03/09/2026
የኢ-ፍሊት ማኔጅመንት ስልጠና ለአመራሮች ተሰጠ።
*********
በተሽከርካሪ ሥምሪት እና አጠቃቀም የሚባክነውን ሃብት ለመቆጣጠር የሚያስችል የኢ-ፍሊት ማኔጅመንት ትግበራ በፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ለማስጀመር ለፍርድ ቤቱ የማኔጅመንት አባላት፣ የየምድብ ችሎት ተጠሪ ዳኞች እና የስራ ክፍል ዳይሬክተሮች ነሐሴ 27 እና 28 ቀን 2018 ዓ.ም ከመንግስት ግዥ እና ንብረት ባለስልጣን በመጡ ባለሙያዎች ስልጠና ተሰጠ።
የመንግስት ግዥ እና ንብረት ባለስልጣን የኢ-ፍሊት ማኔጅመንትን (e-Fleet Management) በተለያዩ ተቋማት በሙከራ ትግበራ በማረጋገጥ በሁሉም የፌደራል ተቋማት ተግባራዊ እንዲደረግ በተወሰነው መሰረት በፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤቱም ተግባራዊ ለማድረግ ስልጠናው መዘጋጀቱን አቶ ተስፋዬ ከበደ የፍርድ ቤቱ የህንፃ አስተዳደር እና ጠቅላላ አገልግሎት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተሩ በስልጠናው መክፈቻ ተናግረዋል።
ስልጠናውን የሰጡት የመንግስት ግዢ እና ንብረት ባለስልጣን ባለሙያዎች አቶ ኢሳያስ መንግስቱ ሲኒየር አፕሊኬሽን ዲቨሎፐር እና አቶ አለምሸት ክንፈ የኢጂፒ ድጋፍ ሰጪ ባለሙያ ሲሆኑ ሲስተሙ ፍርድ ቤቱን ወደ ዘመናዊ፣ ዲጂታል እና ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችል የአሰራር ስርዓት እንዲዘረጋ ከመርዳቱ በተጨማሪ ኢ-ፍሊት ማኔጂመንት ሲስተምን መጠቀም ግልፅ እና ወቅቱን የጠበቀ ሪፖርት ለማግኘት፣ የወረቀት ስራዎችን ለማስቀረት፣ ከሰዎች ንኪኪ ነፃ የሆነ አሰራር ስርዓት ለመዘርጋት፣ የተጠቃሚዎች ጊዜን ለመቆጠብ እንዲሁም የነዳጅ ዘይት እና ቅባት ወጪን ለመቆጣጣር እና ለተሸከርካሪ የሚወጣዉን ወጪ ለማወቅ የሚያስችል አሰራር መሆኑን ገልፀዋል፡፡ እንደ አሰልጣኞቹ ገለፃ ኢ-ፍሊት ማኔጅመንት ክንውኖችን በጥራት፣ በብቃት፣ በሰዓት እና በበጀት መጥኖ መፈፀም የሚያስችል ዘመናዊ የአሰራር ስርአት እንደሆነ በተለይም የተሽከርካሪ ንብረት አጠቃቀም፣ አያያዝ፣ የግዥ ሂደት እና አወጋገድን በተመለከተ የላቀ ጠቀሜታ ያለው የአሰራር እና ቁጥጥር ስርአት መሆኑ ተገልጿል።
መንግስት የግዥ ስርአቱን ቴክኖሎጂን በመጠቀም ወደ ዲጂታላይዜሽን ስርአት በማስገባት ኢጂፒ (e-GP) ተግባራዊ እንደተደረገ ሁሉ በተመሳሳይ በተሽከርካሪ ሥምሪት እና አጠቃቀም የሚባክነውን ሃብት ለመቆጣጠር የሚያስችል በባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ የለማ የኢ-ፍሊት ማኔጅመት ሲስተም መተግበሪያን ተግባራዊ በማድረግ የተሽከርካሪ ሥምሪት እና አጠቃቀምን ከማሻሻል ባለፈ የሃብት ብክነትን ለማስቀረት እየተጋ መሆኑ ተነግሯል።
ኢ-ፍሊት ማኔጅመንት ሲስተም ከተሽከርካሪ ጥገና እና ነዳጅ ጋር የተያያዙ ችግሮችን ለመፍታት ሁነኛ መፍትሄ መሆኑን በመግለፅ ለግልጽ አሰራር እና የሃብት ክትትል መተግበሪያውን በአግባቡ በመጠቀም ለአሰራሩ ውጤታማነትም አስፈላጊውን ሁሉ እገዛ እና ትብብር በስልጠናው የተገኙ ኃላፊዎች በማድረግ በተገቢው ወደ ስራ እንዲገባ በስልጠናው ተገልፆል።
ስልጠናው ከነሐሴ 29 እስከ ጳጉሜ 1 ቀን 2018 ዓ.ም ለሹፌሮች፣ ለዳይሬክተሮች ፀሃፊዎች እና በትራንስፖርት ስምሪት ቡድን መሪ ስር ላሉ ሁሉም ባለሙያዎች የሚሰጥ ይሆናል።