Dr Henok Yitbarek

Dr Henok Yitbarek To create healthy mind through an interactive teaching process of evidence based psychiatric practice.

የአዕምሮ ጤና የማህበረሰብ ጤና ነው  የሚባለው ለዚህ ነው ።============================ብዙ የአዕምሮ ህሙማንን በየጎዳናው ላይ የአዕምሮ ህክምና አገልግሎት ሳያገኙ ሁልጊዜ እ...
18/10/2023

የአዕምሮ ጤና የማህበረሰብ ጤና ነው የሚባለው ለዚህ ነው ።
============================
ብዙ የአዕምሮ ህሙማንን በየጎዳናው ላይ የአዕምሮ ህክምና አገልግሎት ሳያገኙ ሁልጊዜ እየታመሙ መመልከት የተለመደ ነው ።

ዘንድሮም የአለም የአዕምሮ ጤና ቀን ሲከበር መሪ ቃሉ እንደሚለው " የአዕምሮ ጤና የማንኛውም ሰው ሰብዓዊ መብት ነው " በሚል መከበሩ ይታወሳል ።

ስለሆነም ይሄንን ቃል ወደ መሬት በማውረድ ተፈፃሚነቱን ለማረጋገጥ የሁሉም ዜጌችን ድጋፍ እና ርብርብ በማድረግ የማህበረሰባችንን ጤና ለማረጋገጥ ቀጣይ እና ዘለቄታዊ ስርዓት መዘርጋት አስፈላጊ ነው ።

ይህንን መልዕክት እንድፅፍ ያደረገኝ ሰሞኑን በአካል ከገጠመኝ እውነተኛ የጎዳና ታሪክ በመነሳት ነው ።

ታሪኩ እንዲህ ነው ፤ እኔ በምኖርበት አካባቢ አንዲት እናት በወራት እድሜ የሚገመተውን የገዛ ራሷን ልጅ በአደባባይ መሃል ለመግደል ሙከራ ስታደርግ በማህበረሰቡ ርብርብ ህፃኑ ለጊዜው ሊተርፍ ችሏል ።

ሁኔታው በጣም ስላሳሰብኝ እና ሙያዊ ግዴታዬም በመሆኑ ቀረብ በማለት ስለሁኔታው ለመረዳት ሞከርኩ ። አብዛኛው ሰው ባለማወቅ ወይም ባለመረዳት ወላጅ እናት ላይ ወቀሳ ፣ ተግፃፅ እንዲሁም አንዳንድ ሰዎች አካላዊ ጥቃት ሁሉ ለማድረስ ሲሞክሩባት ተመለከትኩ ።

በሰዓቱ የአካባቢው የፀጥታ አካላት ባደረጉት ጥረት ወላጅ እናትን እና ህፃኑን አስቸኳይ እርዳታ በማድረግ ወደ ህጋዊ ከለላ ወስደው የመጀመሪያ እርዳታ አድርገውላታል ።

በመቀጠል ሁኔታዎቹ ሲረጋጉ የምችለውን ያህል በአጠገቤ ካሉት ሰዎች ጋር ስለሁኔታው በመረዳት የአዕምሮ ህመም ሊሆን እንደሚችል በማሰረዳት መጀመር እንዳለብኝ ወሰንኩ ። ከአጠገቤ የነበሩት ሰዎችም ጥሩ መረዳት እንዳለቸው እንዲሁም ወላጅ እናትንም ሆነ ህፃኑን ለመርዳትም ዝግጁ እንደሆኑ ሲነግሩኝ ፣ ጥሩ የማህበረሰባችን አካላት እንደሆኑ ተረዳሁ ።

በመሆኑም ጉዳዩን የበለጠ ገፋ አድርጌ አንድ ርቀት በመሄድ የፖሊስ ፅ/ቤቱ ድረስ በመሄድ የምችለውን ያህል ለመርዳትም ሆነ ሙያዊ አስተያየት በመስጠት የአዕምሮ ህክምና በማግኘት ቀጣይ ህክምና እንድታገኝ የማድረግ ኃላፊነት እንዳለብኝ በማመን ተከትዬ ሄድኩ ።

የፀጥታ አካላቱ ተደጋጋሚ የህይወት ገጠመኝ ስለነበራቸው ሁኔታውን ለመረዳት ብዙም አልተቸገሩም ። እንደዚህ አይነት ሁኔታዎች ሲከሰቱ የህግ ምርመራ እና አገልግሎታቸውን ሲጨርሱ በአቅራቢያው ወደሚገኝ ማንኛም የጤና ተቋም አገልግሎት እንዲያገኙ ከሚመለከተው አካል ጋር እንደሚሰሩ ሲነግሩኝ የቤት ስራው ተስፋ ሰጪ እንደሆነ በመረዳት አመስግኜያቸው ወጣሁ ።

ወደ ዋናው መልዕክቴ ስገባ : -

በአዕምሮ ህመም የሚሰቃዩ የጎዳና ላይ እንዲሁም በተለያዩ ምክንያት በቤታቸው ውስጥ ታስረው የአዕምሮ ህክምና አገልግሎት የተነፈጉ የማህበረሰባችን አባላት በርካታ ናቸው ።

በአንድ ወቅት የጎዳና ላይ የአዕምሮ ህሙማንን ከህጋዊ የፀጥታ አካላት ጋር በጋራ በማንሳት የአዕምሮ ህክምና እንዲያገኙ የተሰሩ ስራዎች ቢኖሩም ፤ የሚመለከታቸው አጋር ተቋማት ዘለቄታዊ የአሰራር ስርዓት ስላልነበራቸው ተመልሶ የጎዳና ላይ የአዕምሮ ታማሚዎችን እየተመለከትን ነው ።

ምንም እንኳን ሰዎችን ለመርዳት ቀና እና መልካም ማህበረሰብ ቢኖረንም ፤ በማህበረሰባችን ውስጥ ያሉት መረዳቶች እና አስተሳሰቦች ለአገልግሎቱ ተሳታፊ የሆነ በቂ ማህበረሰብ ለመፍጠር አልቻልንም ።
ማነቆ ከሆኑብን የማህበረሰባችን የተዛቡ አመለካከቶች መካከል :-
1. የአዕምሮ ጤና የጤና ተቋማት ስራ ብቻ አድርጎ ማሰብ ።
2. የአዕምሮ ጤና የሁላችንም የቤት ስራ አድርገን ለመውሰድ ቁርጠኛ አለመሆን ።
3. የአዕምሮ ህመም የእኔ ህመም አይደለም የሚሉ የተዛቡ አስተሳሰቦች ።
4. በማወቅም ይሁን ባለማወቅ ምን አገባኝ በሚሉ ስሜቶች ነገሮችን በዝምታ መመልከት ።
5. የአዕምሮ ህመም ህክምና የለውም የሚሉ የተዛቡ አመለካከቶች ።
6. የማህበረሰብ ጤና የእኔም ጤና ነው የሚል ማህበረሰብ በበቂ ሁኔታ አለመፍጠር ።
7. የግንዛቤ እና የዕውቀት ማነስ
8. ወዘተ ....

ቀጣይ ትኩረት አቅጣጫዎች :-
===================
• በአሁን ሰዓት ያሉት የግል / የማህበረሰብ ድጋፍ ሰጪ የበጎ አድራጎት ድርጅቶች ቁጥር አነስተኛ በመሆኑ ቁጥራቸውን በመጨመር ከጤና ተቋማት ጋር የአዕምሮ ህክምና ትስስር በመዘርጋት ሳይንሳዊ ህክምና እንዲያገኙ ማድረግ።

• በየጎዳናው ላይ ወድቀው የሚገኙትን የአዕምሮ ህሙማን ሁሉም የማህበረሰብ አካላት የእኔም ኃላፊነት ነው በማለት ከሚመለከታቸው ተቋማት ጋር በጋራ በመስራት ቢያንስ አንድ ሰው ለማሳከም መርዳት ።

• የአዕምሮ ህመም እንደሚታከም እና ለውጥ እንደሚያመጣ ከታች ለሚገኙት ማህበረሰብ ሁልጊዜም ግንዛቤ በመስጠት ክትትል እና ድጋፍ ማድረግ ።

• ከህመማቸው ያገገሙ ታማሚዎችን የህይወት ተሞክሮ እና ጤናማ ለውጥ ዕለት በዕለት በምናገኛቸው አጋጣሚዎች ምስክር በመሆን ተነሳሽነታቸውን መጨመር ።

• የጤናው ተቋም የአንበሳውን ድርሻ እንደመውሰዱ መጠን ፤ ከባለ ድርሻ አካላት ጋር ዘለቄታዊ የአሰራር ስርዓት በመዘርጋት የማህበረሰቡን ተነሳሽነት እና ተሳትፎ በመጨመር ከማህበረሰባችን ጋር በጋራ መስራት ።

• ተከታታይነት እና ዘለቄታዊነት ያለው የድጋፍ እና ክትትል በማድረግ የአዕምሮ ህክምና የተደራሽነት አድማሱን ማስፋት ።

• ነባራዊ በሆኑት የጤና ስርዓት መዋቅር ውስጥ የአዕምሮ ጤናን ትኩረት አግኝቶ እየተሰራ ቢሆንም ፣ የበለጠ ትኩረት በመስጠት አጠናክሮ መስራት ።

• የአዕምሮ ጤና በተቋም ደረጃ ተቋቁሞ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶት ፣ ሰፊ የሆኑ የፓሊሲ ስራዎችንም ጨምሮ እንዲሰራ በመካከለኛም ሆነ በረጅም ጊዜ ዕቅድ ውስጥ የአዕምሮ ጤና በተቋም ደረጃ እንዲሰራ ዝግጁነትን ማሰብ ይፈልጋል ።

ዶ/ር ሔኖክ ይትባረክ (የአዕምሮ ሐኪም )
አማኑኤል ሆ/ል

Address

Addis Ababa

Website

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when Dr Henok Yitbarek posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Share