26/05/2026
የባዮ እና ኢመርጂንግ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት የጫንጮ ወተት ምርት ማሻሻያ እና የሀገር በቀል ዕፅዋት መድኃኒት ምርምር ንዑስ ማዕከል በድምቀት ተመረቀ
18/9/2018 ዓ.ም................................
የአካባቢውን የእንስሳት፣ የወተት ምርታማነት እና የዕጽዋት ሀብትን በሳይንሳዊ ምርምር ለመደገፍና ለማሳደግ ታስቦ የተገነባው አዲስ የምርምር ንዑስ ማዕከል በሰሜን ሸዋ ዞን ጫንጮ ከተማ በይፋ ተመርቋል።
በዚሁ በድምቀት በተከናወነው የምረቃ ስነስርዓት ላይ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢን ጨምሮ የፌዴራል፣ የክልልና የዞን ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች፣ የአካባቢው የሀገር ሽማግሌዎች እንዲሁም በርካታ ቁጥር ያላቸው የማህበረሰብ ተወካዮች ተገኝተዋል።
በምረቃው ወቅት ማዕከሉ በአካባቢው ለሚስተዋሉ የምርትና የብዝሃ ሕይወት መመናመን ችግሮች ሳይንሳዊና ፈጣን ምላሽ ለመስጠት የተቋቋመ መሆኑ ተገልጿል።
የባዮ እና ኢመርጂንግ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ፕሮፌሰር ካሳሁን ተስፋዬ የእንኳን ደህና መጣችሁ መልዕክት ባስተላለፉበት ወቅት ይህ ንዑስ ማዕከል ሁለት አበይትና ስትራቴጂካዊ ዓላማዎችን አንግቦ ወደ ሥራ መግባቱን አብራርተዋል። የመጀመሪያው ግብ የአካባቢውን የእንስሳት ዝርያ በማሻሻል የወተት ምርትን በከፍተኛ ደረጃ ማሳደግ ሲሆን፣ ሁለተኛው ደግሞ በሀገር በቀል ዕፅዋት ላይ ጥልቅ ምርምር በማካሄድ ለዘመናዊው መድኃኒት ማምረቻ ኢንዱስትሪ የሚሆን ጥራት ያለው የግብዓት አቅርቦት ማረጋገጥ ነው።
ፕሮፌሰር ካሳሁን አክለውም የማህበረሰቡን ጥያቄ በመያዝ ወደ ኢንስቲትዩቱ በመምጣት ለዛሬው ስኬት መሠረት ለሆኑት የአካባቢው የሀገር ሽማግሌዎችና ተወካዮች እንዲሁም የመሬት አቅርቦትን ጨምሮ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ላበረከቱት ለጫንጮ ከተማና ለዞኑ አስተዳደሮች ምስጋናቸውን አቅርበው ተቋሙ ለፕሮጀክቱ ስኬት በልዩ ትኩረት እንደሚተጋ አረጋግጠዋል።
ሌላኛው ማዕከሉ ትኩረት አድርጎ ከሚሰራባቸው ዘርፎች መካከል የሀገር በቀል ዕፅዋት መድኃኒት ምርምር አንዱ ሲሆን ይህ ተግባር ሀገሪቱ ያላትን ሰፊ የብዝሃ ሕይወትና የባህላዊ ሕክምና ዕውቀት ወደ ዘመናዊ ኢንዱስትሪ ለመቀየር ትልቅ አቅም ይፈጥራል። ኢትዮጵያ እጅግ የበለፀገ የመድኃኒት ዕፅዋት ክምችት ቢኖራትም ባህላዊ ዕውቀቱ በሳይንሳዊ መንገድ ያልተሰነደና በቃል ብቻ የሚተላለፍ በመሆኑ የማህበረሰብ ሽማግሌዎችና አዋቂዎች ሲያልፉ አብሮ የመጥፋት ከፍተኛ ስጋት ደቅኗል።
ከዚህ በተጨማሪም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እየተስፋፋ የመጣው የደን መጨፍጨፍ፣ የከተሞች መስፋፋት፣ የግብርና መሬት ፍላጎት መጨመርና ዕፅዋቱን ያለአግባብ መመንጠር ለአካባቢው ስነ-ምህዳር መመናመንና ለዝርያዎቹ መጥፋት ዋነኛ ተግዳሮቶች ሆነው በመቆየታቸው አዲሱ ማዕከል እነዚህን ዕፅዋት በላቦራቶሪ በመደገፍና በመንከባከብ ረገድ የሚኖረው ሚና ከፍተኛ መሆኑ በምረቃው ላይ ተመላክቷል።
በመድረኩ ላይ ቁልፍ መልዕክት ያስተላለፉት የሰሜን ሸዋ ዞን ዋና አስተዳደሪ ተወካይ የተከበሩ አቶ ታገል ጌትነት በበኩላቸው ለማዕከሉ ግንባታ የሚሆን የመሬት አቅርቦትና ተያያዥ ድጋፎች ከጫንጮ ከተማ አስተዳደር ጋር በመሆን በቅንጅት መከናወናቸውን ጠቅሰው በቀጣይም ማዕከሉ ለሚፈልጋቸው ማናቸውም ስራዎች አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርጉ አረጋግጠዋል። አቶ ታገል በተለይም የጫንጮ እና የአካባቢው የእንስሳት እና ወተት ልማት በአሁኑ ወቅት ከፍተኛ አደጋ የተጋረጠበት መሆኑን በመጥቀስ ይህንን የወተት ኮሪደር ወደ ቀድሞ ህልውናውና ምርታማነቱ ለመመለስ ከአዲሱ የምርምር ማዕከል ፈጣንና ውጤታማ ምላሽ እንደሚጠበቅ በአጽንዖት አሳስበዋል።
የሰሜን ሸዋ ዞን በተለይም የጫንጮ አካባቢ ለአዲስ አበባና ለሌሎች ትላልቅ ከተሞች ባለው ቅርበት እንዲሁም ለእንስሳት እርባታ ምቹ በሆነው የአየር ንብረቱ ሳቢያ ከፍተኛ የወተት ምርት አቅም ያለው ቀጠና ቢሆንም በአሁኑ ወቅት በርካታ ስር የሰደዱ ችግሮች እየተፈታተኑት ይገኛሉ። ጥራትና ብዛት ያለው የእንስሳት መኖ እጥረት፣ ለግጦሽ የሚሆን የመሬት ጥበት፣የነባር እንስሳት ዝርያ ደካማ የወተት ምርት አቅም፣ በቂ የእንስሳት ሕክምናና የሰው ሰራሽ ማባዣ አገልግሎት ተደራሽ አለመሆን እንዲሁም የገበያ ትስስር ማነስ ዘርፉን ክፉኛ የጎዱት ዋነኛ ተግዳሮቶች ናቸው።
እነዚህ ችግሮች በአርሶ አደሩና በአርብቶ አደሩ ኢኮኖሚ ላይ የፈጠሩትን ጫና ለመቀረፍ አዲሱ ንዑስ ማዕከል የሚያቀርባቸው ሳይንሳዊ የምርምር ውጤቶችና የተሻሻሉ ዝርያዎች እንደ ትልቅ መፍትሔ ተወስደዋል።
የማጠቃለያ ንግግርና የቀጣይ የሥራ አቅጣጫ የሰጡት በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሰው ሀብት ልማት፣ ሥራና ስምሪት እና ቴክኖሎጂ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ዶ/ር ነገሪ ለንጮ ኢንስቲትዩቱ በአካባቢው የገነባው ማዕከል ታሪክ የማይረሳውና ተቋሙ ለማህበረሰቡ ያለውን የላቀ ቅርበትና ፍቅር ያሳየበት ሰው ተኮር ተግባር መሆኑን ገልጸው አድንቀዋል።
የማህበረሰቡ ጥያቄዎችና ዘርፈ ብዙ ችግሮች ዘላቂ ምላሽ ማግኘት የሚችሉት በሳይንሳዊ ምርምር ብቻ መሆኑን ያስገነዘቡት ዶ/ር ነገሪ ማዕከሉ በቀጣይ በልዩ ትኩረትና በዕቅድ በመመራት በአጭር ጊዜ ውስጥ ተጨባጭ ውጤት በማስመዝገብ የአካባቢውን ህዝብ ከእንስሳትና ከወተት ልማት ጋር ተያይዘው ካሉበት ስር የሰደዱ ችግሮች ማውጣት እንዳለበት የስራ አቅጣጫ አስቀምጠዋል።
በመጨረሻም በምረቃ ስነስርዓቱ ላይ የተሳተፉት የአካባቢው ነዋሪዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በማዕከሉ መከፈት የተሰማቸውን ከፍተኛ ደስታ በመግለፅ ማዕከሉ ለታለመለት ዓላማ እንዲበቃና ቀጣይነት ያለው ስኬት እንዲያስመዘግብ የበኩላቸውን እገዛ እንደሚያደርጉ ቃል በመግባት ለቀጣይ ስራዎች የሚረዱ ጠቃሚ ሀሳቦችን በግብዓትነት አቅርበዋል።
18/9/2018 ዓ.ም (BETin)