04/09/2026
በ13 ዓመት ህጻን ላይ የግብረ-ሰዶም ወንጀል የፈጸመው ግለሰብ በፅኑ እስራት ተቀጣ
#ሣውላ ነሐሴ 29/2018 ዓ.ም (ሣውላ ከተማ መንግሥት ኮሙዩኒኬሽን )
በሣውላ ከተማ መብራት ኃይል ከተማ ቀበሌ በ13 ዓመት ሕጻን ላይ የግብረ ሰዶም ወንጀል የፈጸመው ግለሰብ በ8 ዓመት ፅኑ እስራት እንዲቀጣ የሣውላ ከተማ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ውሳኔ አስተላልፏል ።
የ52 ዓመቱ አቶ አልቤኔ ካልፃዬ ወንጀሉን የፈፀመው በመብራት ኃይል ከተማ ቀበሌ ዲሞ ቀጠና ተብሎ በሚጠራው አካባቢ ነው ፡፡
የክስ መዝገቡ እንደሚያስረዳው ተከሳሽ አቶ አልቤኔ ለአካለ መጠን ያልደረሰና ዕድሜው 13 ዓመት የሆነውን ህፃን ሐምሌ 26 ቀን 2018 ዓ.ም ከምሽቱ 1: 00 ሰዓት ገደማ ህፃናት ተሰብስበው ከሚጫወቱበት የግል ተበዳይን የማን ልጅ ነህ በማለት ኃይል እና ማስገደድ በተሞላበት አኳኃን የግብረ ሰዶም ጥቃት ያደረሰበት በመሆኑ በፈፀመው ወንጀል ተከሷል፡፡
ተከሳሹ የተከሰሰበት ክስ በችሎት ተነቦለት የክስ ድርጊቱን አልፈፀምኩም በማለት ቃሉን የሰጠ ሲሆን ዐቃቤ ህግም ተከሳሽ ክሱን ክዶ የተከራከረ በመሆኑ በጉዳዩ ላይ የሚያስረዱ የህግ ምስክሮች ይሰሙልኝ በማለት ባቀረበው የሰውና የህክምና ማስረጃ መሰረት ተገቢውን ብይን ይሰጥልኝ ሲል ፍርድ ቤቱን ጠይቋል፡፡
በኢፌዲሪ የወንጀል ህግ አንቀጽ 631 ንዑስ 1 ( ሀ ) መሠረት በአቃቤ ህግ ባቀረበው ክስ መሠረት ፍርድ ቤቱም ተከሳሽ ወንጀሉን ስለመፈጸሙ በሰውና የሰነድ ማስረጃ በማጣራት ነሐሴ 29/2018 ዓ. ም በዋለው ችሎት ተከሳሽ ጥፋተኛ ሆኖ በመገኘቱ ያስተምረዋል በማለት በ8 ዓመት ጽኑ እስራት እንዲቀጣ ውሳኔ አስተላልፏል ።