23/08/2026
በምስራቅ ባሌ ዞን የተከናወነ ስኬታማ የክረምት በጎ አድራጎት ተግባር
*********
አዲስ አበባ፣ ነሀሴ 17/2018፣ ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን
በክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ አነሳሽነት በአገር አቀፍ ደረጃ እየተካሄደ የሚገኘውን የክረምት በጎ አድራጎት ኢኒሼቲቭ በመደገፍ፤ ተጠሪነታቸው ለጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት የሆኑት የፌዴራል ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን እና የኢትዮጵያ አደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን በኦሮሚያ ክልል፣ ምሥራቅ ባሌ ዞን፣ ጊኒር ወረዳ፣ ሸወዴ ቀበሌ ሰፊ የበጎ አድራጎት ተልዕኮ አከናወኑ።
የሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን ኮሚሽነር ክቡር ዶ/ር መኩሪያ ኃይሌ በቦታው ተገኝተው መርሀ ግብሩን ያስጀመሩና መልእክት ያስተላለፉ ሲሆን፣ የኮሚሽኑ ምክትል ኮሚሽነሮች ክቡር ዶ/ር ጌታቸው ጀምበርና ክቡር አቶ ሽብሩ አባዲማም ተገኝተዋል፡፡
ለገጠር ኮሪደር ልማት ተስማሚ የሆኑ የ15 መኖሪያ ቤቶች እና የአንድ መዋለ ህጻናት ግንባታ የመሠረተ ድንጋይ ማኖር፣ 42,000 ችግኞችን የመትከል መርሃ ግብር፣ አነስተኛ ገቢ ላላቸው ቤተሰቦች ለሚገኙ 540 ህጻናት የትምህርት መማሪያ ቁሳቁስ ድጋፍ፣ ከአካባቢው ወጣቶች ጋር የማነቃቃት እና የውይይት መድረክ ማካሄድ በክረምት በጎ አድራጎት መርሀግብሩ የተከናወኑ ተግባራት ናቸው፡፡
እስከ መጪው አዲስ ዓመት መባቻ ድረስ የቤቶቹን ግንባታ ለማጠናቀቅ ርብርብ እየተደረገ ሲሆን ከዞኑ አስተዳደር ጋር በተደረገው ስምምነት መሰረት ተጨማሪ 5 ቤቶች በዞኑ አስተዳደር የሚገነቡ ሲሆን፤ ጎን ለጎን አቅም ያላቸው አርሶ አደሮች ቴክኖሎጂውን ተጠቅመው የራሳቸውን ቤቶች እንዲገነቡ ምቹ ሁኔታዎች እየተፈጠሩ በመሆኑ ፕሮጀክቱ ሲጠናቀቅ አካባቢው ለገጠር ኮሪደር ልማት ስራዎች ጥሩ ማሳያ ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል።
በስፍራው የተገኙት የተቋማቱ የጋራ ልዑካን ቡድን ከተልዕኮው ጎን ለጎን ከጎባ-ሮቤ ከተማ 100 ኪ.ሜ ርቀት ላይ የሚገኘውን አስደናቂውን የሶፍ ዑመር ዋሻ ጎብኝተዋል፡፡ ከ12ኛው ክፍለ ዘመን ጀምሮ ታሪካዊ ዳራ ያለው ይህ ድንቅ የተፈጥሮ ስጦታ፤ በአሁኑ ወቅት ወደ ስፍራው የሚያደርሰው መንገድ እየተሰራና አካባቢውም እየለማ በመሆኑ፣ ዜጎች ይህንን ሀገራዊ ሀብትና የቱሪስት መዳረሻ ቦታ ሄደው እንዲጎበኙ ኮሚሽኑ ጥሪውን ያቀርባል።
#የውጭ ግንኙነትና ኮሚኒኬሽን ስራ አስፈጻሚ