05/03/2024
እንኳን ለ46ኛው የካራማራ ድል በዐል በሰላም አደረሳችሁ💚💛❤️
“ታላቋ ሶማሊያን” እውን በማድረግ ቅዠት የተለከፉት የሶማሊያ መሪ ዚያድ ባሬ በ1969ዓ.ም በምሥራቅ ኢትዮጵያ 700 ኪሎ ሜትር ድረስ ዘልቀው በመግባት ኢትዮጵያን ወራ ነበር።ኢትዮጵያውያን ካራማራ ተራራ አካበቢ በእልህ አስጨራሽ ውጊያ፣ ድል ያደረጉበት መታሰቢያ ቀን በነገው እለት በኢትዮ_ኩባ ፓርክ በድምቀት ይከበራል፡፡
ጄኔራል ዚያድ ባሬ በ1969 ኢትዮጵያን ለመውረር ሲወስን አንዱ ገፊ ምክንያት፣ ኢትዮጵያውያን በወቅቱ በውስጣዊ ፖለቲካ ተከፋፍለው መገኘታቸው ነበር፡፡
በወቅቱ ኢትዮጵያን ሲያስተዳድር የነበረው የደርግ መንግስትም ሀገሪቱን ከተቆጣጠረ የሦስት ዓመት ዕድሜ የነበረውና በውስጣዊ የፖለቲካ ክፍፍልም በከፍተኛ ደረጃ ተወጥሮ የነበረበት ጊዜ ነበር፡፡ ዚያድ ባሬ በአሜሪካን ታግዞ በወቅቱ መፍጠር ከቻለው የጦር አቅም አንጻር ድል እንደሚያደርግ ተማምኖ ነበር የመጣው፡፡
የወቅቱ የኢትዮጵያ ሶሻሊስት መሪዎች ተጨማሪ ለሦስት ወራት 300 ሺህ ሚሊሺያ በወቅቱ አጠራር (ሕዝባዊ ሠራዊት) በማሰልጠን ከመደበኛው ጦር ጋር በአብዮት አደባባይ ታላቅ ሠልፍ በማዘጋጀት ካስተዋወቁ በኋላ ከጠላት ጋር ተፋለሙ፡፡ የሶማሊያ ጦር የቆሬን የመከላከያ ቀጣና በጎን በማለፍ በጃርሶና ኮምቦልቻ በኩል አድርጎ ድሬዳዋን፣ በፌዲስና ሐኪም ጋራ በኩል ሐረርን ለመያዝ ታኅሣስ 15 ቀን 1970 ዓ.ም. ጀምሮ ከፍተኛ ማጥቃት ቢያደርግም ጀግኖቹ ኢትዮጵያውያን ወደ ሐረር በመገስገስ ላይ የነበረውን ፌዲስ ላይ፣ ድሬዳዋን ለመያዝ በመገስገስ ላይ የነበረውን ድሬዳዋ አውሮፕላን ማረፊያና ጨርቃ ጨርቅ ፋብሪካው አካባቢ ሁለት ከፍተኛ የመልሶ ማጥቃት ዘመቻዎችን በማካሄድ ጠላትን አይቀጡ ቅጣት ቀጡ፡፡
ኢትዮጵያ በታሪክ እጅ እንድትሰጥ እና ታሪኳ እንዲበላሽ ሲያሴሩ የኖሩት የኔቶ አባል ሀገራት እና ግብጽ ለሶማሊያው ዚያድባሬ እገዛ በማድረግ ሉዓላዊት
ኢትዮጵያን ለማስደፈር እና በእጃቸው መዳፍ ለማድረግ ያልቆፈሩት ጉድጓድ አልነበረም፤ ሳይሳካ ተሸንፈው ማቅ ለበሱ እንጅ፡፡በመጨረሻም የአባቶቻቸውን ታሪክ በማደስ ጀግንነታቸውን ያደሱት ኢትዮጵያውያን አብዛኛውን ምሥራቃዊ ደጋ ክፍል ነፃ በማውጣት የካቲት 26 ቀን 1970 ዓ.ም እጅግ ‹‹ስትራቴጂካዊ››
የሆነውን የካራማራን ኮረብታና አካባቢ ከወራሪው ጠላት በከፍተኛ መስዋትነት አስለቀቁ፡፡ የካቲት 27 ቀን 1970 ዓ.ም የጅግጅጋ ከተማና አካባቢዋን በቁጥጥር ስር አውለው ሰንደቅ ዓላማቸውን በነፃነት እና በኩራት ዳግም እንድትውለበለብ አደረጉ፡፡
በዚህ ጦርነት ከ60,000 በላይ ኢትዮጵያውያን የተሰው ሲሆን በዓሉ ብሔራዊ በዓል ሆኖ እንዲከበር የተለያዩ ወገኖች እስካሁን ጥያቄ እያቀረቡ እንደሆነ ይታወቃል፡፡