05/09/2026
በደብረ ብርሃን ከተማ ሰክሰስ ፕላስ ከሴቶች ወጣቶች ማኅበራዊ ጉዳይ ጋር በመተባበር የ5 ሚሊዮን ብር ዊልቸር ለአካል ጉዳተኞች ድጋፍ አደረገ፤
በድጋፍ ርክክቡ ላይ የተገኙት የደብረ ብርሃን ከተማ ተቀዳሚ ከንቲባ አቶ በድሉ ውብሸት እንደተናገሩት፣በከተማው አካል ጉዳተኞች በማኅበራዊ፣ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ዘርፎች ተጠቃሚ እንዲሆኑ የተሰራው ሥራ ውጤታማ ነው ብለዋል።
በተለይም አካል ጉዳተኞች ሰርተው ራሳቸውን እንዲችሉና እንዲለውጡ መስሪያና መሸጫ ቦታ በማመቻቸት፣የመኖሪያ ቤት በመስጠት፣ተደራጅተው የመኖሪያ ቤት መስሪያ ቦታ በማቅረብ እንዲሁም በቅርበት ክትትልና ድጋፍ በማድረግ በኩል ብዙዎችን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን አመልክተዋል።
በዕለቱም ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ፣ የክልሉ ሴቶች ወጣቶች ማኅበራዊ ጉዳይ ቢሮ ከበጎ አድራጎት ድርጅቱ ጋር በመተባበር የተደረገው ድጋፍ
የመንቀሳቀስ ችግር ያለባቸውን ችግር ለመፍታት ከፍተኛ ጥቅም እንዳለው በመጠቆም ምስጋና አቅርበዋል።
በቀጣይም ለአካል ጉዳተኞች የሚደረገው ድጋፍ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ፍንጭ ሰጥተዋል።
የሰክሰስፕላስ የበጎ አድራጎት ድርጅት ሥራ አስኪያጅ አቶ ፍሬውሁን መንገሻ በበኩላቸው፣ድርጅቱ ባላፉት ሶስት ዓመታት በኢትዮጵያ በአራቱም አቅጣጫዎች ለአካል ጉዳተኞች ዘርፈ ብዙ ድጋፎችን ሲያደርግ መቆየቱን አስታወቀዋል።
ድርጅቱ በዋናነት በዊልቸር ድጋፍ፣በገቢ ማስገኛ፣በትምህርት ዕድልና ስፖንሰርሺፕ በመስጠት ከመንግስት ጋር በመተባበር እየሰራ እንደሚገኝ ጠቁመው፣ዛሬም በደብረ ብርሃን ከተማ ለሚገኙ አካል ጉዳተኞች 5 ሚሊዮን ብር ወጪ የሆነበት 100 ዊልቸር ድጋፍ ማድረጋቸውን አስታውቀዋል።
በአካል ጉዳተኞች ዘርፍ የሚታዩ የተሳሳቱ አመለካከቶችን ለማረም እና ሁለንተናዊ ተሳትፏቸውን ለማረጋገጥ እየተሰራ መሆኑን በሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚንስቴር የአካል ጉዳተኞች ሥራ አስፈፃሚ አቶ ሲሳይ ጥላሁን አስታውሰው፣አሁን ግን መንግስት ለዘርፉ በሰጠው ልዩ ትኩረት ተሳትፏቸውን የሚያረጋግጡ ስራዎች
እየተከናወኑ እንደሚገኙ አመልክተዋል።
የአካል ድጋፍ መሳሪያዎች ዋጋቸው ውድ በመሆኑ በራሳቸው ገዝተው ለመጠቀም ለማይችሉ ወገኖች ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ከፌዴሬሽኑ፣ከሰርከስ ፕላስ እና ከአማራ ክልል ሴቶችና ማህበረሰብ ጉዳይ ቢሮ ጋር በመተባበር የድጋፍ ስራዎችን እያከናወነ ይገኛል ብለዋል።
የአማራ ክልል ሴቶች ወጣቶች ማኅበራዊ ጉዳይ ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ብርቱካን ሲሳይ አክለው እንደገለጹት፣አካል ጉዳተኞች በማህበረሰቡ ዘንድ ባለው የተዛባ አመለካከት፣ የተደራሽነት እጥረት፣ የባለሙያና የተቋማት አሰራር ድክመቶች ምክንያት ለአካላዊ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች ተጋልጠው እንደሚገኙ ጠቁመዋል።
የኢኮኖሚና የህክምና አገልግሎት እጥረ፣የመሰረተ ልማትና የተደራሽነት ችግር፣የትምህርትና የመረጃ ተደራሽነት እጥረት፣የህጎችና ስማምነቶች አፈፃጸም ክፍተት መኖሩን ጠቁመው፣በተለይም የእንቅስቃሴ ጉዳት ያለባቸው በርካታ ዜጎች በሰው ሰራሽ አካል ድጋፍ እጥረት ከቤት መውጣት አቅቷቸው በጨለማ ውስጥ ለመኖር መገደዳቸውን ጠቁመዋል።
የሴቶችና ወጣቶች ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ የአካል ጉዳተኞችን ችግር የሚቀርፉ የፖሊሲ ሀሳቦች ከማመንጨት ባለፈ፣ የተደነገጉ አለም አቀፍ ስምምነቶች በክልሉ ተፈፃሚ እንዲሆኑ እየሰራ እንደሚገኝ በመግለጽ፣ተቋማዊ አሰራርን በማጠናከር፣ልዩ አገልግሎቶችን በማስፋፋት፣አካል ጉዳተኞችን በማብቃት ላይ ትኩረት መደረጉን ተናግረዋል።
ሰክሰስ ፕላስ ለ100 ወገኖች የዊልቸር ድጋፍ በማድረጉ፣የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር ከማንም በላይ አካል ጉዳተኞችን ተጠጠቃሚ በማድረጉ ምስጋና አቅርበው፣የዕለቱ ዕድለኞችም የተሰጣቸውን በአግባቡ ሊጠቀሙበት እንደሚገባ መልዕክት አስተላልፈዋል።
በተለያየ ምክንያት የመንቀሳቀስ ጉዳት እንዳጋጠማቸው ድጋፍ የተደረገላቸው ወገኖች በሰጡት አስተያየት ተናግረዋል።በተደረገላቸው ድጋፍ መደሰታቸውን በመግለጽ፣ከዚህ በኋላ የተሰጣቸውን ዊልቸር ተጠቅመው እንደሚንቀሳቀሱ አመልክተዋል።