24/05/2026
“ግብር ከፋዩ 'በኔ ታማኝነት ሀገር እየተገነባ ነው' በሚል ሀገርን የመውደድ እሳቤ ግብሩን በታማኝነት እና በወቅቱ የመክፈል ባህሉን ሊያሳድግ ይገባል”
- ወ/ሮ ዓለምነሽ ደመቀ (የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የገቢዎች ቢሮ ኃላፊ)
ግንቦት 16/2018 ዓ.ም (የገቢዎች ሚኒስቴር)
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የገቢዎች ቢሮ በክልሉ ያለውን ትልቅ የገቢ አቅም አሟጥጦ ለመጠቀም የሚያስችሉ ስራዎችን እያከናወነ እንደሚገኝ የቢሮው ኃላፊ ወ/ሮ ዓለምነሽ ደመቀ ገለጹ።
ቢሮው የተለያዩ የሪፎርም ስራዎችን ማከናወኑን የገለጹት የቢሮ ኃላፊዋ የታክስ ሕግ ማሻሻያዎችን በማድረግ እና የሰው ኃይል የመፈጸም አቅምን ለማሳደግ የሰው ኃይል የሪፎርም ስራዎችን የማከናወን ተግባር ቀዳሚው እንደነበር ተናግረዋል።
በክልሉ ባሉ 138 የታክስ ማእከላትን ጨምሮ የታክስ አሰባሰብ ስርዓቱን በቴክኖሎጂ የማስደገፍ እና የማዘመን ሰፊ ስራ መሰራቱን ገልፀው በዚህም ግብር ከፋዩ ያለበት ቦታ በመሆን በቀላሉ ግብሩን እንዲከፍል እና ገቢ የመሰብሰብ አቅም እንዲያድግ ያስቻለ ነው ብለዋል።
ክልሉ እንደአዲስ ከተዋቀረ በኋላ ባሉት ዓመታት የገቢ አፈጻጸሙ እያደገ መምጣቱን የገለጹት ወ/ሮ ዓለምነሽ በ2016 በጀት ዓመት 13 ቢሊየን የነበረው የገቢ አቅም በ2018 በጀት ዓመት 32.4 ቢሊየን ለመሰብሰብ በማቀድ በአስር ወራት ውስጥ ብቻ 25.5 ቢሊየን መሰብሰብ መቻሉን ገልጸዋል። አፈጻጸሙም ከ2017 በጀት ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ11 ቢሊየን ብር ብልጫ እንዳለውም አሳውቀዋል።
የታክስ ሕግ ማስከበርን ጋር ተያይዞ ክልሉ ቅድሚያ የሚሰጠው የግብር ከፋዩን የታክስ ግንዛቤ ለማስጨበጥ ስራ መሆኑን የጠቀሱት ኃላፊዋ ነገር ግን ከዚህ አልፈው የታክስ ሕግ ጥሰትን በሚፈጽሙት ላይ ሕግ የማስከበር ስራዎችን እያከናወነ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
የክልሉ ገቢ የመሰብሰብ አቅም እንዲያድግ የገቢዎች ሚኒስቴር የታክስ ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ልማት ስራዎች እንዲሁም የሰው ኃይል አቅም ማጎልበት ላይ ድጋፍ እያደረገ እንደሆነ ገልጸው በቀጣይም የበለጠ ተቀራርበው እንደሚሰሩ ያላቸውን እምነት ገልጸዋል።
ወ/ሮ ዓለምነሽ ለግብር ከፋዩ ባስተላለፉት መልእክትም ግብር ከፋዩ በኔ ታማኝነት ሀገር እየተገነባ ነው በሚል ሀገርን የመውደድ እሳቤ እንዲንቀሳቀስ እና ታክስን ማጭበርበር እራስንም፤ ሀገርንም የሚጎዳ ተግባር መሆኑን በመገንዘብ ግብርን በታማኝነት እና በወቅቱ በመክፈል ተቋሙ ገቢን በተገቢው ልክ ሰብስቦ ለሀገር ልማት ለማዋል ከሚያደርገው ጥረት ጎን እንዲሰለፍ ጥሪ አቅርበዋል።
ፎቶ:- የትናየት እንዳያፍሩ