28/08/2026
ከህመም ስጋት ወደ ሙሉ ተስፋ፡ የ70 ዓመቷ ወይዘሮ አብረሀት ገብረ የህይወት ምስክርነት
22/12/2018 ዓም ኢጤመአ
እድሜ እየገፋ ሲሄድ ከሰውነት አቅም መዳከም ጋር ተያይዞ የተለያዩ ህመሞች የመከሰታቸው አጋጣሚ ከፍተኛ ነው፡፡ በተለይም በቋሚ ገቢ ላይ ላልተመሰረቱና ዝቅተኛ የኢኮኖሚ አቅም ላላቸው አዛውንቶች ድንገት የሚከሰት የጤና መታወክ ህይወትን ለከባድ አደጋ ከማጋለጡ ባሻገር፣ የቤተሰብን ምጣኔ ሀብት ምስቅልቅሉን ያወጣዋል፡፡ ሆኖም ይህንን የህክምና ወጪ ስጋት በዘላቂነት በመቅረፍ ረገድ የማህበረሰብ ዓቀፍ ጤና መድኅን አገልግሎት ለአያሌ ዜጎች ትልቅ የህይወት አለኝታ እየሆነ ይገኛል፡፡
በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በልደታ ክፍለ ከተማ ወረዳ 3 ነዋሪ የሆኑት የ70 ዓመቷ አዛውንት ወይዘሮ አብረሀት ገብረ፣ የዚሁ ተስፋ ሰጪ ስርዓት እውነተኛ ተጠቃሚ ምስክር ናቸው፡፡
ወይዘሮ አብረሀት ከእድሜ መገፋት ጋር ተያይዞ ከቆዩባቸው የወገብ ህመም፣ የደም ግፊት እና የኮሌስትሮል ችግሮች ጋር ትግል ሲያደርጉ ቆይተዋል፡፡ እነዚህ ህመሞች ደግሞ ተከታታይነት ያለው የህክምና ክትትልና የመድኃኒት አቅርቦት የሚሹ በመሆናቸው፣ በየጊዜው የሚጠየቀውን የህክምና ወጪ መሸፈን ለእሳቸው እጅግ አታካችና ከአቅም በላይ የሆነ ፈተና ነበር፡፡ "እድሜ ሲገፋ የመስራት አቅም ይቀንሳል፤ የመስራት አቅም ሲቀንስ ደግሞ ገቢ አብሮ ያንሳል" የሚሉት ወይዘሮ አብረሀት፣ በራሳቸው የኢኮኖሚ አቅም ብቻ ተደጋጋሚ የህክምና ወጪዎች መሸፈን እንደማይችሉ በቁጭት ያስታውሳሉ፡፡
ሆኖም የማህበረሰብ ዓቀፍ ጤና መድኅን አባል ከሆኑበት ጊዜ ጀምሮ ያጋጠማቸው የፋይናንስ ስጋት ሙሉ በሙሉ ሊቀረፍ ችሏል፡፡ አሁን ላይ በቅርባቸው በሚገኘው በአብነት የመጀመሪያ ደረጃ ህክምና መስጫ ማዕከል በመገኘት አስፈላጊውን የህክምና ክትትልና መድኃኒት በሙሉ ጥራትና ያለ ምንም የገንዘብ ስጋት በማግኘት ላይ ይገኛሉ፡፡
አዛውንቷ ወይዘሮ አብረሀት ስለ ጤና መድኅን ጠቅሜታ ሲናገሩ «ጤና መድኅን ለእኔ ነፍሴ ነው!» በማለት በከፍተኛ ስሜትና ምስጋና ይገልጻሉ። የማህበረሰብ ዓቀፍ ጤና መድኅን አባል በመሆናቸውና በመደገፋቸው ምክንያት፣ ህይወታቸው ሊረዝምና በሙሉ ጤንነት እንዲኖሩ እንደረዳቸው በደስታ ያስረዳሉ፡፡
ህመም አቅዶና አውጥቶ እንደማይመጣና መቼ እንደሚከሰት የማይታወቅ በመሆኑ፣ እያንዳንዱ ዜጋ ነገን ሳይጠብቅና ጊዜ ሳይሰጥ የአባልነት ምዝገባውን ማጠናቀቅ እንዳለበት ይመክራሉ፡፡
በአጠቃላይ የሦስትዮሽ ትስስር ያለው የማህበረሰብ መደጋገፍ፣ ጥራት ያለው የህክምና አገልግሎት እና የዜጎችን ህይወት የመታደግና የማራዘም አቅሙ የጎላ መሆኑን የወይዘሮ አብረሀት ገብረ የህይወት ታሪክ ግልጽ ማረጋገጫ ነው፡፡
"Youtube: https://www.youtube.com/-HealthInsurance
Website: www.ehis.gov.et
Twitter: http://twitter.com/service4E
Facebook: https://web.facebook.com/EthioHIS/
Telegram: https://t.me/buuu1lTelegram: https://t.me/buu