18/06/2026
በኢትዮጵያ የተጀመሩ ግዙፍ ፕሮጀክቶች ለአፍሪካ አዲስ የከፍታ ምዕራፍ የሚያስጀምሩ መሆናቸውን የአፍሪካ አምባሳደሮች ገለጹ
------------
በተባበሩት ዐረብ ኤምሬቶች አቡዳቢ የሚገኘው የኢፌዲሪ ኤምባሲ በተለያዩ አገራዊ ወቅታዊ ጉዳዮች ዙሪያ በአቡዳቢ ለሚገኙ የአፍሪካ አምባሳደሮች ሰፊ ገለጻ ሰጥቷል፡፡
ማብራሪያውን የሰጡት በአቡዳቢ የኢፌዲሪ ልዩ መልዕክተኛና ባለሙሉ ሥልጣን አምባሳደር ክቡር ዶ/ር ጀማል በከር ሲሆኑ ገለጻው በዋናነት በአራቱ ቁልፍ አገራዊ አጀንዳዎች ማለትም በቅርቡ በተካሄደው 7ኛው ብሔራዊ ምርጫ፣ በቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ፣ በኮፕ32 (COP32) የአየር ንብረት ጉባኤ ዝግጅት እና በትግራይ ክልል ወቅታዊ ሁኔታ ዙሪያ ያተኮረ ነበር፡፡
ክቡር አምባሳደር ዶ/ር ጀማል በማብራሪያቸው እ.ኤ.አ. ሰኔ 1 ቀን 2026 ዓ.ም የተካሄደውና ከ50 ሚሊዮን በላይ ዜጎች የተሳተፉበት 7ኛው ብሔራዊ አጠቃላይ ምርጫ በአገሪቱ ታሪክ ትልቁ የምርጫ ሂደት መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ ምርጫውን የታዘቡት የአፍሪካ ኅብረትና የኢጋድ (IGAD) ታዛቢ ልዑካንም ሂደቱ ሰላማዊ፣ ተዓማኒና በአግባቡ የተመራ መሆኑን ማረጋገጣቸውን ገልጸዋል፡፡
አያይዘውም በ12 ቢሊዮን ዶላር ወጪ እየተገነባ ስላለውና በአፍሪካ አህጉር ትልቁ የአውሮፕላን ማረፊያ ልማት ፕሮጀክት ስለሆነው የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ የግንባታ ሂደት እንዲሁም ኢትዮጵያ የዓለም አቀፉን የአየር ንብረት ጉባኤ (COP32) በሊቀመንበርነት እንድታስተናግድ ስለመመረጧ ለዲፕሎማቶቹ ሰፊ መረጃ ሰጥተዋል፡፡
በትግራይ ክልል ያለውን ወቅታዊ ሁኔታ በተመለከተም የህወኃት አክራሪ ቡድኖች የፕሪቶሪያውን የሰላም ስምምነት በመጣስ የክልሉን ጊዜያዊ አስተዳደር በሕገ-ወጥ መንገድ ማፍረሳቸውን አምባሳደሩ አስታውቀዋል፡፡ በዚህ ሁኔታ ውስጥ የውጭ ተዋናዮች እጅ እንዳለበትና ሁኔታውን እያባባሱት እንደሚገኘ የጠቀሱት ክቡር አምባሳደር ዶ/ር ጀማል ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ በተለይም የአፍሪካ አገራት ይህንን ድርጊት እንዲያወግዙና ኢትዮጵያ ሕገ-መንግሥታዊ ሥርዓትን ለማስፈን ለምትከተለው ቁርጠኝነት ድጋፋቸውን እንዲሰጡ ጥሪ አቅርበዋል፡፡
ገለጻውን ተከትሎ ሃሳብ አስተያየታቸውን የሰጡት የአፍሪካ አምባሳደሮች ኢትዮጵያ ስኬታማና ሰላማዊ ብሔራዊ ምርጫ በማካሄዷ የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡
በተጨማሪም አምባሳደሮቹ ኢትዮጵያ በአህጉሪቱ ትልቁን ዘመናዊ ኤርፖርት እየገነባች መሆኑን እንዲሁም የተባበሩት መንግሥታት ድርጅትን የኮፕ32 የአየር ንብረት ጉባኤን ለማዘጋጀት መመረጧን አድንቀዋል፡፡
እነዚህ ግዙፍ ፕሮጄክቶች የኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆኑ የመላው አፍሪካ ኩራትና ሀብት መሆናቸውን የገለጹት አምባሳደሮቹ፣ ለፕሮጄክቶቹ ስኬታማነትና ፍጻሜ ማግኘት ከአገሪቱ ጎን በመቆም በጋራ ለመሥራት ሙሉ ዝግጁ መሆናቸውን አረጋግጠዋል።