18/02/2026
የፕላስቲክ ከረጢቶች /ፌስታል ምርቶችን/ መጠቀም የሚያስከትለው ተጠያቂነት
መግቢያ
በኢትዮጵያ የሕዝብ ቁጥርና የከተሞች እድገትን ተከትሎ ባልተገባ መልኩ የሚጣሉ ደረቅ ቆሻሻዎች ማለትም እንደ ፕላስቲክ/ፌስታል/ ያሉት የአካባቢን ስነ ምህዳር በመበከል፣ የውሃ መስመሮችን በመዝጋት፣ ለረጅም ጊዜ ሳይበሰብሱ በመከማቸት ለተላላፊ በሽታዎች መስፋፋት መንስኤ ሲሆኑ ይታያሉ። በተለይ የፕላስቲክ ምርቶች ሳይበሰብሱ ለብዙ ዓመታት በመቆየት የስነ ምህዳር ጠንቅ እንደሆኑ ሳይንሳዊ ምርምሮች ያወሳሉ። በመሆኑም ኢትዮጵያ ከሕገ መንግስቱ ጀምሮ የአካባቢ እንክብካቤን የተመለከቱ ሕጎች ያሏት ሲሆን የሁሉም ሕግ የበላይ ከሆነው ሕገ መንግስታችን ብንነሳ በአንቀጽ 44/1/ ስር ሁሉም ሰዎች ንጹህና ጤናማ በሆነ አካባቢ የመኖር መብት እንዳላቸው ይደነግጋል። በዚሁ ሕገ መንግስት አንቀጽ 92 ስር መንግስት ሁሉም ኢትዮጵያዊ ንጹህና ጤናማ በሆነ አካባቢ እንዲኖረው ጥረት የማድረግ ኃላፊነት እንዳለበት ተደንግጓል። በዚህ መነሻነት የወንጀል ሕጉ እና ሌሎች አዋጆች ለምሳሌ የደረቅ ቆሻሻ አያያዝ አዋጅ ቁጥር 513/1999 ተግባራዊ ሲደረግ የቆየ ሲሆን ከጉዳቱ መጠን እና በኢትዮጵያ ካለው የስርጭት አድማስ አንጻር በተለይ የፕላስቲክ ምርትን አስመልክቶ የሕግ ማእቀፍ መዘርጋት አስፈላጊ ሆኗል። ስለሆነም የፕላስቲክ ምርቶችን መጠቀም የሚከለክል አለፍ ሲልም የወንጀል ቅጣትን የሚደነግግ አዋጅ ቁጥር 1383/2017 ወጥቶ በስራ ላይ ውሏል። በዚህ አጭር ጽሁፍም እነዚህን ክልከላዎች እና የሚያስከትሉትን ተጠያቂነት እንዳስሳለን።
የፕላስቲክ ምርት/ፌስታል/ ምንነት
በአዋጅ ቁጥር 1383/2017 አንቀጽ 2/9/ ስር እንደተደነገገው ፕላስቲክ ማለት በዋናነት ከፔትሮኬሚካል የተሰራ፣ ለስላሳና የማይበሰብስ የፖሊመር ይዘት ያለው ምርት እንደሆነ ትርጉም ተሰጥቶታል። ይህም በተለምዶ ፌስታል ተብሎ የሚጠራውን ምርት የሚያመለክት ነው። በዚሁ አዋጅ አንቀጽ 2/10/ ስር እንደሰፈረው የፕላስቲክ ከረጢት ማለት አነስተኛ ጥግግት ያለው፣ በቀላሉ በስብሶ ከአፈር ጋር የማይዋሃድ እና ሌሎች ምርቶችን ለመያዝ የሚያገለግል ፕላስቲክ እንደሆነ ተመላክቷል። ይኸውም የፌስታል ከረጢትን የሚያመለክት ነው።
ከዚህ ጋር ተያይዞ የሚነሳው የስስ ፌስታል ጉዳይ ሲሆን በአዋጁ አንቀጽ 2/11/ ስር አንድ ጊዜ ጥቅም ላይ የሚውል ፕላስቲክ የሚል ስያሜ የተሰጠው ሲሆን ይኸውም መልሶ ጥቅም ላይ የማይውል ወይም መልሶ ኡደት የማይደረግ እና አንድ ጊዜ ብቻ ጥቅም ላይ ውሎ ቀጥታ የሚወገድ የፕላስቲክ ምርት እንደሆነ በዚሁ ድንጋጌ ተገልጿል።
በፕላስቲክ ምርት/ፌስታል/ ላይ የተደረገው ክልከላ
ለአንድ ጊዜ ጥቅም ላይ የሚውል ፕላስቲክ/ በተለምዶ ስስ ፌስታልን/
• መጠቀም ወይም ለመጠቀም ይዞ መገኘት፣
• ማምረት፣ ወደ አገር ውስጥ ማስገባት፣ ለገበያ ማቅረብ፣ መሸጥ፣ ለንግድ ዓላማ ማከማቸት ወይም ይዞ መገኘት ክልክል መሆኑን እና አስተዳደራዊ ተጠያቂነትን እንደሚያስከትል በአዋጁ አንቀጽ 24/9/ ስር ተደንግጓል። ሆኖም ግን የፌዴራል አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ለአንድ ጊዜ ብቻ ጥቅም ላይ የሚውሉ ፕላስቲኮች እንዲመረቱ ወይም ጥቅም ላይ እንዲውሉ በልዩ ሁኔታ በመመሪያ ሊፈቅድ እንደሚችል በአዋጁ አንቀጽ 14 ስር ተደንግጓል።
የወንጀል ተጠያቂነት
በአዋጁ አንቀጽ 25 ስር ክልከላዎችን መተላለፍ የወንጀል ተጠያቂነትን እንደሚያስከትል ተደንግጓል። ይኸውም፡-
• ማንኛውም ሰው የፕላስቲክ ከረጢት/የፌስታል ከረጢት/ ከተጠቀመ ወይም ለመጠቀም ይዞ ከተገኘ ከ2,000/ሁለት ሺህ ብር/ በማያንስና ከ5,000/አምስት ሺህ ብር/ በማይበልጥ የገንዘብ መቀጮ ይቀጣል።
• ማንኛውም ሰው የፕላስቲክ ከረጢት/የፌስታል ከረጢት/ ካመረተ ወይም ወደ አገር ውስጥ ካስገባ፣ ለገበያ ካቀረበ ወይም ከሸጠ፣ ለንግድ ዓላማ ካከማቸ ወይም ይዞ ከተገኘ ከ50,000/ሀምሳ ሺህ ብር/ በማያንስና ከ200,000/ሁለት መቶ ሺህ ብር/ በማይበልጥ የገንዘብ መቀጮ እና ከ5/አምስት አመት/ በማይበልጥ ጽኑ እስራት ይቀጣል፡፡ ይኸውም የፕላስቲክ ከረጢት/ፌስታል/ ከግለሰባዊ አገልግሎት ውጪ ለንግድ ዓላማ ጥቅም ላይ ሲውል ከገንዘብ ቅጣት በተደራቢነት በእስራት እንደሚያስቀጣ መረዳት ይቻላል።
• ከላይ የተመለከቱትን የወንጀል ድርጊቶች የፈጸመው ሕጋዊ ሰውነት ያለው ድርጅት ከሆነ የገንዘብ ቅጣቱ ከላይ የተገለጸውን 3/ሶስት እጥፍ/ ይሆናል።
ማጠቃለያ
የፕላስቲክ ምርቶች/ፌስታሎች/ የአካባቢ ስነ ምህዳር ብሎም የሰዎች እና የእንስሳት ጤና ጠንቅ ናቸው። ይህንን ጉልህ የሆነ የጤና ጠንቅ ለመከላከል በምርቶቹ ላይ ክልከላ እና ተጠያቂነትን የሚደነግግ ሕግ ማውጣት አንዱ ዘዴ ነው። ኢትዮጵያም ፌስታል መጠቀምን የሚከለከል ህግ አውጥታ ተግባራዊ አድርጋለች። ስለሆነም ህብረተሰቡ እነዚህን ለጤና ጠንቅ የሆኑ ምርቶችን ባለመጠቀም አጠቃላይ የስነ ምህዳር ጤንነትን በማስጠበቅ ሂደት የበኩሉን ሊወጣ ይገባል።
በንቃተ ሕግ፣ ትምህር የተዘጋጀ
https://www.facebook.com/share/1HShiqKeRQ/?mibextid=wwXIfr
For Law Justice Equity!