08/05/2026
"አረጋዊያንን መርዳት የሕሊና እርካታ ነው።" የሰሜን ጎንደር ዞን የመቄዶንያ ቅርንጫፍ።
ሚያዚያ 30/2018 ዓ.ም (ሰሜን ጎንደር ኮሙዩኒኬሽን)
የሰሜን ጎንደር ዞን የኅብረት ሥራ ማኅበራት ተጠሪ ጽሕፈት ቤት በደባርቅ ከተማ ለሚገኘው መቄዶንያ አረጋዊያንና የሕሙማን መርጃ ማኅበር የስኳርና የዘይት ድጋፍ አድርጓል።
የድጋፉን ያስረከቡት የዞኑ የኅብረት ሥራ ማኅበራት ተጠሪ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ወይዘሮ አስራት ከብረት የደባርቅ ከተማ ዩኒዬን አስተባብሮ 50 ኪሎ ግራም ስኳርና 150 ሊትር ዘይት ድጋፍ ማድረጉን ተናግረዋል። ዩኒዬኑ ባስቀመጠው ደንብና መመሪያ መሠረት ከሚያገኘው ትርፍ ለማኅበራዊ አገልገሎት በፐርሰንት እንዲቆረጥ አድርጎ ለማኅበራዊ አገልግሎት የሚውለውን የትርፍ ክፍፍል ለመቄዶንያ እንዲውል ወስኗል ብለዋል።
ወይዘሮ አስራት እንደሚሉት "ሰው ለመርዳት ሰው መኾን በቂ ነው" የሚለውን የመቄዶንያ መሪ ቃል መደገፍና መርዳት የሁሉም ተቋም ኃላፊነት እንደኾነ ተናግረዋል። ይህን መነሻ በማድረግ በዞኑ ውስጥ የሚገኙ መሠረታዊ የኅብረት ማኅበራት መቄዶንያን መደገፍ እንዳለባቸው አሳስበዋል።
የሰሜን ጎንደር ዞን ከተማና መሠረተ ልማት መምሪያ ኃላፊና የመቄዶንያ አስተባባሪ አቶ ወገኔ አማረ ለተደረገው ድጋፍ ምስጋና አቅርበው አረጋዊያን ከመርዳት በላይ ትልቅ ተግባር እንደሌለ አስገንዝበዋል። የሰሜን ጎንደር ዞን የኅብረት ሥራ ማኅበራትና የደባርቅ ዩኒዬን ያደረጉት ድጋፍ በጎ አስተሳሰብ በመኾኑ ሌሎች ግለሰቦች፣ የመንግሥት ተቋማትና መንግሥትዊ ያልኾኑ ድርጅቶች ድጋፋቸው ተጠናክሮ እንዲቀጥል ሲሉ መልእክት አስተላልፈዋል።
መቄዶንያ የሰሜን ጎንደር ዞን ቅርጫፍ አስተባባሪ ዲያቆን አስማማው መንግሥቴ ለተደረገላቸው ድጋፍ በማኅበሩ ስም ላቅ ያለ ምስጋና አቅርበዋል። ለሀገር ባለውለታ የኾኑት በመቄዶንያ ግቢ የተጠለሉ አረጋዊያን የሰው ናፍቆት ስላለባቸው ሁሉም ሰው ቢጎበኛቸው የሚል አስተያየት ሰጥተዋል።
እንደ ሀገር ከ8,500 በላይ አረጋዊያን በመቄዶንያ እንክብካቤ እየተደረገላቸው እንደኾነ የጠቆሙት ዲያቆን አስማማው እንደ ደባርቅ ቅርንጫፍ ከግንቦት 1/2018 ዓ.ም ጀምሮ አረጋዊያንን ከጎዳና ላይ የማንሳት ሥራ እንደሚሠራ ጠቅሰዋል። ማንኛውም በጎ እና ቅን ልቡና ያለው ሰው ሁሉ በሚችለው ልክ ድጋፍ እንዲያደርግላቸው ሲሉ አሳስበዋል።
በመጨረሻም አረጋዊያኑ ለመቄዶንያ መሥራችና ድጋፍና እንክብካቤ ለሚያደርጉት ወገኖች ሁሉ ምስጋና እና አባታዊ ምርቃንም ለግሰዋል።