02/09/2026
የሀዋሳ ከተማ ምክትል ከንቲባና የንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ኃላፊ አቶ አገና ኔቶ የወላይታ ብሔር ዘመን መለወጫ ጊፋታ በዓል ላይ ለመታደም ከወላይታ ዞን አስተዳደር የተላከላቸውን ጥሪ ተቀብለዋል
ወላይታ ሶዶ | ነሐሴ 27 ቀን 2018 ዓ.ም
የወላይታ ብሔር ዘመን መለወጫ የጊፋታ በዓልን ምክንያት በማድረግ የወላይታ ሕዝብ ተወካዮች ከሀዋሳ ከተማ አስተዳደር የሥራ ኃላፊዎች ጋር በዓሉን በጋራ ለማክበር ጥሪ አቀረቡ።
በመርሃ-ግብሩ የከተማዋ ምክር ቤት አባላት፣ ከፍተኛ የመንግሥት ሥራ ኃላፊዎች እና የሀገር ሽማግሌዎች ተገኝተዋል። የሲዳማና የወላይታ ሕዝቦች ከጥንት ጀምሮ የኖረ ጥልቅ ታሪካዊ ትስስር፣ አብሮነት እና የቆዩ እሴቶች ባለቤቶች መሆናቸው ተመላክቷል፤ ይህን ታሪክ ተሻጋሪ አብሮነት ይበልጥ ለማጠናከርም በዓሉን በጋራ ለማክበር ጥሪው ቀርቧል።
ለልዑኩ አቀባበል ያደረጉት የሀዋሳ ከተማ ምክትል ከንቲባና የንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ኃላፊ አቶ አገና ኔቶ፤ የወላይታና የሲዳማ ሕዝቦች በደስታም ሆነ በሐዘን ጊዜ አብረው የቆዩ መሆናቸውን ገልጸዋል። ይህንን የቆየ እሴት ለማስቀጠልም በሁለቱም ወገን የሚደረጉ ሕዝብ ለሕዝብ ትስስሮች ተጠናክረው መቀጠል እንዳባቸው አጽንኦት ሰጥተዋል።
የከተማ አስተዳደሩ ከፍተኛ ኃላፊዎች ከወላይታ ዞን አስተዳደርና ሕዝብ ጋር በመሆን ቀኑን በደስታ ማክበራቸው ሕዝባዊ ትስስሩን ይበልጥ ለማጠናከር ሰፊ አስተዋጽኦ እንዳለውም አቶ አገና አክለው ገልጸዋል።
በአጠቃላይ፣ ይህ ዝግጅት ሁለቱ ሕዝቦች ያላቸውን ጠንካራ ማኅበራዊ ትስስርና አንጸባራቂ እሴቶች በድምቀት የሚያሳይ ሆኖ፣ ወደፊትም የጋራ ሰላምና ልማት ሥራዎችን አጠናክሮ ለመቀጠል ትልቅ ድርሻ የሚኖረው መሆኑ ተገልጿል።
#ሀዋሳ ከተማ መንግሰት ኮሙኒኬሽን