08/05/2026
የሰው ሕይወት ያጠፋን የፖሊስ አባልን በቁጥጥር ስር አውሎ ምርመራ እያጣራ መሆኑን የአዲስ አበባ ፖሊስ ዋና ጠቅላይ መምሪያ አስታወቀ፡፡
***
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 30 ቀን 2018 ዓ/ም (አዲስ ፖሊስ)፦ የአዲስ አበባ ፖሊስ ዋና ጠቅላይ መምሪያ ሚያዚያ 29 ቀን 2018 ዓ/ም በጉለሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 1 ከቀኑ 10፡40 ላይ አቶ ተገኝ ባልቻን በክላሽን ኮፕ ጠመንጃ የገደለውን ረዳት ሳጅን ማቴዎስ ተመቸውን በቁጥጥር ስር አውሎ ምርመራ እያጣራ መሆኑን አስታወቀ፡፡
ፖሊስ ባደረገው ምርመራ ከዚህ ቀደም በሟች እና በፖሊስ አባሉ መካከል ጠብ ተፈጥሮ አቶ ተገኝ በፖሊስ ላይ ባደረሰው ጉዳት ታስሮ በዋስ መለቀቁን አስታውሷል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ በእለቱ ሟች በሌላ ወንጀል ተጠርጥረው በፖሊስ ተይዘው ወደ ፖሊስ ጣቢያ ከሄዱ በኋላ ከመኪና ወርዶ ወደ ውስጥ እንዲገባ ሲጠየቅ አልገባም በሚል ግብ ግብ በመፍጠራቸው በአካባቢው ግርግር አጋጥሞ እንደነበር ፖሊስ ገልጿል፡፡
ምንም እንኳ ግለሰቡ ከፖሊስ አባላት ጋር ግርግር መፍጠራቸው ተገቢ ባይሆነም የፖሊስ አባሉ የፈፀመው ድርጊት ፍፁም ተቀባይነት የሌለው ኢ-ሰብዓዊ ድርጊት መሆኑን እና ፖሊስ ከቆመለት ዓላማ በተቃራኒ የተፈፀመ በመሆኑ ተቋሙን የማይወክል መሆኑን የአዲስ አበባ ፖሊስ ዋና ጠቅላይ መምሪያ አስታውቋል።
የአዲስ አበባ ፖሊስ በግለሰቦች ላይ የሚፈፀምን መሰል ድርጊቶች የማይታግስ መሆኑን እና የግድያውን የምርመራ ውጤት በቅርቡ ለህዝብ ይፋ እንደሚያደርግ አስታውቋል፡፡
በተፈጠረው ድርጊት የአዲስ አበባ ፖሊስ ጠቅላይ መምሪያ የተሰማውን ሀዘን በመግለፅ ለሟች ቤተሰቦቸ፣ ዘመድ አዝማዶች፣ ጓደኞች መፅናናትን ተመኝቷል፡፡
*
ለፖሊሳዊ መረጃዎቻችን፦
በፌስቡክ :- https://www.facebook.com/Addisababapolice
በቴሌግራም:- https://t.me/addispolice
በዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/AddisAbabaPoliceCommission
በትዊተር፦Twitter https://twitter.com/AddisPolice
ድረ ገጽ፦ web https://www.addispolice.gov.et/
“በጀግንነት መጠበቅ በሰብዓዊነት ማገልገል!”