02/06/2026
#የውኃ መስመሮች እንክብካቤና የጋራ ኃላፊነታችን
ውኃ የሕይወት መሠረት፣ የጤናችንና የዕለት ተዕለት እንቅስቃሴያችን ዋስትና ነው። ንጹሕ የቧንቧ ውኃ እስከ ቤታችን ድረስ ተደራሽ እንዲሆን የውኃ መስመሮች (አውታሮች) የሚጫወቱት ሚና በቀላሉ የሚገመት አይደለም። ይሁን እንጂ እነዚህን ውድ ንብረቶች መጠበቅና መንከባከብ የመንግሥት ወይም የባለሙያዎች ብቻ ሳይሆን የሁላችንም የጋራ ኃላፊነት ነው።
1. የውኃ መስመሮችን መንከባከብ ለምን አስፈለገ?
ብክነትን ለመቀነስ፦ በየቀኑ በሚያፈሱና በተሰበሩ መስመሮች ምክንያት የሚባክነው ውኃ ከፍተኛ ነው። መስመሮቹን በመጠበቅ የውኃ እጥረትን መቅረፍ ይቻላል።
ንጽሕናን ለመጠበቅ፦ የተበላሹና የተቀደዱ የውኃ ቧንቧዎች ቆሻሻና ተላላፊ በሽታ አምጪ ተህዋስያን ወደ ንጹሑ ውኃ እንዲገቡ በር ይከፍታሉ።
የንብረት ውድመትን ለመከላከል፦ የመስመሮች መፍሰስ የመንገዶች መበላሸትን፣ የህንጻዎች መሠረት መዳከምንና የአፈር መሸርሸርን ያስከትላል።
2. የእኛ ድርሻ እና ኃላፊነት ምንድን ነው?
"ንጹሕ ውኃ ለሁሉም እንዲደርስ፤ እያንዳንዱ የውኃ ቧንቧ ጥበቃ ያስፈልገዋል!"
አርቆ ማሰብና ጥንቃቄ ማድረግ፦ በየአካባቢያችን ግንባታዎችን ስናከናውን፣ መሠረተ ልማት ስንዘረጋ ወይም ለእርሻና ለተለያዩ ሥራዎች መሬት ስንቆፍር የውኃ መስመሮች እንዳይበጠሱ ቅድመ ጥንቃቄ ማድረግ ።
ፈጣን ጥቆማ መስጠት፦ በየመንገዱም ሆነ በሕዝብ መገልገያ ቦታዎች ላይ የውኃ መፍሰስ (ሊኬጅ) ሲያጋጥም፣ ሳይዘገዩ በአቅራቢያዉ ላለ የዉኃና ፍሳሽ አገልግሎት ድርጅት ቅርንጫፍ በአካል ወይም በስልክ ጥቆማ መስጠት።
ሕገ-ወጥ ድርጊቶችን መከላከል፦ ያለአግባብና ያለቆጣሪ ከመስመር ውኃ መጥለፍን (ሕገ-ወጥ ቅጥያ) መከላከልና መቆጣጠር። ይህ ድርጊት የውኃ ግፊትን ከመቀነሱም በላይ የሌሎችን ዜጎች ዉኃ የማግኘት መብት ይጋፋል።
የውስጥ መስመሮችን መፈተሽ፦ በየቤታችንና በየተቋማቶቻችን ያሉትን የውኃ መውረጃዎች፣ ቧንቧዎችና የፊቲንግ ዕቃዎች በየጊዜው በመፈተሽ ብልሽቶችን በፍጥነት ማስተካከል።
የውኃ መስመሮችን በአግባቡ መያዝ ማለት የራሳችንን ጤና፣ ኢኮኖሚና የወደፊት ሕይወት መንከባከብ ማለት ነው። ዛሬ የምናደርገው እያንዳንዷ ጥንቃቄ ነገ ለልጆቻችን የሚተርፍ ንጹሕ መሠረተ ልማት ለመገንባት መሠረት ነው።
#ኃላፊነታችንን እንወጣ፤ የውኃ መስመሮቻችንን እንጠብቅ!
የባህር ዳር ከ/መ/ዉ/ፍ/አገ/ድርጅት
ለባሕር ዳር ከተማና ለአካባቢው ማህበረሰብ ደህንነቱ የተጠበቀ፣አስተማማኝ፣ዘላቂና በተመጣጣኝ ዋጋ የዉኃና ፍሳሸ አገልግሎቶችን ማቅረብ።
Provide Safe, Reliable, Sustainable and Affordable water and sewerage service to Bahir Dar city and the serawunding.