25/06/2026
በ2018 በጀት ዓመት በወሳኝ ኩነቶች ምዝገባ አገልግሎት 17,369 ዜጎችን ተጠቃሚ ማድረጉን የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር ሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ ቡድን አስታወቀ ።
ሰኔ 17/2018ዓ.ም
የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር ሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ ቡድን ከባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን የ2018 በጀት ዓመት ዕቅድ አፈፃፀም ግምገማና የግንዛቤ ፈጠራ መድረክ አካሂዷል። በበጀት ዓመቱም 17,369 ዜጎችን የሲቪል ምዝገባ በመመዝገብ የዕድሜ ልክ የምስክር ወረቀት ባለቤት ማድረጉን የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር ሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ ቡድን መሪ አቶ ሰለሞን ጌታቸው ገልፀዋል ።
የሰቪልና ቤተሰብ ምዝገባ ፖለቲካዊ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ልማትን ለማቀድ፣ የተለያዩ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ አገልግሎቶችን ዜጎች ማግኘት እንዲችሉ ለማድረግ፣ በፍትሕ አስተዳደር ቀልጣፋና ውጤታማ አሠራር እንዲኖር ለማስቻል የሲቪል እና የቤተሰብ ምዝገባ ቁልፍ ሚና ይጫወታል ብለዋል።
የምዝገባ አፈፃፀሙ በበጀት አመቱ ለመመዝገብ ከታቀደው አኳያ ከፍተኛ ቢሆንም በአንዳንድ ክፍለ ከተሞች የታየው የወቅታዊ ምዝገባ አፈፃፀም ዝቅተኛ ሆኖ በመገኘቱ በቀጣይ ከተማ አስተዳደሩ በልዩነት ገምግሞ አስፈላጊውን ማስተካከያ እንደሚያደርግና የ2019 በጀት ዓመት የትኩረት ነጥብ መሆኑን ተናግረዋል ።
በምዝገባ አፈፃፀም በቅንጅታዊ ስራዎች ፣ በቴክኖሎጂ አመዘጋገብና በሌሎችም በዩኒሴፍ ድጋፍ በአጠቃላይ ለ648 ሚመለከታቸው የንድፈ ሃሳብና ተግባር ስልጠና መሰጠቱን ተገልፀዋል።
የተመዘገቡ ስኬቶችና የባለድርሻ አካላት ቅንጅት በበጀት ዓመቱ ውስጥ የልደት፣ የጋብቻ፣ የፍቺ እና የሞት ኩነቶችን በትክክል በመመዝገብ ረገድ ከፍተኛ መሻሻል የታየ ሲሆን፣ የተቀናጀ አሰራርን በመዘርጋት የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ማሳደግ ተችሏል። ይህም ከተማዋ ወደ ዘመናዊ የዲጂታል አሰራር ለምታደርገው ሽግግር ትልቅ እምርታ መሆኑ ተገልጿል። ከጤና ተቋማት፣ ከእድር አመራሮችና ከማህበረሰብ አንቀሳቃሾች ጋር የተደረገው ቅንጅታዊ አሰራር ለዕቅዱ መሳካት በዋናነት የተጠቀሰ ጥንካሬ ነው።
በ2018 በጀት ዓመት የተለያዩ አማራጮችን በመጠቀም ለ103,042 ህብረተሰብ ግንዛቤ መፈጠሩን ያስታወቁት አቶ ሰለሞን ከተማ አስተዳደሩ ከፋና ሬድዮ ጣቢያ ጋር ውል በመግባት የሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ መልዕክቶች ለከተማው ነዋሪ ተደራሽ እንዲሆን መሰራቱን ገልፀው ለቀጣይም ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል ።
የአገልግሎት አሰጣጡ ከብልሹ አሰራር በፀዳ መንገድ እንዲሳለጥ ከሚመለከታቸው ጋር በመቀናጀት ስራዎች በመከናወናቸው በበጀት ዓመቱ ለውጦች መታየታቸውን ጠቁመው በአዲሱ በጀት ዓመትም ክትትሉ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።
ቡድን መሪው አክለውም በበጀት ዓመት በሁሉም ኩነቶች የተጀመሩት ስራዎች የሚበረታቱ መሆኑን ገልፀው ከንቲባው ቃል በገቡት መሰረት የቀበሌ መዝጋቢ ባለሙያ ቅጥር እና ቁሳቁሶችን በማሟላት ሌሎች ለኦንላይን ምዝገባ የሚያግዙ በጀት በመመደብ ስራው እንዲፋጠን ያሳሳቡ ሲሆን ተሳታፊዎች በበኩላቸው የኦንላይን ምዝገባ ስራቸውን እንዲፋጠን ገልፀዋል፡፡
በመድረኩ ማጠቃለያ ላይ የዕቅድ አፈፃፀም ሪፖርቱን መነሻ በማድረግ ከተሳታፊዎች ጋር ሰፊ ውይይት የተደረገ ሲሆን፣ በቀጣይ በጀት ዓመት ምዝገባውን ይበልጥ ተደራሽ ለማድረግና ያሉትን የአሰራር ክፍተቶች ለማረም የሚያስችሉ የጋራ አቅጣጫዎች ተቀምጠዋል።