08/07/2024
ፍትሕ በሌለበት ሰላም ሊኖር አይችልም!
(Without justice, there can be no peace)
የእርስ በእርስ ጦርነትና የመጠፋፋት ሃገር ኢትዮጵያ
የወጣትነት ዘመኔን ባገባደደው የውትድርና አገልግሎቴ ኢትዮጵያ ውስጥ ለ30 ዓመታት በዘለቀው የእርስ በእርስ ጦርነት ወደ 20 ዓመት የሚጠጋውን ጊዜ በውስጡ ያለፍኩ በመሆኔ ዛሬ ላይ ሆኜ በየጦር ቀጠናው በሰው ልጅ ላይ ላይ ሲደርስ የነበረው አሰቃቂና ዘግናኝ የጦር ሜዳ እልቂትና ውድመት፤ እንዲሁም ይደርስብን የነበረውን ስቃይና መከራ፤ ወደ ኋላ ሄጄ በዓይነ ሂሊናዬ ስቃኘው ይህ ነው የማይባል ከፍተኛ ቁጭትና ጥልቅ የሆነ የሃዘን ስሜት ያሳድርብኛል፡፡
ጦርነቱ ይካሄድ የነበረው በአንዲት ሉዓላዊ ሃገር ኢትዮጵያ ስር ካሉ 14 ክፍለ ሃገራት ውስጥ በኤርትራ እና ቀጥሎም ከ14 ዓመት በኋላ እንዲሁ በትግራይ ከኢትዮጵያ ተገንጥለን የራሳችንን ነፃ ሀገር እንመሠርታለን በሚል መሣሪያ አንስተው በሚዋጉ እና የሃገሪቱን ሉዓላዊነት እና አንድነት በሚያስከብር የሃገሪቱ የፀጥታ ኃይል መካከል ነበር፡፡
ከነጻ አውጪዎቹ በተጓዳኝ ሌሎች የፖለቲካም ሆነ የፍትሕና የመብት ጥያቄ በማንሳት ነፍጥ አንስተው የሚዋጉትን ጨምሮ በድምሩ 30 ዓመታትን ያስቆጠረው የእርስ በእርስ ጦርነት ሲካሄድ በመካከሉ ደግሞ ከውጪ ወራሪ ኃይል ጋር የተደረገው መጠነ ሰፊና ከፍተኛ ጦርነት ጋር ተዳምሮ በሃገራችን በሰው ልጅ ላይ የደረሰውን እልቂት፤ የአካል መጉደልና የሃብትና የንብረት መውደም ሁሉ ሲታሰብ ሃገሪቷም ሆነች ሕዝቧ እስከ አሁን ህልው ሆነው መቀጠላቸው በእጅጉ ያስገርማል፡፡
ከቶ ይህ ሁሉ ለምን እና እንዴት ሆነ? በማለት ወደ ኋላ ሄደን ስንጠይቅ በሚገባ ልንረዳውና ልንገነዘበው የምንችለው ነገር ቢኖር ሃገራችን ላለፉት ዘመናት ብቻም ሳይሆን አሁንም ድረስ እርስ በእርስ በመጠፋፋትና በመገዳደል ከዛም ጋር ተያይዞ በሚመጣ ረሃብ፤ በሽታ፤ ድህነትና ኋላ ቀርነት ተጋላጭ ሆና ለመኖሯ ዋንኛው ምክንያት ለዚች ጥንታዊትና ታሪካዊት፤ የታላቅ ሕዝብ መገኛ ለሆነች ሃገር የሚመጥናት እና የሚበጃት ዘመኑን የዋጀ መንግሥታዊ ሥርዓት ኖሯት ባለማወቁ ፍትሕ፤ ነፃነት፤ ዲሞክራሲ፤ የሕግ የበላይነትና ተጠያቂነት የሚባል ነገር ሰፍኖባት የማያውቅ በመሆኑ ነው፡፡
በዚህ መሠረት ፍትሕ በሌለበት ሰላም ሊኖር አይችልም! (Without justice, there can be no peace) እንደተባለው የሃገራችንን ሰላም ለማረጋገጥ የፍትሕ፤ ነፃነትና ዲሞክራሲ መስፈን ዋናው መሠረት ስለሆነ ሃገራቸውን እና ሕዝባቸውን የሚወዱ ግለሰቦችም ሆኑ ድርጅቶች ይህ መሠረታዊ ጥያቄ እስካልተመለሰ ድረስ ከእርስ በእርስ ጦርነት፤ ከመከራ፤ ከሰቆቃ፤ ከድህነትና ከኋላ ቀርነት መላቀቅ እንደማንችል ተረድተው ፍትሕ፤ ነፃነትና ዲሞክራሲን ለማስፈን በአንድነት ቆመው መታገል ብቸኛው አማራጫቸው አድርገው መውሰድ ይኖርባቸዋል፡፡
በሃገራችን ኢትዮጵያ ከንጉሠ ነገሥቱ አገዛዝ ቀጥሎ የተቀያየሩት አገዛዞች ሁሉ አንዱ ከሌላው ይሻል ይሆናል የአሁኑ ካለፈው ስህተት ይማር ይሆናል ተብሎ ሲታሰብ ሁሌም ከነበረው በከፋ ሁኔታ የሥልጣን ጥመኝነት፤ አንባ ገነንነት፤ እብሪትና ጭካኔ መባባስ ካልሆነ የተሻለ የሚባል መንግሥታዊ ሥርዓት ሊፈጠር አልቻለም፡፡
ከዚህ ሁሉ የከፋው ሁኔታ ደግሞ ላለፉት 33 ዓመታት የተያዘው ከሃገሪቱ ተጨባጭ ሁኔታ አንፃር መጠፋፊያ ካልሆነ በስተቀር አንዳችም ጥቅም የሌለውን ኋላ ቀር ዘር፤ ጎሳ፤ ብሔርና ቋንቋን መሠረት ያደረገ የፖለቲካ አካሄድ ነው፡፡
በዚህ የዘር ፖለቲካ ውስጥ እጅግ አስገራሚው ነገር ተማሩ፤ በዕድሜ ጎለመሱ የሚባሉት ፖለቲከኞች ሳይቀሩ ብሔርንም ሆነ ማህበረ ሰብን ከገዢ መደብ ባለመለየት አንዱን ብሔር የሌላው ታሪካዊ ጠላት ወይም የሌላው ገዢና ጨቋኝ፤ ሆኖ የኖረ በማስመስል ሕዝብን ከሕዝብ ጋር ማጋጨትና ማናከስን፤ አንዱ የሌላው ስጋት አድርጎ በማቅረብ ሕዝብ እርስ በእርሱ በስጋትና በጥላቻ እንዲኖር ማድረግን የሃገር ፖለቲካ መዘውር አድርገው በልማት ፋንታ ጥፋትን በሰላም ፋንታ የእርስ በእርስ ጦርነትን ጠማቂዎች ሆነው መገኘታቸው ነው፡፡
ኢትዮጵያ ውስጥ ትግራይ እና አማራ ክልል፤ ኦሮሚያ እና ሶማሌ ክልል አፋርና እና ደቡብ ክልል፤ ወ.ዘ.ተ ባሉ የትኛውም የኢትዮጵያ ምድር ላይ ቢኬድ ከ80% በላይ የሚሆነው በእርሻ እና በአርብቶ አደርነት የሚተዳደር ሕዝብ ነው፡፡
ይህ የሃገሪቱን አብዛኛውን ቁጥር የሚይዘው የሕብረተ ሰብ ክፍል ደግሞ በቂ የትራንስፖርት አገልግሎት፤ የህክምና እና የሆስፒታል አገልግሎት በበቂ ደረጃ የሌለው፤ ንጹህ ውሃና የመሳሰለው ያልተሟላለት፤ ከሁለት ሺህ ዓመት በላይ ባስቆጠረ እጅግ ኋላ ቀር በሆነ የአስተራረስና የአመራረት ዘዴን የሚጠቀምና ከዚህ ተላቆ ወደ ተሻለ ደረጃ የሚወስደው መንግሥታዊ አስተዳደር አጥቶ ዘመናትን ያስቆጠረ ነው፡፡
ይህም በመሆኑ አብዛኛውና ለም በተባለ አካባቢ የሚኖረው የኢትዮጵያ አርሶ አደር ሕዝብ ሳይቀር የሚያመርተው ምርት ከዓመት ዓመት አላደርስህ እያለው በክረምት ጎመን እና ቅጠል እየበላ ጭምር የሚያሳልፍና በድህነትና በጉስቁልና የሚኖር ነው፡፡
ይህም ብቻ አይደለም በዓለም ላይ ባለው የአየር ንብረት መለዋወጥ ምክንያት በየ10 ዓመቱና አንዳንዴም ባልተጠበቀ ሁኔታ በዝናብ መታጣት እና በድርቅ በመመታት ይህችኑ ከእጅ ወደ አፍ የሆነችውን ኑሮውን በማጣት ለከፋ ሁኔታ የሚዳረገው ይኸው አብዛኛውን የኢትዮጵያ ሕዝብ ቁጥር የያዘው የአርሶ አደሩ ክፍል ነው፡፡
እንግዲህ ይህንን ዓይነቱን አብዛኛውን የኢትዮጵያ ሕዝብ ነው የዘመኑ ፖለቲከኞችና የመንግሥት ባለሥልጣናት ሳይቀሩ አንዱ የሌላው ጠላት፤ አንዱ የሌላው ጨቋኝ ወይም ገዢ መደብ አድርገው በማቅረብ ሕዝብ ኋላ ቀርነቱ፤ ድህነቱና ጉስቁልናው ሳይበቃው በማያባራ የእርስ በእርስ ጦርነት ውስጥ በመግባት የመከራና የሰቆቃ ኑሮን እንዲገፋ የሚያደርጉት፡፡
ይህንን ስንመለከት ዛሬም ያለው አገዛዝ ሆነ ነገም የሚመጣው በኢትዮጵያ ውስጥ ፍትህ፤ ነጻነትና ዲሞክራሲን እስካላሰፈነ ድረስ በምድሪቷ ላይ አንዳችም ሰላም እንደማይኖር መረዳት አለበት፡፡
ይህም ስለሆነ ለሃገሩና ለሕዝቡ የሚቆረቆር የትኛውም ኢትዮጵያዊ ዓላማና ግቡ አድርጎ መያዝ ያለበት የሁሉም ቁልፍ የሆነው በኢትዮጵያ ውስጥ ፍትሕ ነፃነት፤ ዲሞክራሲና ከዚህም ጋር የሕግ የበላይነትን እና ተጠያቂነትን ማስፈን በሚለው ላይ ብቻ መሆን ይኖርበታል፡፡
ሻለቃ ማሞ ለማ