04/09/2026
የጠገዴ ወረዳ በጎ አድራጎት ማህበር ለክረምት በጎ ፈቃድ ተግባር የሚውሉ ቁሳቁሶችን አስረከበ
📍 ጠገዴ | ነሐሴ 28/2018 ዓ.ም
በአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ወልቃይት ጠገዴ ሰቲት ሑመራ ዞን የጠገዴ ወረዳ በጎ አድራጎት ማህበር፣ በተጠናከረ መንገድ እየተካሄደ ለሚገኘው የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት የሚውሉ ቁሳቁሶችን አስረክቧል።
ማህበሩ ከበጎ አድራጊ ግለሰቦችና ድርጅቶች በሰበሰበው ሀብት የ42,090 ብር ግምት ያላቸው 45 ቆርቆሮዎች፣ 16 ደርዘን ደብተሮችና 3 ፓኮ እስክርቢቶዎችን ለጠገዴ ወረዳ ሴቶችና ወጣቶች ማህበራዊ ጽ/ቤት እና ለወረዳው ትምህርት ጽ/ቤት አስረክቧል።
“በጎነት ለኢትዮጵያ ከፍታ” በሚል መሪ ቃል ለተጀመረው የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት የተደረገው ይህ ድጋፍ፣ አቅም ለሌላቸው ተማሪዎች የመማሪያ ቁሳቁስ ለማቅረብ እንዲሁም ለአቅመ ደካሞችና አረጋውያን መኖሪያ ቤቶችን ለመገንባትና ያረጁ ቤቶችን ለመጠገን እንደሚውል ተገልጿል።
በጎ ፈቃድ አገልግሎት ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮችን ከመፍታት ባለፈ የእርስ በርስ ትስስርንና የመረዳዳት ባህልን የሚያጠናክር መልካም ተግባር በመሆኑ፣ ሌሎችም በመሳተፍ የወገን ደራሽነታቸውን እንዲያሳዩ ጥሪ ቀርቧል።
ምንጭ፡ ጠገዴ ወረዳ ኮሙኒኬሽን