12/02/2018
በመስኖ ልማት ተጨባጭ ለውጥ እየመጣ ነው ፡፡
በኑሬ ረጋሳ
አርሶአደሩ የዝናብን ወቅት ተጠቅሞ በልግና መህር ያርሳል ከዚህም በተጨማሪ በየአካባቢያቸው ያሉትን የውሃ አማራጮችን ተጠቅመው በመስኖ ልማት ስራ ተሰማርተው ውጤታማ ስራ በመስራት ምርትና ምርታማነታቸው በከፍተኛ ሁኔታ እያሳደጉ ይገኛል፡፡
በቸሀ ወረዳ በተለያዩ ቀበሌዎች በሴቶች እና በወጣቶች ውጤታማ የመስኖ ልማት ስራዎች በባለ ድርሻ አካላቶች ሰሞኑን ተጎብኝተዋል፡፡
አርሶአደሩ በየአመቱ የግብአት አጠቃቀምና የምርትና ምርታማነት እድገት በከፍተኛ ሁኔታ እየለወጠ እንደሆነም ይታወቃል፡፡
በየአካባቢው ያለውን የውሀ አማራጮች በመጠቀም የተለያዩ አትክልቶችን በማምረት የአርሶአደሩ ህይወትና ኑሮ እንዲሁም ኢኮኖሚያዊ አቅማቸውን እየለወጡ እንደሆነም ይታወቃል፡፡
በወረዳው በመስኖ ልማት በየጊዜው ተጨባጭ ለውጥ እየመጣ ሲሆን በዚህም የአርሶደሩ፤የወጣቶች እና የሴቶች የገቢ አቅማቸው እያሳደጉ እንደሆነም የማይዋሽ ሀቅ ነው፡፡
ወጣት ዳንኤል ሽፈታ በቸሀ ወረዳ በወድሮ ቀበሌ ያሚኒ የመስኖ ልማት ማህበር አባል ሲሆን የመጀመሪያው ዲግሪው በሰመራ ዩንቨርሲቲ በሆልቲ ካልቸር ተመርቋል፡፡
ከዩኒቨርሲቲ ተመርቆ እንደወጣ ቲናው የአበባ እርሻ ልማት ማህበር በወር 3 ሺህ ብር እየተከፈለው ለ4 ወራት ያህል ሰርቷል፡፡
መንግስት ለገጠር ወጣቶች ያመቻቸውን የሥራ ዕድል ፈጠራ ተጠቅሞ ከ አራት አባላቶቹ ጋር በመደራጀት በመስኖ ልማት 10 ሄክታር መሬት ከመንግስት ተቀብለው እያለሙ ይገኛሉ፡፡
በማህበር ተደራጅተው መስራት ከጀመሩ በኋላ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን እያረጋገጡ እንደሆነምና ውጤታማ ስራ እየሰሩ ከመሆኑም በተጨማሪ ለሌሎች ወጣቶች የስራ እድልን መፍጠር መቻላቸው ነግሮናል፡፡
በዚህ ተግባር ሲሰማሩ መነሻ ካፒታላቸው 35 ሺህ ብር እንደነበረ እና በመጀመሪያ አመት ስራቸው 80 ሺህ ብር ትርፍ ማግኘት እንደቻሉም ወጣት ዳንኤል ተናግሯል፡፡
በጉብኝቱ የተገኙት የጉራጌ ዞን እርሻና ተፈጥሮ ሀብት መምሪያ ሀላፊ አቶ አለም ይርጋ ወልደስላሴ እንዳሉት በተያዘው በጀት አመት ሁሉም አርሶአደሮች በመስኖ ልማት ስራ እንዲሳተፉ ለማድረግ ለባለሞያዎችና ለአርሶአደሩ የክህሎት ስልጠና በመስጠት ወደ ተግባር ተገብቷል፡፡
በዚህም በመጀመሪያው ዙር በመስኖ ልማት 57 ሺህ ሄክታር መሬት በሰብል ለመሸፈን ግብ ተይዞ ወደ ተግባር በመግባት እስካሁኑም ባለው ሂደትም 45 ሺህ ሄክታር መሬት በሰብል መሸፈኑን ተናግረው የአርሶአደሩ የግብአት አጠቃቀም በየጊዜው መሻሻል እየታየበት እንደሆነና በሄክታር ኤንፒኤስ ከአንድ ኩንታል በላይ እንዲሁም ዩሪያ 68 ኪሎ ግራም እየተጠቀሙ ይገኛሉ፡፡
ቀደም ሲል በዞኑ መስኖ የሚያለሙ ውስን ወረዳዎች ብቻ እንደነበሩ አስታውሰው በአሁኑ ወቅት ሁሉም አካባቢዎች ቀደም ሲል በመስኖ ተግባር በተሰማሩ በሶዶ ፣ በመስቃን ፣በማረቆ ወረዳዎች ልምድ በመውሰድ በተጠናከረ ሁኔታ እየሰሩበት ይገኛል ብለው በዘርፉም ለውጥ ካመጡበት ወረዳዎች ውስጥ የቸሀ ወረዳ ተጠቃሽ ነው፡፡
በመስኖ ልማት ስራ ተጨባጭ ለውጥ እየመጣ ነው ያሉት ሀላፊው በዚህም የሴቶችና የወጣቶች ተጠቃሚነት በስፋት እየተረጋገጠ ይገኛል ብለው ሁሉም ወረዳዎች የተለያዩ የውሀ አማራጮችን ተጠቅመው በበጀት አመቱ የተያዘውን እቅድ የበለጠ ውጤታማ ለማድረግ በትኩረት አየተሰራ ይገኛል፡፡
በዞኑ የመስኖ ልማት ስራ ከጊዜ ወደ ጊዜ መሻሻል የታየበትና የአርሶአደሩም ምርትና ምርታማነት አየተረጋገጠ የመጣበት እንደሆነና ኢኮኖሚያቸው እያሳደጉ ይገኛሉ ያሉት ሀላፊው የሚመረተው ምርት የገበያ ትስስር በመፍጠር በኩል የሚታየውን ውስንነት በዘላቂነት ለመቅረፍ አጽኖት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው፡፡
ቅንጅታዊ አሰራርን በመፍጠር በመጀመሪያው ዙር ያለሙ 12 ሺህ ሄክታር መሬቶች በሁለተኛው ዙር እንደሚለማም አክለው ገልጸውልናል፡፡
የቸሃ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ መሀመድ ሰይድ እንዳስታወቁት በወረዳው በሁሉም ቀበሌዎች መስኖ የማልማት ስራ በስፋት እየተሰራበት እንደሆነም ተናግረው በዚህም በርካታ አርሶደሮች፣ ወጣቶችና ሴቶች በዘርፉ ተጠቃሚነታቸው እያረጋገጡ እንደሆነም ተናግረዋል፡፡
ወንዝ የሌለባቸው አካባቢዎች ሰፋፊ ኩሬዎችን የመቆፈር ስራ በብዛት ማከናወን የተቻለ መሆኑን ጠቁመው ባለፉት አመታት በተከናወኑ የአፈርና ውሀ ጥበቃ ስራዎች ለመስኖ ስራ የሚሆኑ ሰፋፊ ኩሬዎችን በአርሶአደሩ ጉልበት መቆፈር እንደተቻለም፡፡
በዘንድሮ አመት በመስኖ ልማት ስራ የተያዘውን እቅድ ስኬተማ ለማድረግ ከፍተኛ እንቅስቃሴ እየተደረገ እንደሆነም ተናግረው ለዚሁም ተግባር የሚውል ወደ 2 መቶ የሚጠጉ ሞተር ፓንፖች አገልግሎት እንዲሰጡ የተደረገ እንደሆነና የአርሶአደሩ የቴክኖሎጂ አጠቃቀም ውስንነት በተገቢው መቅረፍ የሚያስችል ተገቢውን ግንዛቤ በመፍጠር ተጠቃሚ ለማድረግ ከፍተኛ ጥረት እየተደረገ መሆኑን አስረድተዋል፡፡
የወረዳው እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ጽህፈት ቤት ሀላፊ አቶ ሩፋኤል ንዥናጋ በበኩላቸው በዘንድሮ አመት በወረዳው ያሉትን የውሀ አማራጮችን በመጠቀም 4 ሺህ 4መቶ 16 ሄክታር መሬት በሰብል ለመሸፈን ግብ ተጥሎ እየተሰራ ሲሆን በዚህም 4ሺህ 16 ሄክታር መሬት መሸፈኑም አስታውሰዋል፡፡
የአርሶአደሩ የግብአት አጠቃቀም ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተሻሻለ እንደሆነ ጠቅሰው በአምና ደረጃ በአንድ ሄክታር መሬት ከ60 እስከ 70 ኪሎ ግራም ማዳበሪያ ይጠቀሙ እንደነበር ያስታወሱት ሀለፊው በዘንድሮ አመት 100 ኪሎ ግራም በሄክታር ተጠቅመዋል፡፡
በወረዳው በመስኖ ልማት ሴቶች ወጣቶች እና አርሶ አደሮች በስፋት ተጠቃሚ እየሆኑ ሲሆን በዚህም በወረዳው በዘንድሮ አመት ከተያዘው 10 በመቶ በወጣቶች ፣30 በመቶ በሴቶች እንዲለማ መደረጉም ተናግረው በወረዳው 23 ሺህ አርሶአደሮች በመስኖ እንደሰማሩ ማድረግ ተችሏል፡፡
ወጣቶችን የበለጠ ተጠቃሚ ለማድረግ የገበያ ትስስሩ ላይ በትኩረት እየተሰራበት እንደሆነ ጠቅሰው ችግሩንም ለመፍታት ፣በተለያዩ ወረዳዎችና ከተማዎች እንዲሁም ከወልቂጤ ዩኒቨርስቲ ጋር የገበያ ትስስር እየተፈጠረ ሲሆን በዚህም አበረታች የሚባል ለውጥ ማምጣት መቻሉም አስረድተዋል፡፡
በመስኖ ተግባር ላይ በማህበር ተደራጅተው የሚሰሩ አንዳንድ ወጣቶችና ሴቶች በሰጡት አስታያየት የውሀ አማራጮችን በመጠቀም ጎመን ፣ካሮት፣ ቲማቲምና ሌሎችም አትክልቶችን በማልማት ተጠቃሚነታቸውን እያረጋገጡ እንደሆነም ተናግረዋል፡፡
በጉብኝቱም ከዞንና ከተለያዩ ወረዳዎች የተውጣጡ የስራ ሃላፊዎች ፣ ከሁሉም ቀበሌዎች የተውጣጡ አርሶአደሮች እና ሌሎች የሚመለከታቸው ባለድረሻ አካላቶች ተሳታፊ ነበሩ፡፡