10/06/2026
በድሬደዋ አስተዳደር የተዘረጋው የማይንቀሳቀስ ንብረት ግመታና ግብይት ስርዓት የዘርፉን አገልግሎት ለማቀላጠፍና የገቢ አሰባሰብን ለማጠናከር ከፍተኛ አስተዋፅኦ እያበረከተ መሆኑ ተገለጸ።
በድሬደዋ አስተዳደር መሬት ልማትና ማኔጅመንት ቢሮ የማይንቀሳቀስ ንብረት ግመታና ግብይት አገልግሎት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ መሃመድ ጌዲ እንደገለጹት በድሬደዋ የተዘረጋው የግምት ስርዓት በሀገር አቀፍ የተሞክሮ ማዕከል ሆኖ እየተጠቀሰ ይገኛል።
ዳይሬክተሩ እንደገለጹት የንብረት ግመታ ስርዓቱ ራሱን የቻለ መዋቅር እንዲኖረው በመደረጉ የተገልጋዮችን ፍላጎት በተሻለ ሁኔታ ማሟላት እና ከዘርፉ የሚገኘውን ገቢ ማሳደግ ተችሏል።
ባለፉት አምስት ዓመታትም ወደ 77 ሺህ የሚጠጉ ደንበኞችና ባለድርሻ አካላት ለካሳ፣ ለስም ዝውውር፣ ለግብር እና ለፍርድ ቤት ትዕዛዝ የግምት አገልግሎቶች ተሰጥቷል።
የግብር አሰባሰብ ስርዓቱን ይበልጥ ቀልጣፋና ውጤታማ ለማድረግ በአራት ወረዳዎች የብዝሃ ግመታ (Mass Valuation) ስራ መከናወኑ ተገልጿል።
በተጨማሪም ከግምት ስራዎች ጋር በተያያዘ የሚስተዋሉ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመቅረፍ ከእጅ ንክኪ በማላቀቅ በሲስተም አገልግሎት እንዲሰጥ መደረጉ ተጠቅሷል።
እንዲሁም ከ10 ዓመታት በላይ ያልተሻሻለው የነባር ይዞታዎች የኪራይ ተመን እንዲሻሻል መደረጉን እና ለ7 ዓመታት ሳይሻሻል የቆየው የጋራ መኖሪያ ቤቶች የግምት ዋጋም በወቅታዊ የገበያ ዋጋ መሠረት እንዲሻሻል ተደርጓል። በዚህም በቁርጥ ዋጋ ስሌት የተመሰረተ ዘመናዊ የግምት ስርዓት ተዘርግቷል።
በተጨማሪም የቦታ ደረጃና የሊዝ መነሻ ዋጋ ወቅታዊ በመደረጋቸው እና ልዩ ባህሪ ያላቸው ንብረቶች ላይ የልየታና የግምት ጥናቶች በመካሄዳቸው ከመሬት የሚሰበሰበውን ገቢ በከፍተኛ ደረጃ ማሳደግ መቻሉን አቶ መሃመድ ጌዲ ገልጸዋል።
ግንቦት 16 ቀን 2018 ዓ.ም።