05/09/2026
“የሕብረተሰባችንን ተሳትፎ መሠረት ያደረገ የሰፈር ልማት ፕላን እውን እናደርጋለን!” ፦ አቶ ገመዳ መሀመድ
ነሐሴ 30/2018 ዓ/ም
ሀላባ ቁሊቶ
በሀላባ ቁሊቶ ከተማ አስተዳደር እየተዘጋጁ ባሉት የሰፈር ልማት ፕላኖች (NDPs) ዙሪያ ከነዋሪዎችና ከባለድርሻ አካላት ጋር ትኩረት ያደረገ ሰፊ የችግሮች ልየታ የውይይት መድረክ ተካሄዷል።
የዕለቱን የውይይት መድረክ የሀላባ ቁሊቶ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ገመዳ መሀመድ፣ የክልሉ ከተማ ልማት ቢሮ ምክትል ሃላፊ አቶ እሼቱ ካሰ እና የሀላባ ዞን ከተማ ልማት መምሪያ የዋና ሃላፊ ተወካይና የመመሪያ ፕላን ዘርፍ ሃላፊ ኢንጂነር ሀብሲሳ መሀመድ በጋራ መርተዋል።
በመድረኩም በከተማ አስተዳደሩ በዙሪያ ቀጠናዎች በ10 ሳይቶች የሰፈር ፕላን ትግበራ በተግባር እየተካሄደ እንደሚገኝ ተገልጿል።
የሀላባ ቁሊቶ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ገመዳ መሀመድ የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሕብረተሰባችንን ተሳትፎ መሠረት ያደረገ የሰፈር ልማት ፕላን እውን እናደርጋለን ብለዋል።
ከተማችንን ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ ከመጣው የዕድገት ፍላጎት ጋር ለማጣጣም እና ዘመናዊ መዋቅር እንዲኖራት ለማድረግ የሰፈር ልማት ፕላኖች ሚና ከፍተኛ መሆኑን አንስተዋል።
የህብረተሰቡን ተሳትፎ በማጠናከር የሚስተዋሉ የመልካም አስተዳደርና የፕላን አፈፃፀም ችግሮችን በጋራ መፍታት ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ እንደሚገኝም አብራርተዋል።
የክልሉ ፕላን ኢንስቲትዩት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ እሸቱ ካሳ እንደተናገሩት ፕላኖች በወረቀት ላይ ብቻ ሳይወሰኑ መሬት ላይ ወርደው የህብረተሰቡን የኑሮ ሁኔታ የሚቀይሩ መሆን እንዳለባቸው አጽንኦት ሰጥተው ተናግረው ለዚህም የባለድርሻ አካላትና የነዋሪዎች ቀጣይነት ያለው ንቁ ተሳትፎና ባለቤትነት ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል።
አሁን ላይ የሚሰራው የሰፈር ፕላን የነገዋን የከተማ ገጽታ የሚገነባ፣ የትውልድ ዕጣ ፈንታ የሚያሳድግ እና የጋራ ብልጽግና ማዕቀፍ ነው ብለዋል። ፕላኑ ተፈጻሚ ሲሆን ከተማዋን ለኑሮ ምቹ፣ ለንግድ ማራኪ እና ለትውልድ የምትመች እንደሚያደርግም ገልጸዋል።
የሀላባ ዞን ከተማ ልማት መምሪያ የዋና ሃላፊ ተወካይና የመመሪያ ፕላን ዘርፍ ሃላፊ ኢንጂነር ሀብሲሳ መሀመድ ይህ የውይይት መድረክ በሂደት ላይ ያሉ የሰፈር ልማት ፕላኖችን ክፍተቶች በመሙላት የተሻለና ኑሮን ምቹ ያደረገች ከተማ ለመፍጠር ትልቅ መሠረት የሚጥል ነው ብለዋል።