05/06/2026
በሰቆጣ ቃል ኪዳን ፕሮግራም በተመረጡ ትምህርት ቤቶች በጤናና በስርዓተ-ምግብ ዙሪያ ስልጠና ተሰጠ።
ሆሣዕና፣ግንቦት28/2018ዓ.ም(ሌሞ ኮሚዩኒኬሽን)
በሀድያ ዞን ሌሞ ወረዳ ትምህርት ጽ/ቤት በሰቆጣ ቃል ኪዳን ፕሮግራም ለሁለት አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ርዕሳነ መምህራን፣ለስርዓት-ምግብ ፎካል እና ለተማሪዎች በስርዓተ-ምግብ አዘገጃጀት ዙሪያ ስልጠና ተሰጠ፡፡
በዕለቱም ስልጠናውን የሰጡት በወረዳው ትምህርት ጽ/ቤት የሰቆጣ ቃል ኪዳን ፕሮጀክት አስተባባሪ አቶ ዳንኤል ሙሉጌታ ስለ ምግብ ምንነት፣ አስፈላጊነት እና ምድቦች ሰፊ ስልጠና በሰጡበት ወቅት እንዳሉት የሰቆጣ ቃል ኪዳን ፕሮግራም የስርዓተ-ምግብ ችግርን ለመፍታት የሚሠራ መሆኑን በመግለጽ የህፃናት የመቀንጨር አስከፊነት እንደ ሃገር የሚያደረሰውን አሉታዊ ተፅዕኖ በውል በመረዳት የፕሮግራሙን ተግባር ዳር ለማድረስና ጤናማ ትውልድ ለመፍጠር ሁላችንም መረባረብ ይገባናል ብለዋል፡፡
አቶ ዳንኤል አያይዘውም ስርዓተ-ምግብ ላይ መስራት ሃገርን መገንባት እና ትውልድን ማስቀጠል በመሆኑ በተወሰደው ስልጠና ልክ ተግባሩም በትኩረት መሰራት እንዳለበት በማሳሰብ በቀጣይ ቅንጅታዊ አሰራሮችን በማጠናከር የፕሮግራሙን ዓላማ ከግብ ማድረስ አለብን ብለዋል፡፡
በስልጠናው ላይ የተገኙት የታችኛው አምቢቾና የሹሩሞ ዱባንቾ አንደኛ ደረጃ ት/ቤቶች ርዕሳነ መምህራን በሰጡት አስተያየት ስልጠናው ትምህርት ቤቶች የጓሮ አትክልት ሰርቶ ማሳያ ለመስራት ከቦታ መረጣ ጀምሮ የጓሮ አትክልቶችን እንዲሁም ሌሎች ተግባራትን አቀናጅተው እንዴት መምራት እንዳለባቸው ግንዛቤ እንዳገኙ ገልጸዋል፡፡
ዘጋቢ:-ዕፁብ አዳነ