29/05/2026
ብሔራዊ የአቮካዶ ልማት ፕሮግራም ለአቮካዶ ምርታማነት ዕድገት!
አዲስ አበባ፣ ግንቦት 21/2018 (ግብርና ሚኒስቴር) ብሔራዊ የአቮካዶ ልማት ፕሮግራም ሃገራችን ከአቮካዶ ምርት የምታገኘውን የውጭ ምንዛሬ ለማሳደግ ትልቅ አቅም ይፈጥራል።
ይህ ፕሮግራም ከሌሎች ሀገራዊ እና ዓለማቀፋዊ የልማት ግቦች ጋር እንዲጣጣም ተደርጎ የተቀረፀ ሲሆን በዚህም የሀገራችንን ኢኮኖሚ ለማሳደግ፣ የህብረተሰባችንን ኑሮ ለማሻሻል እና የምግብና ስርዓተ-ምግብ ዋስትናን ለማሳደግ እንዲሁም ለአግሮ-ኢንዱስትሪ በቂ ጥሬ ዕቃ ለማቅረብ ትልቅ አቅም እንዲኖረው ተደርጎ የተቀረፀ ነው።
በዚህም ፕሮግራሙ እየተተገበረ በሚገኝባቸው ክልሎች ያለውን አፈፃፀም በመገምገም ውሳኔ በሚሹ ጉዳዮች ላይ ከክልል ከፍተኛ አመራሮችና ከባለድርሻ አካላት ጋር በዛሬው ዕለት ውይይት ተደርጓል፡፡
በግብርና ሚኒስቴር የእርሻ እና ሆርቲካልቸር ልማት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ደሳለኝ ተሻለ እንደተናገሩት፤ ይህ ፕሮግራም ሀገራችን የሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያ ፕሮግራሞችን ከጀመረችባቸው ዘርፎች አንደኛው ተደርጎ የሚወሰድና በግንባር ቀደምትነት ትኩረት ተሰጥቶት በመንግስት ከፍተኛ በጀት የሚሰራ ስራ ነው።
ብሔራዊ አቮካዶ ልማት ፕሮግራም ከአረንጓዴ አሻራ፣ ከሌማት ትሩፋት እንዲሁም ሌሎች ሀገራዊ ኢኒሼቲቮች ጋር በማቆራኘት ይበልጥ ውጤታማ እንዲሆን ተደርጎ መቀረፁን አንስተው፣ ሀገራችንም ከዘርፉ ማግኘት ያለባትን የውጭ ምንዛሬ፣ የስራ እድል ፈጠራና መሰል ጉዳዮችን መነሻ በማድረግ የተዘጋጀና ለ15 ዓመት የሚቆይ ፕሮግራም መሆኑንም ሚኒስትር ዴኤታው አብራርተዋል።
የእርሻና ሆርቲካልቸር ልማት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ አማካሪ ፕሮፌሰር አሊ መሃመድ የአቮካዶ እሴት ሰንሰለት አለም አቀፋዊ እና ሀገራዊ እይታ፣ ስትራቴጂካዊ ጠቀሜታና ዕድሎች እንዲሁም የሆርቲካልቸር ዘርፍ ለውጥ ላይ ትኩረት ያደረገ ጽሁፍ አቅርበዋል።
በምግብና ስርዓተ-ምግብ ራሳችንን ለመቻል፣ ለኢንዱስትሪዎች የጥሬ እቃ አቅርቦት እንዲሁም ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ ግኝትን ለማሳደግ አቮካዶ ከፍተኛ ሚና እንደሚጫወት አማካሪው ባቀረቡት ጽሁፍ አብራርተዋል።
በተጨማሪም ብሔራዊ የአቮካዶ ልማት ፕሮግራም አጠቃላይ እይታ፣ በበጀት ዓመቱ የተመዘገቡ ስኬቶች፣ ተግዳሮቶች እና የወደፊት ስትራቴጂያዊ አቅጣጫዎች እንዲሁም ገበያ ተኮር የሆነ ክላስተር ላይ የተመሰረተ አቮካዶ ምርትን በተመለከተ ጽሁፍ ቀርቦ ሰፊ ውይይት ተደርጎበታል።
ዘጋቢ፦ ሰለሞን ደምሰው
ፎቶ፦ ማቲዎስ ተገኝ
#ከማምረትበላይ
-----------------
በተለያዩ የማህበራዊ ሚዲያ አማራጮች ስለግብርና ወቅታዊ መረጃዎችን ለማግኘት👇
📌ድረ-ገጽ፦ www.moa.gov.et
******
📌ፌስቡክ፦ https://www.facebook.com/MoAEthiopia
******
📌ዩቲዩብ፦ https://youtube.com/-ethiopia
******
📌ቴሌግራም፦ https://t.me/MoAEthiopianews
******
📌ቲዊተር፦ https://x.com/MoA_Ethiopia
*****
📌ሊንክድኢን፡- https://shorturl.at/7O6cs
******
📌ቲክቶክ፦ http://www.tiktok.com/
******
📌ኢንስታግራም፦ https://www.instagram.com/moa_ethiopia/