22/08/2026
በመርሕና በስክነት የተካሄደ ምክክር ሳይኾን የእነ አጼ በጉልበቱ ትዕይንት በመኾኑ ሕዝብ እንዳይቀበለው!
(በሀገራዊ ምክክሩ ዙሪያ ከእናት ፓርቲ በድጋሚ የተሰጠ መግለጫ)
እናት ፓርቲ ከመነሻው የሀገራዊ ምክክር ሂደቱ ግልጽነት የጎደለውና በአገዛዙ የተጠለፈ መሆኑን ተረድቶ፣ የተዛነፈው አካሄድ መሥመር እንዲይዝ ለሀገር ይበጃል ያላቸውን አቅጣጫዎች ሲጠቁም መቆየቱ ይታወቃል። በቅርቡም ነሐሴ 6 ቀን 2018 ዓ.ም ባወጣነው መግለጫ መስመሩን የሳተ ሂደት እንደሆነ ጠቅሰን ሕዝቡም በንቃት እንዲጠብቅ ጥሪ ማድረጋችን ይታወሳል፡፡ ሆኖም የፓርቲያችንና የሌሎች መሰል ተቋማት ምክንያታዊ የእርምት አስተያየቶችን በበጎ ከመቀበል ይልቅ ጆሮ ዳባ ልበስ በመባሉ የምክክር ጉባዔው የእነ አጼ በጉልበቱ መፈንጫ ሆኖ አልፏል፡፡ አልፎ ተርፎም እንኳንስ ለአገር አዲስ መፍትሔ ሊያዋልድ ይቅርና ላለው ሀገራዊ ቀውስ ጭራሽ ቤንዚን የሚያርከፍከፍ የዜሮ ድምር ውጤት ሆኗል፡፡
ገና በእንቁላሉ ይስተካከል ስንል የከረምነው መዋቅራዊ ስህተት፤ ኮሚሽኑ ራሱ ላስቀመጠው መርሕ እንኳን ያለመገዛት፤ አብዛኛውን ተሳታፊ የወከለው ራሱ ገዢው ፓርቲ መሆን፤ አብዛኛውን ሰዓት ለበሳል ምክክርና ክርክር ሳይሆን በእረፍትና በዋዛ ፈዛዛ በማሳለፍ ጠንካራ ጉዳዮች ትኩረት መነፈግ፤ ሀገርን ሰቅዘው የያዙ ጉዳዮችና ችግሮችን ማለባበስ፤ ቀድመው በጓዳ በር የተወሰኑ ውሳኔዎችን ለማጸደቅ ሽኩቻና ሀሳቦችን ለይስሙላ ማንሳት፤ አሰልጣኝ ተብዬዎች ፕሬዝዳንቱን በሕዝብ ከመምረጥ ይልቅ እንደ ደቡብ አፍሪካ ከፓርላማ መምረጥ የምትለዋንና መሰል የጓዳ ውሳኔዎችን ብቻ እንዲያጸኑ የመጡ ሰባኪያን ሆነው መገኘት፤ የእጅ አሰጣጡ ለተወሰኑ ሰዎችና ለሚፈልጓቸው ብቻ መሆኑ፤ ድምጽ ባልተሰጠበት ሁኔታ “አብዛኛው/ሁሉም ተመካካሪ የተስማማበት” እየተባሉ ምክረ ሀሳቦች መቀመጥ፤ አጀንዳው በሚፈለገዉ መንገድ ያልሄደ ከመሰላቸው ደግሞ ምክክሮች ካለቁ በኋላ ያለቀን ጉዳይ መልሶ መላልሶ የማቅረብ፤ ከተመካካሪዎች የሚሰጡ ምክረ ሀሳቦች በድምጽ አሰጣጥ ሂደት እንደሚያልፉ ከተመካካሪዎች ስምምነት ውጭ ከሆነ ደግሞ ጉዳዩን ወደ ስምምነት የሚያመጣ የክልል ም/ቤት የተቋቋመ ቢሆንም ይህ ነው የሚባል ሥራ ያልሠራና የይስሙላ መሆኑ፡፡ ይህንና ለመዘርዘር የሚያዳግቱ መሰል ሂደታዊና መዋቅራዊ ግድፈቶች የነበሩበት ነበር፡፡
ከላይ የተጠቀሱ ችግሮች አንኳርና ለማሳያ የተጠቀሱ እጅግ ጥቂቶቹ ናቸው፡፡ በተለይ ሌሎች ጉዳዮችን እንዲሸፍን ሆነ ተብሎ በሚመስል አኳኋን ሲራገብ የነበረው የአዲስ አበባ ጉዳይ አብዛኛው ተመካካሪ ተስማምቶ ያስቀመጠው ሀሳብ “አዲስ አበባ ለፌዴራል መንግሥት ተጠሪ ትሆናለች” የሚል ቢሆንም ብልጽግና በሚፈለገዉ መንገድ የተወሰነ ባለመሆኑ ያዳራጃቸው ቡድኖች አዳራሽ ረግጦ መውጣት፣ አዳራሽ መረበሽ፣ የተቋጨን አጀንዳ እንደገና ማንሳት፣ ማስፈራራት፣ ውስጥም ከአዳራሽ ውጭም ድባቡ እንዲያስፈራ ማዋከብና “የክልል ም/ቤት” የሚባለው ከተረሳና ጊዜዉ ካለፈ በኋላ እንደገና ተሰብሰቦ ጉዳዩን እንዲያይና ያልተመከረበትን ወይም በአብዛኛው/አብላጫው ውድቅ ያደረገውን ሀሳብ ቅቡልነት እንዳለው ተደርጎ መቅረቡ ኮሚሽኑ ወጥ መርኅ የሌለውና የገዢው መንግሥት ጉዳይ አስፈጻሚ መሆኑን በገሃድ ያሳየ ጉዳይ ነው፡፡ የአዲስ አበባ ጉዳይ ከላይ በተገለጸው ሁኔታ በ50፣ 250፣ 500 ቡድኖች ጸድቆና ስምምነት ተደርጎ ለ4000 ቡድኖች ቀደም ብሎ ቀርቦ ምክክሩም ከሞላጎደል የተጠናቀቀ ሲሆን የተፈለገውና የእነ አጼ በጉልበቱ ፍላጎትና የጓዳ ውሳኔ ያ ባለመሆኑ ምክክሩ አንዴ ጠዋት ተቀጥሮ ምሽት ሲገናኝና በአብዛኛውም እንዲሁ በመጉላላት ሲበተን እስከ አርብ እንዲራዘም ተደርጎ ምን አልባትም ተመካካሪው በተሳለቸበት፣ ሙሉ ቀን ሲታሽ ውሎ ባለቀ ሰዓት ጊዜ በማሳጠር፣ በጨለማና ለአደጋ በሚያጋልጥ ሁኔታ፣ ከተመካካሪዎች ስምምነት ውጭ አስጨብጭቦ ለማሳለፍ በታሰበ አኳኋን ሲራዘም ቆይቷል፡፡ እውነታውን ግን አይቀይረውም፤ ሕዝብም እንዲህ ካለው የእቃ እቃ ጨዋታ የሚወጣ ሕግን ፈጽሞ ሊቀበል አይችልም! አዲስ አበባ በታሪክም በመርሕም የነዋሪዎቿ ብሎም የመላው ኢትዮጵያውያን እንጂ የአንድ ሁሉን የእኔ ባይ ቡድን ፍላጎት ማስፈጸሚያ አልነበረችም፣ አይደለችም፣ አትሆንምም! ይህ የታሪክም የፖለቲካም ቀይ መስመር እንደሆነ ፓርቲያችን በጽኑ ያምናል፡፡ መላው የኢትዮጵያ ሕዝብም ሆነ፣ የአዲስ አበባ ነዋሪ ከዚህ እውነት ያፈነገጠ ሀሳብ ቢሰነዘር የሕልውና ጥቃትና ሀገር የማፍረስ ማስጀመሪያ ፊሽካ አድርጎ ይቆጥረዋል፡፡
የምክክሩ አጠቃላይ ሂደትና የተቋጨበትን መንገድ ስንመለከት ኮሚሽኑ ከመነሻው ባዘጋጀውና ለተሳታፊዎች ባስተዋወቀው የምክክር ሂደት የሥራ መመሪያ ተ.ቁ 3 ውሳኔ አሰጣጥ ሂደት 3.2 በርዕሰ ጉዳይ ላይ ተመካካሪ ቡድን ደረጃ የውሳኔ ስምምነት (Consensus) አለ ለማለት የተሳታፊዎቹን 75% ድጋፍ ማግኘት ሲችል ነው ብሎ በግልጽ ያስቀመጠና ይህንኑ ለተሳታፊዎች የገለጸ ቢሆንም የአሠራር ለውጥ ማድረጉ ለጉባዔ ተሳታፊዎች ባላሳወቀበት ኹኔታ በአንድም ጉዳይ ላይ ድምጽ ተሰጥቶ በ Consensus ሆነ ያ ሊደረስ ካልቻለ በማለት ባስቀመጠው qualified ባለው አካሄድ ስምምነት የተደረሰበት ጉዳይ ባለመኖሩ ኮሚሽኑ ራሱ የዘረጋውን ሥርዓት በመናድ አተገባበሩ በሆይ ሆይ (በዝርፊያ በተሠማሩ ሰዎች ቋንቋ ሿሿ) እንዲሆን ተደርጎ የታለፈ በመሆኑ ተደረሰባቸው የተባሉ ስምምነትቶች በሙሉ ከዚህ አኳያ ሕጋዊነት እንደማይኖራቸው የኢትዮጵያ ሕዝብ እንዲያውቀው ለማድረግ ፓርቲያችን ይገደዳል።
በፓርቲያችን እምነት ምክክሩ ሌሎች ሀገሮች ሲደረግ እንዳየነውና እንደሰማነው በመርሕም እንደምናውቀው ቁልፍና አንገብጋቢ ሀገራዊ ችግሮችን መፍቻ ስልት ተደርጎ የተካሄደ አይደለም ብሎ መደምደም ይቻላል፡፡ እኛ ያደረግነው ምክክር እንኳን እንዲህ ዙሪያ መለስ ቀውስ ውስጥ ላለ ሀገር አይደለም ለቅንጦት እንኳ እንዲደረግ የሚመከር አይደለም፤በአጠቃላይ ምክክሩ ውስብስብ ችግሮችን እያለባበሰ፣ ቀላል ችግሮችን ደግሞ ማወሳሰቢያ መድረክ ሆኖ አልፏል ቢባል ማጋነን አይሆንም!
በመሆኑም፤
1. በታሪክ ፊት ምክክሩ ተጨባጭና አዎንታዊ ውጤት እንዳያስገኝና ባለው ቀውስ ላይ ተጨማሪ ቀውስ እንዲወለድ በር የከፈተው ጠበብ ሲል የኦሮሚያ ብልጽግና ሰፋ ሲል ገዢው ብልጽግና ነው፡፡
2. መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ የምክክሩ ሂደት የተቃኘበትን አደገኛ መንገድ ተገንዝቦ ከዚህ የተዛባና አቅጣጫውን ከሳተ የይምሰል ምክክር የሚወጡ አሳሳች ውሳኔዎችና ሰነዶችን እንዳይቀበልና በአመቸው መንገድ ሁሉ እንዲቃወም ጥሪ እናደርጋለን፡፡
3. እናት ፓርቲ ምክከሩ ከጅምሩ ጀምሮ የጎላ ችግሮች እንደነበሩበት ለኮሚሽኑና ለሕዝብ ያሳወቀ በመሆኑ አሁንም ውጤቱን ለማስቀየር እነአጼ በጉልበቱ የሚዘውሩት ድራማ በመሆኑ ሙሉ በሙሉ እውቅና የማይሰጠው መሆኑን እንገልጻለን፡፡
ፈጣሪ አገራችን ኢትዮጵያንና ሕዝቧን ይጠብቅ!
እናት ፓርቲ
ነሐሴ ፲፮ ቀን ፳፻፲፰ ዓ.ም
አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ