03/09/2026
የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የሴቶች ማህበር ጽ/ቤት በገጠር መሬት አስተዳደርና አጠቃቀም የህግ ማዕቀፎች ላይ የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና እየሰጠ ነው።
ወራቤ፣ ነሃሴ 28/2018 የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የሴቶች ማህበር ጽ/ቤት ከማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ የገጠር መሬት አስተዳደርና አጠቃቀም ኤጀንሲ ጋር በመተባበር በገጠር መሬት አስተዳደርና አጠቃቀም የህግ ማዕቀፎች ላይ ለሴቶች ሴክተርና አደረጃጀት ባለድርሻ አካላት የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና እየተሰጠ ይገኛል።
የስልጠና መድረኩን በይፋ ያስጀመሩት የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የሴቶችና ህጻናት ጉዳይ ቢሮ ኃላፊ ወ/ሮ ዘቢባ መሀመድናስር ከመሬት አጠቃቀም አዋጅ ጋር በተያያዘ አዋጅ ቁጥር 36/2016 የተሰኘ አዲስ አዋጅ መኖሩን አንስተው ከዚያ ጋር ተያይዞ ሰፊ የግንዛቤና የመሬት ሀብት አጠቃቀም ውስንነት እንዳለ ጠቁመዋል።
በክልሉ የተለያዩ አከባቢዎች ፍትሃዊ ያልሆነ በመሬት ገንዘብ ተበድሮ ሙሉውን የመመለስ ልምድ እንደነበር ያመለከቱት ሀላፊዋ በአዲሱ አዋጅ መሬትን አሲዞ የመበደር እና ስራ እድል መፍጠር ላይ የነበረ ክፍተት እንደሚዘጋ አስታውቀዋል።
የሴቶች ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ እየተሰሩ ባሉ ስራዎች ላይ የሚወጡ አዋጆች፣ ደንቦች፣ መመሪያዎችና እቅዶች ሴቶችን ተጠቃሚ ማድረጋቸውን ማረጋገጥ እንደሚገባና ለዚህም መሰል የስልጠና መድረኮች ዘርፈ ብዙ ፋይዳ እንዳላቸው አመላክተዋል።
ለዚህም በቢሮው በኩል አስፈላጊው ድጋፍና ቅንጅታዊ ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ወ/ሮ ዘቢባ አረጋግጠዋል።
የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የሴቶች ማህበር ጽ/ቤት ፕሬዚደንት ወ/ሮ ፎዚያ መሐመድ በበኩላቸው የሴቶች ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊ እንዲሁም ፖለቲካዊ ተሳትፎ፣ ተሳታፊነት እና ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ የሴት አደረጃጀቶች ሚና የጎላ መሆኑን አስታውሰዋል።
የሴቶች ማህበር ጽ/ቤት ከእነዚህ አደረጃጀቶች አንዱ መሆኑን ያነሱት ወ/ሮ ፎዚያ ጽ/ቤቱ ዓላማውን እና ተልዕኮውን ለመወጣት ባለፉ ጊዜያት በየተቋሙ የሚገኙ የሴት አመራሮችን፣ ባለሙያዎችንና ባለድርሻ አካላትን በማሳተፍ ዘርፈ ብዙ ተግባራትን እንዳከናወነ አስረድተዋል።
ከሴቶች ተጠቃሚነት አንጻር ጉድለት ካለባቸው ዘርፎች አንዱ የገጠር መሬት መሆኑን በማስታወስ ሴቶች የመሬት ባለሀብት፣ ባለመብት እና አጠቃቀም አዋጅ ላይ ግንዛቤ ኖሯቸው መሬታቸውን በአግባቡ ሲጠቀሙ በቤተሰብ፣ በኢኮኖሚ እና በማህበረሰብ ደረጃም ትልቅ ለውጥ እንደሚያመጡ አብራርተዋል።
በዚህም የሴቶች የኢኮኖሚ ነፃነታቸው እንደሚጨምር፣ በመሬቱ በማምረት፣ በንግድ እና በሌሎች ምርታማ ሥራዎች በመጠቀም ገቢያቸውን እንደሚያሳድጉ አስታውቀዋል።
በቀጣይ ጊዜያት ጉድለቶችን ታሳቢ ያደረጉ ሥራዎችን በትኩረት በቅንጅት፣ በመተባበርና በኃላፊነት ስሜት እንዲሰራ ሀላፊዋ አሳስበዋል።