22/08/2026
የልደትና የሞት ዲጂታል ማሳወቂያ ሥርዓት ሲስተም በተጠናከረ መልኩ እንዲከናወን ሆስፒታሎች ላይ ምልከታ ተደረገ
CRRSA፡ነሐሴ16/2018ዓ.ም
የሲቪል ምዝገባ እና የነዋሪነት አገልግሎት ኤጀንሲ በ2019 በጀት ዓመት የተሟላ የኩነት ምዝገባ ለማድረግ በተመረጡ አራት ሆስፒታሎች ላይ ያስጀመረው የልደት እና ሞት ዲጂታል የማሳወቂያ ስርዓት ሲስተም ከባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን የደረሰበትን ደረጃ ምልከታ አድርገዋል፡፡
ከኢፌዴሪ ጤና ሚኒስቴር፣ከእስታስቲክስ አገልግሎት፣ከአዲስ አበባ ጤና ቢሮ፣ከዩኒሴፍ ፣ ከቫይታል ስትራቴጂ፣ከብሔራዊ መታወቂያ አገልግሎት(ፋይዳ) እንዲሁም ከኤጀንሲው የተውጣጡ እና በተመረጡ ሆስፒታሎች እየተተገበረ የሚገኘውን የልደት እና ሞት ዲጂታል የማሳወቂያ ስርዓት ሲስተም የተመለከቱት የቴክኒካዊ ቡድን አባላት ሲሆኑ አበረታች ውጤት መመልከታቸውን ተናግረዋል፡፡
ቴክኒካዊ ቡድኑ ባደረገው የሱፐር ቪዥን ምልከታ የተደረገባቸው የሚኒሊክ፣ዘውዲቱ እና ጋንዲ መታሰቢያ የሆስፒታል ኃላፊዎች ለጉዳዩ ትኩረት በመስጠት እየተሰራ እንደሚገኝ ገልፀዋል፡፡በሆስፒታሎቹ የሚከሰቱ ሁሉም ኩነቶች እንደሚመዘገቡ የተናገሩት የጤና ተቋማቱ ኃላፊዎች በቀጣይ ከሲቪል ምዝገባ እና የነዋሪነት አገልግሎት ኤጀንሲ ውጤታማ ስራ እንደሚሰራ የተናገሩ ሲሆን የሚመለከታቸው የጤና ባለሙያዎች የግንዛቤ ፈጠራ እና ቴክኒካዊ ስልጠናዎችን ወስደው ወደ ስራ መገባቱንም አክለዋል፡፡
የኤጀንሲው ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ጥጋቡ ሹመይ፣ በበጀት ዓመቱ በጤና ተቋማት የሚከሰቱ የልደትና የሞት ኩነቶችን በሙሉ በዲጂታል ሥርዓት በመመዝገብ ትክክለኛና አስተማማኝ የሕዝብ መረጃ ምንጭ ለመፍጠር ኤጀንሲው በትኩረት እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል።ይህም ሥርዓት ለሀገራዊ ፖሊሲና ዕቅድ ዝግጅት፣ ለስታቲስቲካዊ መረጃ አያያዝ እና ለተለያዩ የልማት ውሳኔዎች የሚያገለግል ታማኝ የመረጃ መሠረት ለመገንባት ወሳኝ ሚና እንደሚኖረውም አቶ ጥጋቡ አመልክተዋል።
የሲቪል ምዝገባ እና የነዋሪነት አገልግሎት ኤጀንሲ የሚሰጣቸውን አገልግሎቶች ፈጣን፣ቀልጣፋ እና በቴክኖሎጂ የተደገፉ አገልግሎቶችን ተደራሽ ለማድረግ ይቻል ዘንድ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ በተገኙበት የኦን ላይ አገልግሎት መስጫ ፖርታል እና የተቀናጀ የሲቪል እና ቤተሰብ ምዝገባ ስርዓት ሲስተም አስመርቆ ወደ ስራ መግባቱ ይታወሳል፡፡
ለበለጠ መረጃ፣ ጥቆማ ወይም ማብራርያ በተገልጋይ የስልክ መስመራችን 7533 ደውለው ያግኙን
የኦንላይን መመዝገቢያ ፖርታል https://portal.aacrrsa.gov.et
ዌብ ሳይት (website): https://www.aacrrsa.gov.et
ፌስቡክ (Facebook): https://www.facebook.com/profile.php?id=100064083391686
ቴሌግራም (Telegram): https://t.me/addisvaitalpress
ዩትዩብ (youtube)፡ https://www.youtube.com/
ቲክቶክ (TikTok): www.tiktok.com/
ኢንስታግራም (Instagram) https://www.instagram.com/aacrrsa_head_office/
ትዊተር (Twitter): https://x.com/CRRSA1935