09/07/2026
የስልጤ ዞን ፍትህ መምሪያ የ2018 የ12 ወራት እቅድ አፈጻጸም ከባለድርሻ አካላት ጋር በወራቤ ከተማ ገመገመ!
ወራቤ (ሀምሌ 2 /2018 ዓ.ም) — ስልጤ ዞን መንግስት ኮሙኒኬሽን
መምሪያው የዜጎችን መብት ከማስከበር፣ የሕግ የበላይነትን ከማረጋገጥና መልካም አስተዳደርን ከማስፈን አንጻር ያከናወናቸውን ዋና ዋና ተቋማዊ እምርታዎችና ያጋጠሙ ተግዳሮቶችን ከታችኛው መዋቅር ከተገኙ ባለድርሻ አካላትና የህዝብ ክንፍ አባላት ጋር በወራቤ ከተማ በጋራ ገምግሟል።
በግምገማ መድረኩ ላይ እንደተገለጸው፤ መምሪያው በተሻሻለው የፌደራል ሲቪል ሰርቪስ ማሻሻያ ፍኖተ ካርታ መሰረት የሪፎርም መሳሪያዎችን ወደ ተግባር በማስገባት፣ ተቋማዊ የቲም አደረጃጀቶችን በመፍጠርና የአገልግሎት አሰጣጥ ክፍተቶችን በየሳምንቱ በመፈተሽ ተገልጋይ ተኮር እና ፈጣን ምላሽ ሰጪ አሰራርን ማስፈን ችሏል።
በበጀት ዓመቱ የወንጀል ፍትህ አስተዳደሩን ውጤታማ ለማድረግ ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት በተለይም ከፖሊስ ጋር የሦስትዮሽ የመግባቢያ ሰነድ በመፈራረም የተቀናጀ ስራ መሰራቱ ተገልጿል።
በዚህም መሠረት በልዩ ልዩ ወንጀሎች በበጀት ዓመቱ በቀረቡ 1,033 የምርመራ መዛግብት ላይ ዐቃቤ ህግ 100% ውሳኔ በመስጠት የዕቅዱን (99%) በላይ አሳክቷል።
ወደ ፖሊስ ተመላሽ የሚሆኑ መዛግብትን ከ1% በታች ለማድረግ ታቅዶ ወደ 0% ዝቅ በማድረግ አመርቂ ውጤት መመዝገቡም ተገልጿል።
በፍርድ ቤት ክርክር ከተደረገባቸው መዛግብት ውስጥ በመዝገብ 98.03%፣ በተከሳሽ ደግሞ 98.37% የማስቀጣት ስኬት የተመዘገበ ሲሆን፤ በከባድ ወንጀሎች ዘርፍ የማስቀጣት ምጣኔው 100% ደርሷል።
በዓቃቤ ህግ የተጠየቁ የይግባኝ መዛግብት የማሻር ወይም የማሻሻል ምጣኔ በመዝገብም ሆነ በተከሳሽ 100% ሙሉ ስኬት እንደተመዘገበ በሪፖርቱ ቀርቧል።
በበጀት ዓመቱ የፍትህ ሴክተሩ የሙስና እና የታክስ ማጭበርበር ወንጀሎችን በመታገል ረገድ ታሪካዊ የተባለ የሃብት የማስመለስ ስራ ማከነወኑ ተገልጿል።
ለአብነትም:-
-በሙስና ወንጀል፦ በድርድር በተዘጉ 07 መዛግብት ብቻ 9,016,693 (ዘጠኝ ሚሊዮን አስራ ስክስት ሺህ ስድስት መቶ ዘጠና ሦስት) ብር የመንግስትና የህዝብ ሃብት ማዳን ተችሏል።
-በታክስ ማጭበርበር ወንጀል፦ ባልተከፈለ የሰራተኞች የስራ ግብር እና የኦዲት ጉድለት ሳቢያ ተመዝብሮ የነበረ 26,680,011 (ሃያ ስድስት ሚሊዮን ስድስት መቶ ሰማንያ ሺህ አስራ አንድ) ብር 100% ለመንግስት ገቢ ተደርጓል።
-በፍትሃብሔር ዘርፍ፦ በበጀት ዓመቱ ውስጥ በድርድር፣ በክስ ሂደት እና በአፈጻጸም በድምሩ 43,859,145.9 ብር ለመንግስት ገቢ የተደረገ ሲሆን፤ ከከተማና ገጠር መሬት ማስመለስ አንጻርም ከፍተኛ ስኬቶች ተመዝግበዋል።
የሴቶች፣ የህጻናት እና ተጋላጭ ወገኖች መብት ጥበቃ
በሴቶችና ህጻናት ላይ የሚፈጸሙ ጥቃቶችንና ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶችን ለመከላከል ከ11 ሺህ በላይ ለሚሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎች ሰፊ የግንዛቤ ማስጨበጫ ትምህርት ተሰጥቷል።
በተጨማሪም አቅም ለሌላቸው አረጋውያን፣ ሴቶችና አካል ጉዳተኞች ዐቃቤ ህግ የህግ ድጋፍ በመስጠት በፍርድ ቤት 99% የመርታት ምጣኔ አስመዝግቧል።
የመድረኩን ማጠቃለያ የሰጡት የስልጤ ዞን ፍትህ መምሪያ ኃላፊ አቶ ሪድዋን ኑሪ፤ በበጀት ዓመቱ የተመዘገቡት ስኬቶች የሪፎርም መሳሪያዎችን በቁርጠኝነት የመተግበርና የህዝብና የመንግስት ክንፎችን በንቅናቄ የማሳተፍ ውጤት መሆናቸውን ገልጸዋል።
"በበጀት ዓመቱ የተለዩ 11 የመልካም አስተዳደር ችግሮችን መነሻ በማድረግ 81.8% የሚሆኑትን መፍታት መቻሉንም አንስተዋል።
በተለይም የተመዘበረ የመንግስትና የህዝብ ሃብት ማስመለስ፣ በፍትህ ዘርፉ ያለውን ቅንጅታዊ አሰራር ማጠናከርና የወንጀል መዛግብት ደረጃን ለይቶ በማጥራት 100% የስኬት ምጣኔ ማስመዝገብ መቻሉ ትልቅ እምርታ ነው" ያሉት አቶ ሪድዋን፤ ይሁን እንጂ አሁንም ያልተፈቱ የውስጥ ችግሮች መኖራቸውን አልሸሸጉም።
እንደ ተግባርን ያገናዘበ የበጀት ምደባ ማነስ፣ የተሽከርካሪ እጥረት እና እስከ ስር መዋቅር ያሉ ሰራተኞችን አቅም በስልጠና የማሳደግ ውስንነቶች በቀጣይ ልዩ ትኩረት የሚሹ ናቸው ተብሏ።
እነዚህን ክፍተቶች በቀጣዩ የ2019 በጀት ዓመት የውጤት ተኮር (BSC) ዕቅዳችን ውስጥ በማካተት፣ በቁጭትና ከምን ጊዜውም በላቀ ዝግጅት የምንፈታቸው ይሆናል" ብለዋል።
በመጨረሻም፣ በ10 ወረዳዎችና 5 ከተማ አስተዳደሮች የተካሄደውን የድጋፍና ክትትል ቼክ-ሊስት መሠረት በማድረግ ከፍተኛ፣ መካከለኛና ዝቅተኛ አፈጻጸም ያላቸው መዋቅሮች መለየታቸውንና ልዩ ድጋፍ ለሚያስፈልጋቸው ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን በመጠቆም፤ በቀጣይም የዜጎች ቻርተር ስታንዳርድን የጠበቀ ወጥ የፍትህ አገልግሎት በየደረጃው ለማስፈን ሁሉም ባለሙያ በስራ ገበታው ላይ በቁርጠኝነት ሊተጋ እንደሚገባ አቅጣጫ አስቀምጠዋል።