05/09/2026
"ባለፉት አምስት ዓመታት በምክር ቤቱ ለተከናወነው አበረታች ሥራ የምክር ቤቱ ጽሕፈት ቤት ሠራተኞች ሚና የጎላ ነው” — የተከበሩ አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ
-------------------
(ዜና ፓርላማ) ነሐሴ 30፣ 2018 ዓ.ም፤ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባኤ የተከበሩ አቶ ታገሰ ጫፎ፣ ባለፉት አምስት ዓመታት በምክር ቤቱ ለተከናወኑ ውጤታማና አበረታች ተግባራት የምክር ቤቱ ጽሕፈት ቤት ሠራተኞች ያበረከቱት አስተዋጽኦ ከፍተኛ መሆኑን ገልጸዋል።
ሠራተኞቹ ላሳዩት የላቀ የሥራ አፈጻጸም ምስጋናቸውን በማቅረብ፣ ሽልማት አበርክተዋል።
አፈ ጉባኤው ይህንን የገለጹት፣ በ2018 ዓ.ም. በሥራቸው የላቀ ውጤት ላስመዘገቡ የጽሕፈት ቤቱ ሠራተኞች በተዘጋጀው የዕውቅናና የምስጋና ሽልማት ሥነ-ሥርዓት ላይ ተገኝተው ባደረጉት ንግግር ነው።
በዕለቱ በተሰጠው ሽልማት ላይ ጥቂት ሠራተኞች ቢመረጡም፣ በተግባር ግን ሁሉም የጽሕፈት ቤቱ ሠራተኞች ተሸላሚ መሆናቸውን አፈ ጉባኤው ገልጸዋል።
አክለውም፣ የምክር ቤቱ ሥራዎች በስኬት ሊጠናቀቁና ውጤታማ ሊሆኑ የቻሉት በመላው ሠራተኛ ያልተቆጠበ ጥረትና ድካም መሆኑንም አስረድተዋል።
የምክር ቤቱ ጽሕፈት ቤት ሠራተኞች እስከ አሁን ላደረጉት አበረታች አስተዋጽኦ ምስጋናቸውን ገልጸው፣ በቀጣይም ተቋማዊ ስኬቱን አጠናክረው እንዲቀጥሉ ትልቅ የሥራ አደራ ጥለውባቸዋል።
በቀጣይ የሚመጡ አዳዲስ የምክር ቤት አባላትን በተለመደው የምክር ቤቱ ደንብና አሠራር መሠረት ተቀብለው በብቃት እንዲያገለግሉ አሳስበዋል።
የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ጽሕፈት ቤት ዋና ጸሐፊ ተወካይ እና የአስተዳደር ዘርፍ ምክትል ዋና ጸሐፊ አቶ ከረዩ ባናታ በበኩላቸው፣ ጥሩ አፈጻጸም ላሳዩ ሠራተኞች ዕውቅና መስጠት ለሌሎች አርአያ የሚሆንና ለተቋም ግንባታ ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል።
የማበረታቻ ሽልማቱ ዋና ዓላማ የጽሕፈት ቤቱን ተልዕኮ ውጤታማ ለማድረግ መሆኑን አብራርተዋል።
ይህ ሽልማት በጽሕፈት ቤቱ ሥር ያሉ የተለያዩ የሥራ ክፍል ኃላፊዎች ባቀረቡት የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት መነሻነት የተዘጋጀ መሆኑን በመጠቆም፣ በቀጣይም ሌሎች ሠራተኞች ለተሻለ ውጤት እንዲነሳሱ እንደሚያደርግ አብራርተዋል።
የምክር ቤቱ ጽሕፈት ቤት የመንግሥት ዋና ተጠሪ ጉዳዮች መሪ ሥራ አስፈጻሚ እና የምክር ቤቱ ጽሕፈት ቤት ምክትል ዋና ጸሐፊ (የሙያዊ ዘርፍ ተወካይ) ወ/ሮ ቁስቋም ማሞ፣ ሽልማቱ ከቁሳዊ ዋጋው ባሻገር ለሌሎች ሠራተኞች መልካም ተሞክሮ የሚፈጥርና የጽሕፈት ቤቱን ሥራዎች በብቃት ለማከናወን የሚያስችል መሆኑን በመግለጽ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል።
(በሀብታሙ አብርሃም)
ተጨማሪ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
በፌስቡክ http://www.facebook.com/hoprparliament
በዩቲዩብ
https://www.youtube.com/
በቴሌግራም
https://t.me/ParlamaNews
በትዊተር
http://twitter.com/fdrehopr
በዌብሳይት
www.hopr.gov.et ይከታተሉ።