Federal Civil Service Commission

Federal Civil Service Commission We aspire to see a Public Service Which Effectively and Ethically Achieves its Mission by 2020 E.C.

እንኳን ለብርሃነ ትንሳኤው በሰላም አደረሳችሁ!!በዓሉ የሰላምና የጤና እንዲሆንልዎ መልካሙን ሁሉ ይመኛል።የፌዴራል ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን:   🇪🇹🇪🇹🇪🇹
11/04/2026

እንኳን ለብርሃነ ትንሳኤው በሰላም አደረሳችሁ!!
በዓሉ የሰላምና የጤና እንዲሆንልዎ መልካሙን ሁሉ ይመኛል።
የፌዴራል ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን:
🇪🇹🇪🇹🇪🇹

የመንግሥት አገልግሎትና አስተዳደር ሪፎርም ክትትልና ድጋፍ ቡድን በክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች  ሥራውን ጀመረ!+++++++++++++++++++++++++++መጋቢት 29 ቀን 2018 ዓ.ም፣ ሲቪ...
07/04/2026

የመንግሥት አገልግሎትና አስተዳደር ሪፎርም ክትትልና ድጋፍ ቡድን በክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች ሥራውን ጀመረ!
+++++++++++++++++++++++++++
መጋቢት 29 ቀን 2018 ዓ.ም፣ ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን፣ አዲስ አበባ
የመንግሥት አገልግሎትና አስተዳደር ሪፎርም ድጋፋዊ ክትትል ቡድን ወደ ተለያዩ ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች በማቅናት የድጋፍና ክትትል ሥራውን በይፋ መጀመሩ ተገለጸ።

ቡድኑ ወደ ክልሎቹ ሲደርስ መልካም አቀባበል የተደረገለት ሲሆን፣ የድጋፋዊ ክትትሉን ዋና ዓላማና አስፈላጊነት በዝርዝር በማብራራት የቅድመ ምልከታ ሥራዎቹን በስኬት አጠናቆ ወደ ዋናው ተግባር መሸጋገሩን ካገኘነው መረጃ ለመረዳት ተችሏል።

ቡድኑ በተመደበባቸው አካባቢዎች ለሚቀጥሉት ሁለት ቀናት የሚቆይ ሲሆን፣ በዚህም ቆይታው የሪፎርም ሥራዎችን አፈጻጸም በመገምገምና አስፈላጊውን ድጋፍ በመስጠት የክትትል ሥራውን የሚያጠናቅቅ ይሆናል።
# የውጭ ግንኙነትና ኮሚኒኬሽን ስራ አስፈጻሚ

የፌዴራል ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን ለሠራተኞቹ የሞራልና የመልካም ሥነ-ምግባር እሴቶች ላይ ሥልጠና ሰጠ::****************************አዲስ አበባ መጋቢት 26 ቀን 2018 ዓ.ም፣...
04/04/2026

የፌዴራል ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን ለሠራተኞቹ የሞራልና የመልካም ሥነ-ምግባር እሴቶች ላይ ሥልጠና ሰጠ::
****************************
አዲስ አበባ መጋቢት 26 ቀን 2018 ዓ.ም፣
የፌዴራል ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን ሰራተኞች በስነ-ምግባር የታነፀና ውጤታማ አገልግሎት እንዲሰጡ የሚያስችል “የሞራል እሴትና መልካም ሥነ-ምግባር” በሚል ርዕስ የተዘጋጀ የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና ተሰጠ።

ስልጠናውን የሰጡት የኮሚሽኑ የመንግስት ሰራተኞች ሥራ ሥምሪት መሪ ሥራ አስፈፃሚ ዶ/ር ጌታቸው ዋጋው እንደገለጹት፣ በተቋም ውስጥ ውጤታማ ስራን ለመስራትና የአገልግሎት አሰጣጥን ለማሻሻል የቴክኒክ እውቀት ብቻውን በቂ ባለመሆኑ ማንኛውም ሰራተኛ በሥነ-ምግባር የታነፀ መሆን ይኖርበታል ብለዋል።

በተለይም ተአማኒነት፣ ቅንነት እና አገልጋይነትን እንደ ሰብአዊ ግዴታ በመቁጠር ራስን በሥነ-ምግባር መነጽር መፈተሽ ለተቋማዊ ስኬትና ለጤናማ የስራ አካባቢ መሰረት መሆኑን አስገንዝበዋል።

ዶ/ር ጌታቸው አክለውም ክህሎት ስራን ቢያስቀጥልም ስነ-ምግባር ግን ከፍታን እንደሚያረጋግጥ በመጠቆም፣ እሴቶች በሚሸረሸሩበት ወቅት ተቋማዊ ውድቀት ሊከተል እንደሚችል አጽንኦት ሰጥተዋል።

በዚህ የሥልጠና መድረክ ላይ የፌዴራል ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ክቡር አቶ ሽብሩ አባዲማ እና ሌሎች ከፍተኛ የተቋሙ ሃላፊዎች የተገኙ ሲሆን፣ ክቡር ምክትል ኮሚሽነሩ ለተነሱ ጥያቄዎችና አስተያየቶች ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል።

ሰልጣኞች በበኩላቸው ስልጠናው ከእለት ተእለት ስራ ባለፈ በግል ህይወታቸውና ከሰዎች ጋር ያላቸውን ግንኙነት ለማሻሻል ትልቅ ግንዛቤ እንደፈጠረላቸው ገልጸው፣ ለተገልጋዮች ቀልጣፋና ሰብአዊነት የተላበሰ አገልግሎት ለመስጠት ዝግጁ መሆናቸውን አረጋግጠዋል።

ይህ ስልጠና ኮሚሽኑ በሰው ኃይል ብቃትና ልማት ላይ የጀመረው የለውጥ ጉዞ አካል ሲሆን፣ መሰል የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ታውቋል።
# የውጭ ግንኙነትና ኮሚኒኬሽን ስራ አስፈጻሚ

የመንግስት አገልግሎትና አስተዳደር ሪፎርም ትግበራን የሚከታተል የድጋፋዊ ክትትል ቡድን ከነገ ጀምሮ ወደ ክልሎች ይሰማራል::***************************************መጋቢ...
04/04/2026

የመንግስት አገልግሎትና አስተዳደር ሪፎርም ትግበራን የሚከታተል የድጋፋዊ ክትትል ቡድን ከነገ ጀምሮ ወደ ክልሎች ይሰማራል::
***************************************
መጋቢት 26/2018፣ ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን፣ አዲስ አበባ
የሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን ኮሚሽነር ክቡር ዶ/ር መኩሪያ ኃይሌ "የምልከታው ዋና ዓላማ መቆጣጠር ሳይሆን ድጋፍ በማድረግ ተቋማት አንድ እርምጃ ወደፊት እንዲራመዱ ማስቻል ነው" ሲሉ ገለጹ። ኮሚሽነሩ ይህንን ያሉት ኮሚሽኑ በመንግስት አገልግሎትና አስተዳደር ሪፎርም ትግበራ በመጀመሪያው ዙር (Wave 1) ወደ ዝግጅት ምእራፍ የገቡ የክልልና የከተማ አስተዳደር ቢሮዎችን የስራ እንቅስቃሴ ለመገምገምና ለመደገፍ የሚያስችል የሱፐርቪዥን ቡድን ባሰማራበት ወቅት ነው።

በዕለቱ ለሱፐርቪዥን ቡድኑ የስራ መመሪያ የሰጡት ኮሚሽነሩ፤ አመራሮቹ ከሚሰሩበት ክልል ወጥተው ወደ ሌሎች ክልሎች መጓዛቸው ልምድ እንዲቀስሙ፣ ያላቸውን ተሞክሮ እንዲያካፍሉ እና የመተባበር መንፈስን እንዲያጠናክሩ የሚያስችል መሆኑን በመጥቀስ፣ ቡድኑ ስራውን በውጤታማነትና በስነ-ምግባር እንዲመራ ከአደራ ጭምር አሳስበዋል።

በም/ቢሮ ኃላፊዎች የሚመራውና ከተለያዩ ባለሙያዎች የተውጣጣው የሱፐርቪዥን ቡድን ወደ ስራ ከመሰማራቱ በፊት አስፈላጊው የዝግጅት ገለጻ ተደርጎለታል። በዚህም የትራንስፎርሜሽንና ለውጥ ስራ አስፈጻሚ ዶ/ር ወርቁ ደጀኔ መርሃ ግብሩን በንግግር የከፈቱ ሲሆን፣ የሪፎርሙ ተግባራት አፈጻጸም በሚለካበት የቼክ ሊስት አጠቃቀም ላይም ማብራሪያ ሰጥተዋል።

በተመሳሳይም የሰው ሀብት ብቃት ማረጋገጫ ፕሮጀክት ጽ/ቤት ም/ኃላፊ አቶ ተስፋዬ አጥሬ አማካኝነት ስለ መንግስት አገልግሎትና አስተዳደር ሪፎርም ፖሊሲ ለቡድኑ ግንዛቤ የሚሰጥ ገለጻ ቀርቧል።

ቡድኑ በየቢሮዎቹ የሚታዩ ክፍተቶችን በድጋፍ ለመሙላትና መልካም ተሞክሮዎችን ለመቀመር የሚያደርገውን ምልከታ አጠናቆ ሲመለስ፣ የምልከታውን ውጤት ለበላይ ኃላፊዎች ሪፖርት እንደሚያደርግ ይጠበቃል።
# የውጭ ግንኙነትና ኮሚኒኬሽን ስራ አስፈጻሚ

የሪፎርም ስራዎችን ወደ ተግባር የሚያሸጋግሩ መመሪያዎችና ማኑዋሎች በመገምገም ላይ ናቸው፡********************************መጋቢት 25 ቀን 2018 ዓ.ም | ሲቪል ስርቪስ ኮ...
03/04/2026

የሪፎርም ስራዎችን ወደ ተግባር የሚያሸጋግሩ መመሪያዎችና ማኑዋሎች በመገምገም ላይ ናቸው፡
********************************
መጋቢት 25 ቀን 2018 ዓ.ም | ሲቪል ስርቪስ ኮሚሽን | አዲስ አበባ |
የሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን የመንግስት አገልግሎትና አስተዳደር ሪፎርምን በውጤታማነት ለማስፈጸም የሚያስችሉ የተለያዩ መመሪያዎችንና ማኑዋሎችን የመገምገም ስራ እያከናወነ ይገኛል።

በሪፎርሙ የዝግጅት ምዕራፍ ፖሊሲዎች፣ ስትራቴጂዎች፣ ደንቦችና መመሪያዎች ሲዘጋጁ የቆዩ ሲሆን፤ የሪፎርም ፖሊሲው፣ አዋጁ እና አስር ስትራቴጂዎች ተጠናቀው ዝግጁ መሆናቸውን ኮሚሽኑ አስታውቋል።

አሁን ላይ ደግሞ ይህንን ግዙፍ ሀገራዊ ሪፎርም ወደ ተግባር ለመቀየርና መሬት ለማውረድ የሚያስችሉ የህግ ማእቀፎችና ማኑዋሎች በተለያየ ጊዜ ጥልቅ ግምገማና ማሻሻያ ሲደረግባቸው የቆዩ ቢሆንም፣ የመጨረሻና የማጠቃለያ ግምገማ እየተደረገላቸው ይገኛል።

ለተከታታይ ቀናት በሚቆየው የግምገማ መድረክ ላይ የኮሚሽኑ ከፍተኛ አመራሮች ክቡር ኮሚሽነር ዶ/ር መኩሪያ ኃይሌ እና ክቡር ምክትል ኮሚሽነር ዶ/ር ጌታቸው ጀምበር ተገኝተዋል፡፡

እነዚህ ሰነዶች ጸድቀው ወደ ስራ ሲገቡ ለመንግስት አገልግሎትና አስተዳደር ሪፎርሙ ስኬታማነት ትልቅ የማስፈጸሚያ መሳሪያ ሆነው እንደሚያገለግሉ ይጠበቃል።
# የውጭ ግንኙነትና ኮሚኒኬሽን ስራ አስፈጻሚ

በፌዴራል ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን አራተኛው የዳኞች አስተዳደር ጉባኤ ተካሄደ፡፡***************************መጋቢት 25 ቀን 2018 ዓ.ም | ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን| | አዲስ አበ...
03/04/2026

በፌዴራል ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን አራተኛው የዳኞች አስተዳደር ጉባኤ ተካሄደ፡፡
***************************
መጋቢት 25 ቀን 2018 ዓ.ም | ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን| | አዲስ አበባ
4ኛው መደበኛ የዳኞች አስተዳደር ጉባኤ በተለያዩ አጀንዳዎች ላይ በዝርዝር በመወያየት የውሳኔ ሃሳቦችን በማሳለፍ ተጠናቋል።

ጉባኤው በቆይታው የፍትህ ስርዓቱን ውጤታማነት ለማሳደግ፣ የዳኞችን የስራ አፈፃፀም ለማሻሻል እና ተያያዥ የአስተዳደር ጉዳዮች ላይ ትኩረት አድርጎ መክሯል።

በውይይቱም የቀረቡ አጀንዳዎችን በጥልቀት ከመረመረ በኋላ ለቀጣይ ስራዎች መነሻ የሚሆኑ ጠቃሚ የውሳኔ ሃሳቦችን አስተላልፏል። ይህ ጉባኤ የዳኞች አስተዳደር ስርዓት ይበልጥ ግልፅ፣ ቀልጣፋና ተጠያቂነት የሰፈነበት እንዲሆን ለማስቻል የሚደረገው ጥረት አካል መሆኑ ተገልጿል።
#የውጭ ግንኙነትና ኮሚኒኬሽን ስራ አስፈጻሚ

 #አዋጁ የፌዴራል መንግስት ሰራተኞች አዋጅ 1353/17 Federal Civil Servants Proclamation  No. 1353/2025የሥራ አካባቢ ደህንነትና ጤንነት:ሁኔታ ምን ይላል?ክፍ...
02/04/2026

#አዋጁ
የፌዴራል መንግስት ሰራተኞች አዋጅ 1353/17
Federal Civil Servants Proclamation No. 1353/2025
የሥራ አካባቢ ደህንነትና ጤንነት:ሁኔታ ምን ይላል?
ክፍል አሥር አንቀፅ 77 -78
77. የሥራ አካባቢ ደህንነትና ጤንነት ዓላማና ተፈጻሚነት

1. ማንኛውም የመንግሥት መሥሪያ ቤት የሥራ አካባቢ ደህንነትና ጤንነት ዓላማ፡-
ሀ) የመንግሥት ሠራተኞችን ደህንነትና ጤንነት በመጠበቅ የሥራ ብቃትን ማጐልበት፤
ለ) የሥራ ቦታን ለመንግሥት ሠራተኞች ደህንነትና ጤንነት በሚስማማ መልኩ ማዘጋጀት፣ ማሻሻልና መጠበቅ፤
ሐ) የመንግሥት መሥሪያ ቤት በጐ በሆነ ማህበራዊ ሕይወት ላይ ተመሥርቶ አመርቂ የሥራ ውጤት እንዲያስመዘግብ ማብቃት ይሆናል፡፡

2. ማንኛውም የመንግሥት መሥሪያ ቤት የሥራ ከባቢ ምቹነትን ማሻሻል፡-
ሀ) የሥራ ከባቢን ምቹ ማድረግን ትኩረት ሰጥቶ እና የዕቅዱ አካል አድርጎ መሥራት፣
ለ) ሠራተኛው በቅርበት በተመጣጣኝ ዋጋ የካፊቴሪያ አገልግሎት እና የስፖርት ማዘውተሪያ እንዲያገኝ ማመቻቸት፤አለበት፡፡

3. የዚህ ክፍል ድንጋጌ ለጊዜያዊ ሠራተኞችም ተፈጻሚ ይሆናል፡፡

78. በሥራ ላይ ስለሚደርስ ጉዳት

1. “በሥራ ላይ የሚደርስ ጉዳት” ማለት በሥራ ላይ የሚደርስ አደጋ ወይም በሥራ ምክንያት የሚመጣ በሽታ ነው፡፡

2 “በሥራ ላይ የሚደርስ አደጋ” ማለት የመንግሥት ሠራተኛው መደበኛ ሥራውን በማከናወን ላይ እንዳለ ወይም ከሥራው ጋር በተያያዘ ምክንያት በአካሉ ወይም በአካሉ የተፈጥሮ ተግባር ላይ በድንገት የሚደርስ ጉዳት ሲሆን የሚከተሉትን ይጨምራል:-
ሀ) የመንግሥት ሠራተኛው ከመደበኛ ሥራው፣ የሥራ ቦታው ወይም የሥራ ሰዓቱ ውጭ ወይም ለጊዜው ሥራውን ለማሰራት ሥልጣኑ በሚፈቅድለት ሰው የተሰጠውን ትዕዛዝ በመፈጸም ላይ እያለ የደረሰን ጉዳት፤
ለ) ሥልጣኑ በሚፈቅድለት ሰው የተሰጠው ትዕዛዝ ባይኖርም የመንግሥት ሠራተኛው በመሥሪያ ቤቱ ውስጥ የደረሰን ድንገተኛ አደጋ ወይም ጥፋት
ለመከላከል በሥራ ሰዓት ወይም ከሥራ ሰዓት ውጭ በሚፈጽመው ተግባር ምክንያት የደረሰን ጉዳት፤
ሐ) የመንግሥት ሠራተኛው ወደ ሥራ ቦታው ወይም ከሥራ ቦታው መንግሥት ለሠራተኞች አገልግሎት እንዲሰጥ በመደበው የመጓጓዣ አገልግሎት ወይም መሥሪያ ቤቱ ለዚህ ተግባር በተከራየውና በግልጽ በመደበው የመጓጓዣ
አገልግሎት በመጓዝ ላይ በነበረበት ጊዜ የደረሰን ጉዳት፤
መ) የመንግሥት ሠራተኛው ሥራውን በማከናወን ላይ ባለበት ጊዜ በመንግሥት መሥሪያ ቤቱ ወይም ከሥራው ጋር በተገናኘ ወይም በሦስተኛ ወገን ድርጊት ምክንያት የደረሰበትን ጉዳት፡፡

3 “በሥራ ምክንያት የሚመጣ በሽታ” ማለት የመንግሥት ሠራተኛው ከሚሠራው
የሥራ ዓይነት ወይም ሥራውን ከሚያከናውንበት አካባቢ የተነሳ በሽታን ለሚያስከትሉ ሁኔታዎች ተጋልጦ በመቆየቱ ምክንያት የደረሰ የጤና መታወክ ሲሆን፣ ሥራውን በሚያከናውንበት ቦታ የሚዛመቱና የሚይዙ ነዋሪ ወይም ተላላፊ በሽታዎችን አይጨምርም፡፡

4. በዚህ አንቀጽ ንዑስ አንቀጽ (3) የተመለከተው ቢኖርም በመደበኛ ሥራው ምክንያት ተላላፊ ወይም ነዋሪ በሽታዎችን በማጥፋት ላይ የተሰማራ
የመንግስት ሠራተኛ በዚሁ በሽታ ከተያዘ በሥራ ምክንያት የመጣ በሽታ እንደያዘው ይቆጠራል፡፡

5. በሥራ ላይ በሚደርስ ጉዳት ምክንያት የሚከሰት የአካል ጉዳት መጠን አግባብ
ባለው የመንግሥት ሠራተኞች ጡረታ ሕግ ድንጋጌዎች መሠረት ይወሰናል፡፡

6. በዚህ አንቀጽ ንዑስ አንቀጽ (1) የተመለከተው ቢኖርም ሠራተኛው ሆነ ብሎ በተለይም በመሥሪያ ቤቱ አስቀድሞ በግልጽ የተሰጡትን የደህንነት መጠበቂያ መመሪያዎች በመጣስ ወይም በመጠጥ ወይም በአደንዛዥ ዕፅ ሰክሮ በሥራ
ላይ በመገኘቱ የደረሰበት ጉዳት በሥራ ምክንያት እንደደረሰ ጉዳት አይቆጠርም፡፡

የመንግስት አስተዳደር ሪፎረምን ውጤታማ ለማድረግ የተቋማት የበጀት ዝግጅት ወሳኝ መሆኑ ተገለጸ፡፡*************************መጋቢት 23 ቀን 2018 ዓ.ም | ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽ...
01/04/2026

የመንግስት አስተዳደር ሪፎረምን ውጤታማ ለማድረግ የተቋማት የበጀት ዝግጅት ወሳኝ መሆኑ ተገለጸ፡፡
*************************
መጋቢት 23 ቀን 2018 ዓ.ም | ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን | አዲስ አበባ |
የመንግስት አገልግሎትና አስተዳደር የሪፎርም ሥራዎች በታቀደላቸው መሠረት ውጤታማ በሆነ መንገድ እንዲተገበሩ ለማስቻል፣ በዌቭ አንድና ሁለት ወደ ሪፎረሙ የተቀላቀሉ እንዲሁም በዌቭ ሦስት የሚቀላቀሉ ተቋማት ጋር የሪፎርም ማስፈጸሚያ በጀት የሚፈጥረውን ተጽዕኖ ለመቀነስ የሚያስችል የምክክር መድረክ ተካሂዷል።

በመድረኩ ላይ የፌዴራል ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን ኮሚሽነር ክቡር ዶ/ር መኩሪያ ኋይሌ እና ለውጥና ትራንስፎርሜሽን ዘርፍ ም/ኮሚሽነር ክብርት ወ/ሮ አልማዝ መሰለ የተገኙ ሲሆን፣ የፌዴራል ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቶች፣ የዴሞክራሲ ተቋማትና የጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት ተጠሪ ተቋማት አመራሮችም በውይይቱ ተሳትፈዋል።

በመድረኩ ላይ የለውጥና ትራንስፎርሜሽን መሪ ሥራ አስፈጻሚ ዶ/ር ወርቁ ደጀኔ በጀት የሚያስፈልጋቸው የሪፎርም ተግባራት ላይ ሰፊ ማብራሪያ የሰጡ ሲሆን፣ በተለይ ወደ ሪፎርም መርሃ-ግብሩ የገቡም ይሁኑ በሦስተኛው ምዕራፍ (Wave 3) ወደ ሪፎርሙ የሚቀላቀሉ ተቋማት አስፈላጊውን የበጀት ዝግጅት ከወዲሁ እንዲያደርጉ ጥብቅ ማሳሰቢያ ተላልፏል።

የሪፎርም ስራዎች በበጀት እጥረት ምክንያት እንዳይስተጓጎሉ ተቋማቱ አጠቃላይ የተቋሙ ታሪካዊ ዳራን፣ ፖሊሲ፣ የህግ ማዕቀፎች፣ ለሰው ኃይል ስልጠና፣ ለቴክኖሎጂ ዝርጋታ፣ ለአደረጃጀት ጥናት፣ለሥራ ፍሰት ማሻሻያ እና ለብቃት ምዘና ፈተናዎች ዝግጅት የሚሆን ፋይናንስ ከመደበኛ በጀታቸው በተጓዳኝ በእቅድ እንዲያሲዙ አቅጣጫ ተቀምጧል።

በመጨረሻም ይህ የቅድመ ዝግጅት ስራ ተቋማቱ የተሻለ የአገልግሎት አሰጣጥና ቀልጣፋ የአስተዳደር ስርዓት ለመዘርጋት የሚያደርጉትን ጥረት የሚያግዝ መሆኑ ተመላክቶ፣ ከተሳታፊዎች ለተነሱ ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ በመስጠትና የሪፎርም ሥራው በተቀመጠለት የጊዜ ሰሌዳና ጥራት እንዲከናወን የጋራ መግባባት ላይ በመድረስ መርሃ-ግብሩ በስኬት ተጠናቋል።
#የውጭ ግንኙነትና የኮሙኒኬሽን ሥራ አስፈፃሚ

 #አዋጁየፌዴራል መንግስት ሰራተኞች አዋጅ 1353/17ክፍል አስር :አንቀፅ 84 84.ከሥራ በመጣ ጉዳት ምክንያት የሚሰጥ ህክምና እና ፈቃድ 1. በሥራው ምክንያት ጉዳት ለደረሰበት የመንግሥት...
01/04/2026

#አዋጁ
የፌዴራል መንግስት ሰራተኞች አዋጅ 1353/17
ክፍል አስር :አንቀፅ 84
84.ከሥራ በመጣ ጉዳት ምክንያት የሚሰጥ ህክምና እና ፈቃድ

1. በሥራው ምክንያት ጉዳት ለደረሰበት የመንግሥት ሠራተኛ በሀገር ውስጥ
ለሚሰጡ ለሚከተሉት የሕክምና አገልግሎቶች የሚያስፈልገው ወጪ በመሥሪያ
ቤቱ ይሸፈናል:-

ሀ) የጠቅላላና የልዩ ሕክምና እንዲሁም የቀዶ ሕክምና ወጪዎች፤
ለ) የሆስፒታልና የመድሀኒት ወጪዎች፤
ሐ) የማንኛውም አስፈላጊ ሰው ሰራሽ ምትክ ወይም ተጨማሪ አካሎችና
የአጥንት ጥገና ወጪዎች፡፡

2. ጉዳት ለደረሰበት የመንግሥት ሠራተኛ በዚህ አንቀጽ ንዑስ አንቀጽ (1) መሠረት
የሚሰጠው የሕክምና አገልግሎት በግል የሕክምና ተቋም እንዲሰጠው
የሚደረገው አገልግሎቱ በመንግሥት የሕክምና ተቋማት ሊሰጠው የማይችል
ሲሆን ብቻ ነው፡፡

3. በሥራ ምክንያት ጉዳት የደረሰበት ማንኛውም የመንግሥት ሠራተኛ ከጉዳቱ
መጠን ታይቶ በሕክምና ማስረጃ በሚገልጻው መሠረት ድኖ ወደ ሥራው
እስከሚመለስ ወይም በጉዳቱ ምክንያት ለዘለቄታ መሥራት የማይችል መሆኑ
በሕክምና ማስረጃ እስከሚረጋገጥ ድረስ የሕመም ፈቃድ ከሙሉ ደመወዝ ጋር
ይሰጠዋል፡፡ የመንግሥት ሠራተኛው ለዘለቄታው መሥራት ያለመቻሉ
በሕክምና ማስረጃ ከተረጋገጠ በዚህ አዋጅ አንቀጽ 85 የተደነገጉት ጥቅሞች
ይጠበቁለታል፡፡

4. ሠራተኛው ሕክምናውን በአግባቡ ባለመከታተሉ ወይም በሐኪም የተሰጠውን
ትዕዛዝ ባለማክበሩ ሕክምናውን ያጓተተ እንደሆነ በዚህ አንቀጽ ንዑስ አንቀጽ (1)
እና (2) ድንጋጌ መሠረት የሚሰጠው ሕክምና እና ፈቃድ ይቋረጥበታል፡፡

5. ኮሚሽኑ በዚህ አንቀጽ ንዑስ አንቀጽ (1) ስለተመለከተው የሕክምና ወጪ
አከፋፈል የአፈጻጸም መመሪያ ማውጣት አለበት፡፡

የተጀመረው  የለውጥ ሥራ የመንግስት አገልግሎት አሰጣጥ ፍጥነት፣ ግልጽነትና ጥራት ላይ ከፍተኛ ለውጥ ያመጣል ተብሎ እንደሚታመን ተገለፀ።,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,...
01/04/2026

የተጀመረው የለውጥ ሥራ የመንግስት አገልግሎት አሰጣጥ ፍጥነት፣ ግልጽነትና ጥራት ላይ ከፍተኛ ለውጥ ያመጣል ተብሎ እንደሚታመን ተገለፀ።
,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,,
መጋቢት 22 ቀን 2018 ዓ.ም.፣ ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን፣ አዲስ አበባ
የፌዴራል ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን የኢትዮጵያ መንግስት አገልግሎትና አስተዳደር የኢንዱስትሪና የሙያ ምድብ፣ የስራ ፍሰት (BPMN)፣ የአደረጃጀት እና የቴክኒካል ብቃት ማዕቀፍ ለማዘጋጀት የሚያስችል የሥራ ማስጀመሪያ መድረክ በቢሸፍቱ የኢትዮጵያ ሥራ አመራር ኢንስቲትዩት አካሂዷል።

በዚህ መድረክ ላይ በዌቭ ሁለት (Wave 2) ወደ ሪፎርሙ የገቡት የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስቴር እንዲሁም የትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ ሚኒስቴር የሥራ ኃላፊዎችና ባለሙያዎች ተገኝተዋል።

ይህ የሪፎርም ስራ ተቋማቱ በተለምዶ ከሚሰራበት አሰራር ወጥተው በዓለም አቀፍ ደረጃ ተቀባይነት ወዳለውና በቴክኖሎጂ ወደታገዘ የሥራ ፍሰት ሞዴል (BPMN) እንዲሸጋገሩ የሚያስችል ነው። የሥራው ዋና ዓላማ በሁለቱ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቶች ስር የሚገኘውን የሰው ኃይል ስምሪት ከዘመናዊ የሥራ ሂደቶች ጋር ማጣጣም ሲሆን፣ ይህም አገልግሎት ፈላጊዎች እንግልት ሳይገጥማቸው በፈጣንና በቀጥተኛ መንገድ ምላሽ የሚያገኙበትን አሰራር መዘርጋትን ያካትታል። በተጨማሪም እያንዳንዱ ሰራተኛ ባለው የትምህርት ዝግጅት፣ ልምድና ብቃት ልክ በትክክለኛው የሥራ መደብ ላይ እንዲመደብ የሚያስችል የጥናት ትግበራና የሥራ ፍሰቱን ከወረቀት ንክኪ ነፃ ወደሆነ የዲጂታል አሰራር ማሸጋገር የሪፎርሙ አካል መሆኑ ተገልጿል።

ይህ አዲስ አደረጃጀት ተግባራዊ ሲሆን ግልጽነትና ተጠያቂነትን በማንገስ፣ ማን ምን እንደሚሰራና የትኛው የሥራ ክፍል ምን ውጤት ማምጣት እንዳለበት በግልጽ የሚያሳይ ይሆናል። ተደራራቢ የሥራ ክፍሎችን በማስቀረት የሰው ኃይልንና በጀትን በቁጠባ ለመጠቀም እንዲሁም ግልጽ የሆነ የሙያ እድገትና የምደባ ስርዓት በመዘርጋት የሰራተኛውን የሥራ ተነሳሽነት እንደሚያሳድግ ተጠቁሟል።

በተለይም BPMN(Business Process Model and Notation) የተሰኘውን ዓለም አቀፍ የሥራ ፍሰት መለኪያ መሣሪያ መጠቀም መጀመሩ ተቋማቱ ወደ ዲጂታል አሰራር ለመሸጋገር፣ ውስብስብነትን ለማስቀረትና በሥራ አመራር ሂደቱ ላይ የጋራ መግባባት ለመፍጠር ትልቅ እድል እንደሚሰጥ በመድረኩ ተብራርቷል።

የኢንዱስትሪና የሙያ ምድብ፣ የአደረጃጀት እና የቴክኒካል ብቃት ማዕቀፍ አዘገጃጀትን በተመለከተ በዶ/ር ቻላቸው በሪሁን (የፌዴራል ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን የአደረጃጀትና የሥራ ምዘና መሪ ሥራ አስፈፃሚ) እንዲሁም የሥራ ፍሰት (BPMN) ቀረጻን በተመለከተ በዶ/ር በረከት ሰለሞን (ከኢትዮጵያ ፐብሊክ ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ) ሰፊ ገለጻ ቀርቧል።

ከመድረኩ ለቀረቡ ጥያቄዎችና አስተያየቶችም ማብራሪያና ምላሽ የተሰጠ ሲሆን፣ ስራው ለተከታታይ ቀናት የሚቆይና ከባለሙያዎችና ከባለድርሻ አካላት የሚነሱ ግብዓቶች ተካተውበት ወደ ሙሉ ትግበራ እንደሚገባ ታውቋል።
የውጭ ግንኙነትና የኮሙኒኬሽን ሥራ አስፈፃሚ

ክፍት የስራ ቦታ ማስታወቂያ! አዲስ ዘመን ጋዜጣ ቅዳሜ መጋቢት 19 ቀን 2018 ዓ.ም. የወጣ:የፌደራል ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን ክፍት በሆኑ  የስራ መደቦች ላይ በቋሚ , በዝውውር እና በኮንት...
31/03/2026

ክፍት የስራ ቦታ ማስታወቂያ! አዲስ ዘመን ጋዜጣ ቅዳሜ መጋቢት 19 ቀን 2018 ዓ.ም. የወጣ:
የፌደራል ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን ክፍት በሆኑ የስራ መደቦች ላይ በቋሚ , በዝውውር እና በኮንትራት ሰራተኞችን አወዳድሮ መቅጠር ይፈልጋል፡፡
ስለሆነም በዚህ የሥራ እድል መወዳደር ለምትፈልጉ በመጀመሪያ lmis.gov.et ብላችሁ በመመዝገብ አቅራቢያችሁ ባለ የአገልግሎት መስጫ ማዕከል (ወረዳ ወይም ቀበሌ) በመሄድ የባዮሜትሪክስ መረጃ በመስጠት የሰራተኛነት መለያ ቁጥር /Labor ID/ ከያዛችሁ በዚህ https://forms.lmis.gov.et/federal_-civil_services_three/ በመግባት ትክክለኛ መረጃዎትን ሞልተው ማመልከት የምትችሉ መሆኑን እናሳውቃለን።

አመልካቾች ይህ ማስታወቂያ ከወጣበት ቀን ከ 21/07/2018 ዓ.ም ጀምሮ ለተከታታይ 7ቀናት ማመልከት ይችላሉ።

የሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን ከክልልና ከተማ አስተዳደር የቢሮ ኃላፊዎችና ምክትል ኃላፊዎች ጋር በመንግስት አገልግሎትና አስተዳደር አፈጻጸም ዙሪያ ሰፊ የምክክር መድረክ አካሄደ።============...
28/03/2026

የሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን ከክልልና ከተማ አስተዳደር የቢሮ ኃላፊዎችና ምክትል ኃላፊዎች ጋር በመንግስት አገልግሎትና አስተዳደር አፈጻጸም ዙሪያ ሰፊ የምክክር መድረክ አካሄደ።
============
መጋቢት 19፣ ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን፣ አዲስ አበባ
የፌዴራል ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን ኮሚሽነር ክቡር ዶ/ር መኩሪያ ኃይሌ የመንግስት አገልግሎትና አስተዳደር ፖሊሲ ትግበራን በተመለከተ በሰባቱ የሪፎርም አምዶች ዙሪያ ከዝግጅት ምዕራፍ ጀምሮ እስከ ተግባር ምእራፍ የተከናወኑ ተግባራትን በዝርዝር አቅርበዋል። እነዚህ የለውጥ ስራዎች የሲቪል ሰርቪስ ተቋማትን ከቆመ ቢሮክራሲ ወደ ዘመናዊና ቀልጣፋ አሰራር (Meritocracy) ለማሸጋገር መሰረት መሆናቸውን አክለው ገልጸዋል፡፡

ሪፎርሙ ውጤታማ እንዲሆን ኮሚሽኑ በትኩረት እየሰራባቸው የሚገኝ ዋና ዋና ነጥቦች ከሰነድ ዝግጅቶች የጀመረውን አሰራር ፤የዲጂታላይዜሽን ስራዎች (ICSMIS) ሪፎርሙን በቴክኖሎጂ ለመደገፍና የተገልጋይን እርካታ ለማረጋገጥ የተቀናጀ የሲቪል ሰርቪስ መረጃ ስርአት ትግበራ ቁልፍ መሆኑን ፤ በየደረጃው ያለውን የሰው ኃይል በዕውቀትና በክህሎት ለመመዘን የሚከናወኑ ስራዎች የሪፎርሙ የጀርባ አጥንት መሆናቸውንና የተቋማዊ አሰራር ከባህላዊ አሰራር ወጥቶ ለውጤትና ለተገልጋይ ቅድሚያ የሚሰጥ ተቋማዊ ስብዕና መገንባት ላይ ትኩረት ያደረገ መሆኑንና ሌሎች መሰል ስራዎችን አንስተዋል፡፡

አብዛኞቹ ክልሎች በሚባል ደረጃ የሪፎርሙን የዝግጅት ምዕራፍ የጀመሩ ሲሆን፣ የሰነድ ዝግጅትና የሰው ኃይል የማብቃት ስልጠናዎችን እያከናወኑ ይገኛሉ። የጠቅላይ ሚኒስትሩ ኢንሼቲቭና የሪፎርሙ ውጤት የሆነው የመሶብ (MESOB) አንድ ማዕከል አገልግሎት ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ አገልግሎት እንዲሰጥ እየተሰራ መሆኑ ተገልጿል።

ክቡር ኮሚሽነር ዶ/ር መኩሪያ ኃይሌ እንደገለጹት፤ የስኬት ሚስጥሩ ዝግጅት መሆኑን ገልጸው ክልሎችና ተጠሪ ተቋሞቻቸው በዝግጅት ምዕራፉ ላይ በአግባቡ የሚሰሩና ተመዝነው መስፈርቱን የሚያሟሉ ከሆነ፣ የሪፎርም ትግበራቸው 100% ስኬታማ ሊሆን እንደሚችል አበክረው ገልጸዋል።
ክልሎችም ይህንን ተሞክሮ ወደ ተግባር ለመለወጥ የኮሚሽኑን የባለሙያ፣ የአቅም ግንባታና የቁሳቁስ ድጋፍ ጠይቀዋል።

መድረኩ በክቡር የሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽነር ዶ/ር መኩሪያ ኃይሌ ሰብሳቢነት የተመራ ሲሆን፣ በመድረኩ ለተነሱ ጥያቄዎችና አስተያየቶች የኮሚሽኑ የትራንስፎርሜሽንና የለውጥ ምክትል ኮሚሽነር ወ/ሮ አልማዝ መሰለ እና የመንግስት ስራ ስምሪት ዘርፍ ምክትል ኮሚሽነር አቶ ሽብሩ አባዲማ ሰፊ ማብራሪያና ምላሽ ሰጥተዋል። በመጨረሻም፣ በቀጣይ የስራ አቅጣጫዎችና የመገናኛ መንገዶችን በጋራ በማስቀመጥ መድረኩ በስኬት ተጠናቋል።

# የውጭ ግንኙነትና ኮሚኒኬሽን ስራ አስፈጻሚ

Address

Bole Road, Kirkos S. City Woreda 09 Around Flamingo Restaurant
Addis Ababa
1082

Opening Hours

Monday 08:30 - 17:30
Tuesday 02:30 - 17:30
Wednesday 02:30 - 17:30
Thursday 02:30 - 17:30
Friday 02:30 - 17:30

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when Federal Civil Service Commission posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Contact The Organization

Send a message to Federal Civil Service Commission:

Share