19/01/2026
ከአንድ የፌስቡክ ጋደኛዬ ገጽ ያገኘኋትን የተቋጠረች ጽሁፍ እነሆ አጋራኋችሁ!
የሴኔጋል ተጫዋቾች ተበድለናል ..."ሜዳውን ለቀን እንወጣለን" .. ብለው ፎከሩ። ፕሮፌሽናልነታቸው አውልቀው ጥለው እንደ ሰፈር ጎረምሳ በብሶት ተውጠው ወደ መልበሻ ቤት ማምራት ጀመሩ። እርግጥ ነው የተሰጠባቸው ፔናሊቲ አጨቃጫቂ ከመሆኑም ሌላ ለአዘጋጇ ሀገር የተሰራ ፌበር ይመስል ነበር።
በዚህ ሁሉ ግርግር ውስጥ ግን የአንድ ተጫዋች ትግስት ፣ ፕሮፌሽናሊዝም ፣ እርጋታና ፣ ምክር የሴኔጋል ተጫዋቾችን ስሜት አረገበ። ሜዳውን ለቀው መውጣታቸው ዋንጫውን ለሞሮኮ ፎርፌ እንዲሰጥ ከማድረግ በተጨማሪ ሴኔጋልን ለከፍተኛ ቅጣት እንደሚያበቃት የተረጋገጠ ነበር።
ይህ እንዳይሆን ተጫዋቾችን አረጋግቶ ወደ ሜዳው መለሳቸው። ፔናሊቲው እንዲመታ አሳመናቸው። የስፖርታዊ ጨዋነት መርህ ፣ የእግር ኳስ ተመልካቾች ክብር ፣ የአፍሪካ እግር ኳስ መድረክ ዝና ፣ የሴኔጋላዊያን ጨዋነት እንዳይጣስ አደረገ።
በእሱ ውሳኔ እየሆነ የነበረው በቅፅበት ተቀየር። ሞሮኮ የተሰጣትን ፔናሊቲ ሳተችው። በተስፋ መቁረጥ ውስጥ ገብተው የነበሩ የሴኔጋል ተጫዋቾች ተነቃቁ .... በተጨማሪ 30 ደቂቃ ጎል አስቆጥረው ከእጃቸው ያፈተለከውን ዋንጫ ዳግመኛ በማሳካት የሴኔጋልን ክብር አረጋገጡ ...
በአፍሪካ ዋንጫ ታሪክ እጅግ አጨቃጫቂው ፣ በድራማ የተሞላው ክስተት ፣ ምንአልባት የሴኔጋል ተጫዋቾች ሜዳውን ለቀው ቢወጡ ኖሮ በፎርፌ ለሞሮኮ ሊወሰን የነበረውን ጥቁር ታሪክ ሻረው።
ሳዲዮ ማኔ በሜዳ ላይ ለሀገሩ ክብር ሁሉንም ነገር ሳይሰሰት ሰጠ ... ከሜዳው ባሻገር ደግሞ በስፖርታዊ ጨዋነት ተግባሩ ዳግመኛ ነገሰ። ጥቁር ዳመና አጥልቶበት የነበረውን ጨዋታ በወጋገን የፀሀይ ነፀብራቅ ለወጠ ...
በእርግጥም እንደ ሳዲዮ ማኔ ያሉ በስነምግባራቸው የላቁ ፣ በስለው የረጉ ፣ የፕሮፌሽናልነት መለኪያ የሆኑ ፣ ከስሜት ይልቅ አስተዋይነት የታደሉ ፣ በክብር የደመቁ ፣ መልካም አርአያነት የተላበሱ ተጫዋቾች ባይኖሩ ኖሮ የእግር ኳስ መድረክ በዚህ ልክ ፈፅሞ አይደምቅም ነበር !!