03/09/2026
ግሩፑ 227 ኩንታል ስንዴ ድጋፍ አደረገ
__________________________
የኢትዮጵያ ስኳር ኢንዱስትሪ ግሩፕ ለአገራዊ "ተረጂነትን የማስቀረት" ጥሪ 227 ኩንታል ስንዴ ድጋፍ በማድረግ ምላሽ ሰጥቷል፡፡
ከውጭ ዕርዳታ ጥገኝነት ለመላቀቅና ድጋፍ የሚሹ ዜጎችን ከአገር ውስጥ ሀብት በማሰባሰብ ድጋፍ ለማድረግ እንዲሁም በቀጣይነት ተረጂነትን ለማስቀረት ታስቦ በተጀመረው መርሐ ግብር ግሩፑ ሁለት ሚሊዮን ብር ወጪ በማድረግ የገዛውን የ227 ኩንታል ስንዴ ድጋፍ ዋና ሥራ አስፈጻሚው ክቡር አቶ ወዮ ሮባ ለልደታ ክፍለ ከተማ ወረዳ 10 ሥራ አስፈጻሚ አስረክበዋል፡፡
ክቡር ዋና ሥራ አስፈጻሚው በዚሁ ወቅት ባደረጉት ንግግር የመንግስት የልማት ድርጅቶች ከልማት ሥራዎቻቸው ጎን ለጎን ማሕበራዊ ኃላፊነታቸውን መወጣት አንዱ ተግባራቸው መሆኑን ገልጸው ግሩፑም ባለፉት ዓመታት በወረዳው በማዕድ ማጋራት፣ የአቅመ ደካሞችን መኖሪያ ቤት በማደስና ለትምህርት ቤቶች አስፈላጊ ግብአቶችን በማሟላት ይህንን ኃላፊነቱን ሲወጣ ቆይቷል ብለዋል፡፡
የስኳር ፋብሪካዎች በሚገኙባቸው አካባቢዎች ለሚገኙ ማሕበረሰቦችም ከትምህርት ቤት ግንባታ እስከ ቁሳቁስ ማሟላት፣ መሠረተ ልማትና ማሕበራዊ አገልግሎት መስጫ ተቋማት ግንባታ በማከናወን እና በኤችአይቪ ኤድስ ወላጆቻቸውን ያጡ ሕጻናትን እስከ ከፍተኛ ትምህርት ድረስ ተንከባክቦ በማስተማር ማሕበራዊ ኃላፊነቱን በመወጣት ላይ እንደሚኝም ክቡር አቶ ወዮ አስገንዝበዋል፡፡
የመንግስት አቅጣጫ የአገር ውስጥ አቅምን በማዳበር ችግሮች ሲከሰቱም ሆነ በቋሚነት ድጋፍ የሚሹ ዜጎችን መደገፍ መሆኑን ክቡር ዋና ሥራ አስፈጻሚው ጠቁመው በዚህ ዓመት የውጭ እርዳታ ጥገኝነትን ለማስቀረት ታስቦ በተጀመረው መርሐ ግብር ላይ ግሩፑ በመሳተፉ ደስተኛ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡
በልደታ ክፍለ ከተማ ወረዳ 10 ሥራ አስፈጻሚ አቶ ጀማል አብደላ በበኩላቸው ግሩፑ ያደረገው የ227 ኩንታል የስንዴ ድጋፍ ከተደረጉ ድጋፎች ከፍተኛውና የመጀመሪያው መሆኑን አስታውቀው ለዚሁም ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡
ግሩፑ ያደገረገው የስንዴ ድጋፍ በየወሩ እገዛ ለሚደረግላቸው አቅመ ደካማ ዜጎች እንደሚውል የወረዳው ዋና ሥራ አስፈጻሚ ገልጸው የግሩፑ የተጠናከረ ድጋፍ በቀጣይም እንደማይለያቸው እምነታቸውን ገልጸዋል፡፡