11/08/2026
የሰሜን ሸዋ ዞን መንገድ፣ ትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ መምሪያ የሐምሌ ወር አፈጻጸምን ገመገመ።
ደብረ ብርሃን፦ ነሐሴ 5 ቀን 2018 ዓ.ም (ሰሸዞመኮ) በአማራ ክልል የሰሜን ሸዋ ዞን መንገድ፣ ትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ መምሪያ ከወረዳና ከተማ አስተዳደር ተቋማት ጋር በመሆን የሐምሌ ወር አፈጻጸሙን በዙም ሚቲንግ ገምግሟል።
መምሪያው በ90 ቀናት ውስጥ ለማከናወን ያቀዳቸውን መደበኛ ተግባራትና የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ሥራዎች የሐምሌ ወር አፈጻጸምን ገምግሟል።
በግምገማው የሐምሌ ወር ዋና ዋና ተግባራት በዝርዝር ቀርበው፣ የተገኙ ጥንካሬዎችና የታዩ እጥረቶች በመለየት ሰፊ ውይይት ተደርጓል።
በግምገማው ወቅት በቀጣይ በትራንስፖርት ዘርፍ የግንዛቤ ፈጠራ ሥራዎችን ማጠናከር፣ መደበኛ ቁጥጥርን በማጠናከር ሕገወጥነትን መከላከል፣ ቅንጅታዊ አሠራርን ማጠናከር እንደሚገባ ተመላክቷል።
የመናኸሪያ ስምሪትንና አገልግሎት አሰጣጥን እንዲሁም መሠረተ ልማትን ማሻሻልና ማዘመን፣ የድንገተኛ ተሽከርካሪ ምርመራ አገልግሎትን ማጠናከር እና ሁሉአቀፍ ክትትልና ድጋፍ ማድረግ እንደሚገባ አቅጣጫ ተሰጥቷል።
ከመንገድ ዘርፍ አንጻርም የቅድመ ዝግጅት ሥራዎችን ከወዲሁ መጀመር፣ በሁሉም ዘርፍ ሕዝቡን ባለቤትና ተሳታፊ በማድረግ በትኩረት መሥራት እንደሚገባ ጠበቅ ያለ አቅጣጫ ተሰጥቷል።
መድረኩን የመምሪያው ኃላፊ አቶ ደጀኔ በቀለ የመሩ ሲሆን፣ በመድረኩ የዞን ማኔጅመንት አባላት፣ የወረዳና ከተማ ኃላፊዎችና የማኔጅመንት አባላት እንዲሁም የወረዳና ከተማ ትራፊክ ፖሊስ አስተባባሪዎች ተገኝተዋል።