07/09/2026
ጳጉሜን 2 የማንሰራራት ቀን!
ጳጉሜን የአስራ ሶስት ወር ፀጋ የሆነችው ሀገራችን በረከቶች፣ ከዘመን ዘመን መሸጋገሪያ ድልድል፣ የአዲስ ዓመት መዳረሻ ብሩህ ተስፋ አብሳሪ ተጨማሪ ቀናት እና ወር ናት።
ኢትዮጵያ የራሷ የሆነ የዘመን አቆጣጠር ያላት ጥንታዊት ሀገር መሆኗን ጠቋሚ ምልክቶች፣ የአዲስ ዓመት መዳረሻ ብስራት ናቸው የጳጉሜን ቀናት።
የጳጉሜን ቀናት ከ2011 ዓ/ም ጀምሮ የህዝባችንን ወንድማማችነት እና እህትማማችነት በሚያጎለብቱ፣ የመጪውን አዲስ ዓመት ተስፋዎች በሚያንፀባርቁ ልዩ ልዩ ዝግጅቶች ሲከበሩ ቆይተዋል።
የ2018 ዓ.ም የጳጉሜን ቀናትም እንደ ሀገርም ሆነ በመዲናችን ለአዲስ ዓመት የላቁ ድሎች ተነሳሽነትን ከፍ በሚያደርግ መልኩ ‹‹ የኢትዮጵያ ማንሰራራት!›› በሚል መሪ ቃል በተለያዩ ህዝባዊ ሁነቶች እየተከበሩ ይገኛሉ።
በተለወጠ አዲስ እሳቤ፣ በዳበረ የስራ ባህል የብልፅግና ፓርቲን አሻጋሪ እሳቤዎች በተግባር በመተርጎም ኢትዮጵያን ከነበረችበት ጥልቅ ጉስቁልና በማውጣት ወደ ማንሰራራት ማሸጋገር ተችሏል፡፡
ብልሹ አሰራሮችን በማስወገድ፣ አዳዲስ አቅጣጫዎችን በመተለም፣ ለዓለም አቀፍ ጫናዎች ያልተበገረ ዲፕሎማሲያዊ ድል በማስመዝገብ፣ ባለፈው ዓመት በተባበሩ እጆቻችን ታላቁን የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ዕውን ማድረግ መቻላችን ይታወሳል፡፡
እየተገነባ የሚገኘው ግዙፉ የማዳበሪያ ፋብሪካም ለምርትና ምርታማነት ማደግ በሚኖረው ጉልህ ሚና የምግብ ዋስትናችንን እና የምግብ ሉዓላዊነታችንን ለማረጋገጥ ለምናደርገው ርብርብ ትልቅ አቅም የሚፈጥር ነው፡፡
የተገነቡ ግዙፍ ሆስፒታሎችና ጤና ጣቢያዎች ኢትዮጵያን የጤና ቱሪዝም ማዕከል ለማድረግ የተጀመረውን ጥረት ማፋጠን ችለዋል፡፡
ስታንዳርዳቸውን ጠብቀው የተገነቡ ጥራታቸውን የጠበቁ ግዙፍ መንገዶችም ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴውን አሳልጠዋል፡፡
ከመደበኛ ስራዎች ጎን ለጎን የጳጉሜን ቀናት ስናከብርም፣ የመጪውን ጊዜ ተስፋ የሚያለመልሙ፣ የህዝባችንን ማህበራዊ መስተጋብር የሚያጠናክሩ፣ ለኢትዮጵያ ማንሰራራት ፅኑ መሰረት የሚሆኑ ስራዎችን በማከናወን ሊሆን ይገባል፡፡
በአዲሱ ዓመት በግለሰብ ደረጃም ሆነ በሀገራችን ለሚከናወኑ ተግባራት እንዲሁም ለሚመዘገቡ ድሎች ሙሉ ዝግጅትን አጠናቆ ወደ ተግባር መግባትም ከሁላችንም ይጠበቃል።