06/08/2026
ለዜጎች ሁለንተናዊ ፈውስ ዛሬን እንትከል!
አዲስ አበባ፦ ሐምሌ 30/2018 ዓ.ም (አማ/አእ/ስፔ/ሆ/ል)
አማኑኤል የአእምሮ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል በምዕራብ ሸዋ ዞን የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር አካሄደ።
"ጤናማ አእምሮ በለም አካባቢ ይለመልማል" በሚል መሪ ቃል አማኑኤል የአእምሮ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ ዞን ኤጀሬ ከተማ በ1.3 ሄክታር መሬት ላይ 5,000 ችግኞችን በመትከል አሻራውን አሳርፏል።
በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብሩ ላይ የአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ የበጎ ፈቃድ ስራ ወጣቶች፣ የኤጀሬ ከተማ አስተዳደር አመራሮች እንዲሁም የኤጀሬ ከተማ ከንቲባ በቦታው በመገኘት ችግኞችን በጋራ በመትከል የመርሃ ግብሩ ተሳታፊ ሆነዋል።
የመርሃ ግብሩ ተሳታፊዎች እንደገለጹት የተተከሉት ችግኞች ከሚሰጡት አጠቃላይ ሃገራዊ ጠቀሜታ ባለፈ ከፍተኛ ማህበረሰባዊ ቁርኝትና ትስስር የፈጠረ ነው ብለዋል።
ሆስፒታሉ ከ2015 ዓ.ም ጀምሮ በኤጀሬ ከተማ በቋሚነት የተለያዩ ሃገር በቀል ችግኞችን ሲተከል የቆየ ሲሆን አካባቢውን አረንጓዴ በማልበስ የአየር ንብረት ለውጥ የሚያስከትላቸውን ተፅዕኖዎች በመከላከል ላይ ይገኛል። "ጤናማ አእምሮ በለም አካባቢ" እንደሚለመልመው ሁሉ ለምለምና የተፈጥሮ ጸጋ የተሞላበት አካባቢ ለዜጎች ሁለንተናዊ የአእምሮና የአካል ጤና ፈውስ በመፍጠር እንዲሁም ለአካባቢው ማህበረሰብ ለምግብነት እና ለመድሃኒትነት አገልግሎት የሚውሉ የዛፍ ችግኞች መካተታቸው ደግሞ ጠቀሜታውን ከፍ ለማድረግ ያለመ መሆኑ ተመላክቷል።
የሰው ልጅ ከዕለት ወደ ዕለት ከሚያጋጥሙት ፈተናዎች መካከል የአየር ንብረት ለውጥ፣ የሀብት መመናመን እና የስነ-ምህዳር መዛባት ግንባር ቀደሞቹ ናቸው። ኢትዮጵያ ይህንን ዓለም አቀፍ ችግር በግንባር ቀደምነት ለመቋቋም ከቀረፀቻቸው ስትራቴጂካዊ እርምጃዎች መካከል «የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር» ቀዳሚውን ስፍራ ይይዛል። ይህ መርሃ ግብር የነገውን ትውልድ ደህንነት ለመጠበቅ ዛሬ የሚቀመጥ ቋሚ ማዕዘን ነው።
በመሆኑም ጤናማ ማህበረሰብን ለመገንባት የሕክምና አገልግሎት ብቻውን በቂ እንዳልሆነ የተገነዘበው አማኑኤል የአእምሮ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ከህክምና አገልግሎቱ ጎን ለጎን እንዲህ ያሉ ማህበራዊ ኃላፊነትና የአካባቢ ጥበቃ ስራዎችን አጠናክሮ እየሰራ ይገኛል፡፡ ሆስፒታሉ ጤናማ ማህበረሰብ እንዲኖር ጤናማ አካባቢ አስፈላጊ ነው ብሎም ያምናል።
በዚህም መሰረት ሆስፒታሉ በመጀመሪያው ምዕራፍ (ከ2015 ጀምሮ ለ3 ተከታታይ ዓመታት)፦ በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ ዞን ኤጀሬ ከተማ ከከተማ አስተዳደሩ ጋር በመቀናጀት በ50,000 ካሬ ሜትር መሬት ላይ 20,000 ለምግብነትና ለመድሃኒትነት የሚውሉ ሀገር በቀል የዛፍ ችግኞችን በማልማትና በመትከል የአየር ንብረት ፅናትን በማስጠበቁ ሂደት የበኩሉን ድርሻ አበርክቷል።
በአሁኑ ምዕራፍ (በ2018 ክረምት) ደግሞ እንደ ሀገር በአንድ ጀንበር 800 ሚሊዮን ችግኞችን የመትከል ግብን ለማሳካት በተያዘው ኢኒሼቲቭ ሆስፒታሉ በአራተኛው ዙሩ 5,000 ሀገር በቀል ለምግብነትና ለመድሃኒትነት አገልግሎት የሚሰጡ ችግኞችን በኤጀሬ ከተማ በ1.3 ሄክታር መሬት ላይ በመትከል ለትውልድ ተሻጋሪ የሆነ አሻራውን አሳርፏል።
ይህ ተግባር ሆስፒታሉ የማህበረሰብን አዕምሯዊ ጤና ከመጠበቅ ባሻገር የስነ-ምህዳር ሚዛንን በመጠበቅ በኩል ያለውን ከፍተኛ ኃላፊነት በግንባር ቀደምትነት ያሳየበት እና ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ልማት ሉዓላዊት ሃገር የመሆን ራዕይዋ እንዲሳካ የበኩሉን አሻራ ያሳረፈበት ድንቅ ምዕራፍ ነው።
የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የነገዋን ኢትዮጵያ ገጽታ የሚወስን ታላቅ ሀገራዊ ራዕይ ነው። በመሆኑም እንደ አማኑኤል የአእምሮ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ያሉ ተቋማት ከዕለት የዕለት የስራ አፈፃፀማቸው ባለፈ ለአካባቢና ስነምህዳር ደህንነት የሚያደርጉት አስተዋጽኦ የጋራ ሀገራዊ ግቦችን ለማሳካት ቁልፍ ሚና ያለው ሲሆን የዛሬው ትብብርና ትጋት ለነገው ትውልድ የሚተላለፍ የህይወት ውርስ ነው።