05/04/2026
በሙስና ወንጀል የተከሰሱ ግለሰቦች በፅኑ እስራትና በገንዘብ ተቀጡ
*** **** ***** ******
(ጋም.ሥ.ፀ.ሙ.ኮ መጋቢት 27/2018 ዓ.ም) በአማራ ክልል በደቡብ ወሎ ዞን ባለፉት ዘጠኝ ወራት በተከናወነ ሰፊ የሙስና ወንጀል ምርመራ በስልጣን አላግባብ መገልገል እና በእምነት ማጉደል ወንጀል የተከሰሱ ግለሰቦች በከባድ ፅኑ እስራትና በገንዘብ መቀጮ እንዲቀጡ መወሰኑን የዞኑ ፖሊስ መምሪያ አስታወቀ።
የመምሪያው አዛዥ ኮማንደር አሳምነው ሙላት እንደገለፁት ፖሊስ በዞኑ የመንግስትንና የህዝብን ሀብት ለግል ጥቅማቸው ባዋሉ አመራሮችና ሰራተኞች ላይ ትኩረት በማድረግ ባከናወነው ጥብቅ የምርመራ ስራ ውጤት ተመዝግቧል።
የኩታበር ወረዳ ማዘጋጃ ቤት የስራ ኃላፊዎች በስልጣን አላግባብ መገልገል የሙስና ወንጀል ተከሰው የካቲት 27 ቀን 2018 ዓ.ም በዋለው ችሎት ከፍተኛ ቅጣት ተጥሎባቸዋል፦
በዚህም፣ አቶ አሊ ከበደ የቀድሞ የማዘጋጃ ቤት ኃላፊ በ13 ዓመት ፅኑ እስራት እና በ1,000 ብር ቅጣት፣ አቶ ሙህድን አሊ ምክትል ኃላፊ በ4 ዓመት እስራት እና በ2,000 ብር ቅጣት፣ አቶ አቦል አሸብር በ4 ዓመት ከ5 ወር እስራትና በ2,000 ብር ቅጣት እና አቶ ሙሉጌታ በሪሁን በ5 ዓመት እስራትና በ2,000 ብር ቅጣት ተላልፎባቸዋል።
በተጨማሪም አቶ ኑረዲን መሀመድ ጨምሮ አምስት የማናጅመንት አባላት በሌሉበት በተካሄደ ክርክር እያንዳንዳቸው በ5 ዓመት ፅኑ እስራትና በ5,000 ብር ቅጣት ተወስኖባቸዋል። ተከሳሾቹ በአሁኑ ወቅት በቁጥጥር ስር ውለው በደሴ ማረሚያ ቤት እንደሚገኙ አዛዡ አረጋግጠዋል።
በተመሳሳይ የምርመራ መዝገብ ኢ/ር ምህረት አያሌው የአድማ መከላከል ሻምበል አዛዥ የነበረ በከባድ የእምነት ማጉደልና በስልጣን አላግባብ መገልገል ሙስና ወንጀል ተከሶ በሐምሌ 7 ቀን 2017 ዓ.ም በዋለው ችሎት የ9 ዓመት ፅኑ እስራት ተፈርዶበታል።
አቶ እንድሪስ ይመር አሊ የመነሀሪያ የዕለት ገንዘብ ሰብሳቢ የነበረ ከ950 ሺህ ብር በላይ በኦዲት በመጥፋቱ በ5 ዓመት ከ10 ወር ፅኑ እስራት እና በ5,000 ብር ቅጣት ተቀጥቷል። አቶ ሰይድ ሀሰን ሁሴን የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሰራተኛ የነበረ የደንበኞችን 5 ሚሊዮን 150 ሺህ ብር በመውሰዱ በ5 ዓመት ከ4 ወር ፅኑ እስራት እንዲቀጣ ተፈርዶበታል።
ኮማንደር አሳምነው ሙላት አክለውም ፖሊስ ሙስናን ለመከላከልና ተጠያቂነትን ለማስፈን እያካሄደ ያለውን ጥብቅ ክትትልና ምርመራ ተጠናክሮ ይቀጥላል ማለታቸውን የክልሉ ፖሊስ በፌስቡክ ገጹ መረጃውን አጋርቷል።
ትውልድን በሥነምግባር፤ ተቋምን በአሰራር!
#የነፃ ጥቆማ የስልክ መስመር 8623 https://www.facebook.com/profile.php?id=6156999 #5963416&mibextid=ZbWKwL