትፎ ያደረጉ አካላት ለሕግ እንዲቀርቡ ጠይቋል።
ጥምረቱ በመግለጫው የኃይል አማራጭ ዘላቂ መፍትሔ ሊሆን እንደማይችል በማስገንዘብ፣ ችግሮች በውይይትና በመግባባት መፍታት እንዳለባቸው ገልጿል። “ጥይት የማይመልሳቸውን ጥያቄዎች በውይይት መፍታት የሰለጠነ ማኅበረሰብ መገለጫ ነው” ሲልም አስታውቋል።
በተጨማሪም በብሔርና በሃይማኖት ስም የሚነሱ ጽንፈኛ አመለካከቶች የጋራ አገራዊ እሴቶችን እንደሚያፈርሱ ጠቅሶ፣ ሁሉም ወገኖች ከእንዲህ ዓይነት አጥፊ አስተሳሰቦች እንዲርቁ ጥሪ አቅርቧል።
በመጨረሻም በጥቃቱ ሕይወታቸውን ላጡ ዜጎች ሐዘኑን የገለጸው ጥምረቱ፣ የቆሰሉት ፈጣን ማገገም እንዲያገኙ ተመኝቶ፣ ሁሉም ወገኖች መሣሪያ አውርደው ለሰላም እድል እንዲሰጡ ጥሪ አቅርቧል።
የጥምረቱ ም/ፕረዚዳንት በስልክ በዛጉዌ ሚዲያ በሰጡት መግለጫም “እኛ የሰላም ዘማሪዎች ነን፤ ዜማችንም እርቅ፣ ይቅርታና አብሮነት ነው” ሲል የገለጸው ጥምረቱ፣ ኢትዮጵያ በልጆቿ ጥረትና ሠላሟ ጸንቶ ለዘላለም እንድትኖር ምኞቱን ገልጿል።