21/06/2026
የአጣዬ ከተማ የኮሪደር ስራ የእግረኛ መንገድ የቴራዞ ማንጠፍ ተጀመረ፤
በአጣዬ ከተማ አስተዳደር እየተከናወነ ባለው የመጀመሪያ ዙር የኮሪደር ልማት ግንባታ ፕሮጀክት የእግረኛ መንገድ የቴራዞን ማንጠፍ ስራ በዛሬው ዕለት በይፋ ተጀምሯል።
በቴራዞ ማንጠፍ ስራው ማስጀመሪያ ሥነ-ስርዓት ላይ የአጣዬ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ተመስገን ተስፋ፣ የሰንበቴ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ኑረዲን አህመድ፣ የአጣዬ ከተማ አስተዳደር ብልፅግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ከድር እንድሪስ እንዲሁም ሌሎች የከተማው አመራሮች ተገኝተዋል።
በዚሁ ወቅት የአጣዬ ከተማ መሰረተ ልማት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ኢንጅነር አበቡ ማሞ እንደገለፁት፦ የከተማው ኮሪደር ልማት ግንባታ በተያዘለት የጊዜ ሰሌዳ መሰረት እየተከናወነ ሲሆን እና የቴራዞን ማንጠፍ ስራ መጀመሩ የፕሮጀክቱ አንዱ ወሳኝ ምዕራፍ መሆኑን ገልጸዋል።
በሌላ በኩል የአጣዬ ከተማ ኮንስትራክሽን ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ኢንጅነር እንድሪስ የሱፍ እንደተናገሩት፣ በመጀመሪያው ዙር የኮሪደር ልማት ግንባታ አብዛኛው ስራ ተጠናቆ በአሁኑ ወቅት የቴራዞ ማንጠፍ ስራ መጀመሩ የፕሮጀክቱን እድገት የሚያሳይ መሆኑን ገልጸዋል።
ኃላፊው አክለውም በቀጣይ የአረንጓዴ ቦታዎች ልማትና የፖል መብራት ተከላ ስራዎች እንደሚከናወኑ ገልጸው፣ ቀሪ ስራዎችም በቅርቡ ተጠናቀው ፕሮጀክቱ ሙሉ በሙሉ ተጠናቆ ወደ አገልግሎት እንደሚገባ አስታውቀዋል።
በመጨረሻም የኮሪደር ልማት ፕሮጀክቱ የከተማውን ውበት፣ የእግረኞች ምቹነት እና የትራፊክ ደህንነት በማሻሻል ለነዋሪዎች እና ለእንግዶች የተሻለ የከተማ አካባቢ ለመፍጠር እንደሚያግዝ ተገልጿል።