08/08/2026
በዛላ ወረዳ የባዮ–ዝማ ማዕከል ቀበሌዎችን የሚያስተሳስር የገጠር መንገድ ግንባታ በይፋ ተጀመረ
ነሐሴ 1/2018 ዓ.ም.
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል መንገዶች ባለሥልጣን የ2019 በጀት ዓመት ከሚያስፈጽማቸው የመንገድ ልማት ፕሮጀክቶች መካከል የሻምባራ–ዝማ–የላ ሻቤ መንገድ አካል የሆነው፣ የባዮ–ዝማ ማዕከል ቀበሌዎችን በማኅበረሰብ ተሳትፎ የሚያስተሳስር የገጠር መንገድ ግንባታ በይፋ ተጀምሯል።
ይህ መንገድ ዛላ ወረዳን ከዑባ ደብረ ፀሐይ ወረዳ ጋር በሚያገናኘው ዋና መንገድ ላይ የሚገኝ ሲሆን፣ በአካባቢው የመጓጓዣ አገልግሎትን በማሻሻል ለኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ እንቅስቃሴዎች ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክት ተገልጿል።
በመንገዱ የማስጀመሪያ ሥነ ሥርዓት ላይ የተገኙት የጎፋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ኢንጂነር ዳግማዊ አየለ እንደተናገሩት፣ መንግሥት ለመንገድ መሠረተ ልማት ልዩ ትኩረት በመስጠት ከከተማ እስከ ገጠር የሚደርሱ መንገዶችን በስፋት እየገነባ ነው ብለዋል።
በጎፋ ዞንም ወረዳዎችን ከወረዳዎች፣ ቀበሌዎችን ከቀበሌዎች የሚያገናኙ የገጠር መንገዶች በቅድሚያ እየተገነቡ መሆናቸውን ጠቁመው፣ የመንገድ ተደራሽነትን ማስፋት የህዝቡን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት እንደሚያሳድግ ገልጸዋል።
ኢንጂነር ዳግማዊ አክለውም፣ በዛላ ወረዳ የመንገድ ተደራሽነት የህዝቡ የዘመናት ጥያቄ እንደነበር ጠቅሰው፣ የዛሬው የመንገድ ግንባታ ጅማሮ ለዚህ ጥያቄ የተሰጠ ተግባራዊ ምላሽ መሆኑን ገልጸዋል።
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል መንገዶች ባለሥልጣን የሣውላ ዲስትሪክት ሥራ አስኪያጅ ኢንጂነር ድምሬ ድበታ በበኩላቸው፣ የመንገዱ ግንባታ ከተማውን፣ ወረዳውንና በርካታ ቀበሌዎችን የሚያስተሳስር መሆኑን ገልጸው፣ በፕሮጀክቱ ውስጥ በደላሌ ወንዝ ላይ 16 ሜትር ርዝመት ያለው ድልድይ እንደሚገነባ ገልጸዋል።
የዛላ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አንበስ ሀነና በበኩላቸው፣ የመንገዱ ግንባታ ለህዝቡ የዘመናት ጥያቄ ምላሽ መሆኑን ገልጸው፣ ፕሮጀክቱን በማኅበረሰቡ ንቁ ተሳትፎ በታቀደለት ጊዜ ለማጠናቀቅ ሙሉ ትብብር እንደሚያደርጉ ቃል ገብተዋል።
በፕሮግራሙ ያነጋገርናቸው የአካባቢ ነዋሪዎች የመንገዱ መጀመር እንዳስደሰታቸው ተናግረው የዘመናት ጥያቄያቸው ተመልሶ ለህክምናም ይሁን ለምርት ሽያጭ ተስፋ የሚሰጥ መሆኑን ተናግረዋል።
በማስጀመሪያ ሥነ ሥርዓቱ የጎፋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ኢንጂነር ዳግማዊ አየለ፣ የጎፋ ዞን የመንግሥት ዋና ተጠሪ አቶ ጋሻያለው ገላ፣ የጎፋ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አቶ ምናሴ ኤልያስ፣የሣውላ ዲስትሪክት ሥራ አስኪያጅ ኢንጂነር ድምሬ ድበታ፣ የዛላ ወረዳ አመራሮች፣ የተለያዩ ተቋማት ኃላፊዎች፣ የሀገር ሽማግሌዎችና የአካባቢው ማህበረሰብ በተገኙበት የመንገዱ ግንባታ በይፋ ተጀምሯል።