06/09/2026
ስፖርትን ለአንድነትና ለከተማ ልማት ልንጠቀምበት ይገባል—አቶ ሙራድ ከድር የወልቂጤ ከተማ አስተዳደር
ወልቂጤ፣ ጳጉሜ 1/ 2018 ዓ.ም
ስፖርት የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችን በማሰባሰብ ለአንድነት፣ ለማህበራዊ ትስስርና ለአካባቢ ልማት የሚያግዝ ትልቅ መሳሪያ በመሆኑ በአግባቡ ልንጠቀምበት እንደሚገባ አቶ ሙራድ ከድር የወልቂጤ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ገለጹ።
በወልቂጤ ከተማ የሚገኘው የወልቂጤ ጤና እግር ኳስ ቡድን ዓመታዊ ጠቅላላ ጉባኤውን አካሂዷል።
በጉባኤው ላይ የወልቂጤ ከተማ ከንቲባ አቶ ሙራድ ከድር እንደገለጹት፣ ስፖርት ልዩነቶችን በማጥበብ ህብረተሰቡን በአንድ ዓላማ ዙሪያ ለማሰባሰብ የሚያስችል ኃይል በመሆኑ ይህንን አቅም ለከተማዋ አንድነትና ልማት ማዋል ይገባል።
ከእግር ኳስ ውድድር ባለፈም የቡድኑ አባላት በከተማው ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ላይ በንቃት በመሳተፍ ለአካባቢያዊ ልማት አስተዋጽኦ ሊያደርጉ እንደሚገባ ከንቲባው አስገንዝበዋል።
የጤና ቡድኑ የማህበራዊ መስተጋብርንናg የህብረተሰብ ትስስርን የሚያጠናክሩ ተግባራትን አጠናክሮ በመቀጠል፣ ወጣቶችን በማፍራትና ከሌሎች አካባቢዎች ጋር የሚካሄዱ የወዳጅነት ጨዋታዎችንና የልምድ ልውውጦችን በማጠናከር የወልቂጤን ከተማ ባህል፣ እሴትና ልምድ ማስተዋወቅ እንዳለበትም ጠቁመዋል።
የወልቂጤ ከተማ አስተዳደር ወጣቶችና ስፖርት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ቶፊቅ ጀማል በበኩላቸው፣ የወልቂጤ ጤና ቡድን ከእግር ኳስ ቡድንነት ባለፈ ማህበራዊ ትስስርን እየፈጠረ የሚገኝ ቡድን መሆኑን ገልጸዋል።
ቡድኑ ወጣቶች በስፖርት ልምድና ክህሎት እንዲያዳብሩ፣ ጤናቸውን እንዲጠብቁና ትርፍ ጊዜያቸውን በአምራች ተግባር እንዲያሳልፉ የሚያግዝ መሆኑን የገለጹት አቶ ቶፊቅ፣ በቀጣይም ይህንን ሚና አጠናክሮ እንዲቀጥል ጠይቀዋል።
የወልቂጤ ጤና ቡድን መስራችና ዋና አሰልጣኝ አቶ አብድልሀኒ ተሰማ እንደገለጹት፣ ቡድኑ ከተመሰረተ ስድስት ዓመታት ያስቆጠረ ሲሆን ከ35 እስከ 40 የሚደርሱ አባላትን በማካተት እየሰራ ይገኛል።
ቡድኑ ከስፖርት ተግባሩ በተጨማሪ በተለያዩ በጎ ተግባራት በመሳተፍ ለህብረተሰቡ አርአያ ለመሆን እየሰራ መሆኑንም አሰልጣኙ አብራርተዋል።
በተጠናቀቀው ዓመት ቡድኑ አረጋውያንን በመርዳትና በመደገፍ፣ ወላጅ አልባ ህፃናትን በዩኒፎርምና በትምህርት ቁሳቁስ በማገዝ፣ በችግኝ ተከላና በከተማው የጽዳት ሥራዎች ላይ በንቃት መሳተፉን ገልጸዋል።
የቡድኑ አባላትም እንደገለጹት፣ ስፖርት ጤናን ከመጠበቅና ውድድርን ከማካሄድ ባለፈ ለማህበረሰብ ጠቀሜታ ያለውን በጎ ተግባር ለማከናወን ዕድል ይፈጥራል።
በመሆኑም ቡድኑ በቀጣይ በስፖርት እንቅስቃሴው ላይ በመቀጠል በከተማውና በሀገራዊ የልማት እንቅስቃሴዎች ላይ ያለውን ተሳትፎ ሊያጠናክር ይገባል።
አባላቱ ከወርሃዊ መዋጮ በተጨማሪ የቡድኑን የገቢ አቅም ለማሳደግ የገቢ ማስገኛ ሥራዎችን በማከናወን የቡድኑን ዘላቂነት ማረጋገጥ እንደሚያስፈልግም አመልክተዋል።
በዚህም የወልቂጤ ጤና ቡድን ስፖርትን ከጤናና ከውድድር ባለፈ ለማህበራዊ ትስስር፣ ለወጣቶች አቅም ግንባታ፣ ለከተማዋ ዕድገትና ለበጎ ተግባራት ማጠናከሪያ ለማዋል ያለውን ቁርጠኝነት በጉባኤው አረጋግጧል።