23/08/2026
በፕሮጀክቶች የሚታዩ የአፈጻጸም ስብራቶችን በመቅረፍ ተወዳዳሪና ውጤታማ ኢንዱስትሪ መገንባት ዓላማችን ነው ተባለ
ነሐሴ 16 ቀን 2018 ዓ.ም. / አዲስ አበባበ
በፕሮጀክቶች የሚታዩ የአፈጻጸም ስብራቶችን በመቅረፍ ውጤታማና ተወዳዳሪ የግንባታ ኢንዱስትሪ መገንባት ዓላማችን ነው ሲሉ የኮንስትራክሽን ማኔጅመንት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ታማራት ሙሉ ገለጹ።
ዋና ዳይሬክተሩ ይህን የገለጹት የኮንስትራክሽን ማኔጅመንት ኢንስቲትዩት ከሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ጋር በመተባበር ለተከታታይ 6 ቀናት በፕሮጀክት ማኔጅመንት ፕሮፌሽናል (Project Management Professional) ላይ ያተኮረ ስልጠና በተጠናቀቀበት ወቅት ነው።
ኢንጂነር ታምራት በንግግራቸው፣ ውስብስብ የሆኑ የሀገራችን ፕሮጀክቶች በብቃት፣ በጥራትና በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲጠናቀቁ የሀገር ውስጥ የሥራ ተቋራጮች አሁን በውጭ ተቋራጮች ተይዘው የሚገኙ ሥራዎችን በብቃት ለመረከብ የሚያስችላቸውን አቅም ማሳደግ እንደሚገባቸው ጠቁመዋል።በተጨማሪም በግንባታ ዘርፉ የሚስተዋሉ የአፈጻጸም ስብራቶችን በመቅረፍ በሌሎች የዓለም አገራት እየታየ ያለውን ውጤታማና ተወዳዳሪ የፕሮጀክት አፈጻጸም በሀገራችን ማስመዝገብ የኢንስቲትዩቱ ዋነኛ ዓላማ መሆኑን አስገንዝበዋል።
ስለሆነም ሰልጣኞች በዚህ ደረጃ ተወዳዳሪና ውጤታማ የግንባታ ኢንዱስትሪ ለመገንባት እየተደረገ ያለውን ጥረት በእውቀትና በተግባር ማገዝ እንዳለባቸው አሳስበዋል።
በሌላ በኩል፣ ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕን በመወከል በስነ-ሥርዓቱ ላይ የተገኙት የአቅም ግንባታና አሠራር ሥርዓት ዳይሬክተር ወ/ሮ ማናለብሽ ዳኘው ናቸው።ወ/ሮ ማናለብሽ ባደረጉት ንግግር፣ የተቋሙን አመራሮችና ባለሙያዎች በዘመናዊ የፕሮጀክት አመራር ብቁ ለማድረግ ታስቦ ስልጠናውን ላዘጋጀው ኢንስቲትዩት ምስጋና አቅርበዋል።
የስልጠናው ዋነኛ ዓላማ የሚመሩትን ፕሮጀክቶች ዘመናዊ የፕሮጀክት አመራር መርሆችን በመከተል ውጤታማ ማድረግ መሆኑን ገልጸዋል። ለዚህም እያንዳንዱ ሰልጣኝ ራሱን በማዘጋጀት በሥራ ላይ ውጤታማ ተግባር መፈጸም እንዳለበት አሳስበዋል።
“ይህን በማድረግ ከዘመኑ ጋር መራመድ ይቻላል” በማለትም ገልጸዋል።
በስልጠናው የተሳተፉ ሰልጣኞችም የተሰጣቸው ስልጠና ጥሩ ግንዛቤ ያስጨበጠና ለሥራቸው ጠቃሚ የሆነ እውቀት ያገኙበት መሆኑን ገልጸዋል። ሆኖም የስልጠናው ጊዜ አጭር መሆኑን ጠቁመዋል።
በመጨረሻም ስልጠናውን በተገቢው ሁኔታ ተከታትለው ላጠናቀቁ ሰልጣኞች የምስክር ወረቀት በመስጠት የዕለቱ መርሐ ግብር ፍጻሜውን አግኝቷል።