26/08/2026
የሀገራዊ ምክክር ጉባኤ ሒደት እና ፍጻሜን አስመልክቶ
ከኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትኅ ( #ኢዜማ ) የተሰጠ መግለጫ
ሀገራችን ኢትዮጵያ ላለፉት ዘመናት በርካታ ፖለቲካዊ ቀውሶች ውስጥ አልፋለች። እነዚህ ዘመናትን የተሻገሩ ውስብስብ ችግሮቻችን፣ ሀገራዊ ህልውናችንን አደጋ ላይ የሚጥሉ፣ የዜጎችን ሰብአዊና ዜጋዊ ደኅንነት የሚሸረሽሩ፣ ከድህነትና ከኋላቀርነት እንዳንወጣ የሚያደርጉ እንዲሁም እንደሀገር የጋራ ማንነት፣ ጥቅም፣ ፍላጎትና ስሜት እንዳናዳብር ያደረጉ ዋነኛ ማነቆዎች ሁነው የቆዩ መሆናቸውን እንገነዘባለን። ፓርቲያችን ኢዜማ ለህዝብ ይፋ ካደረጋቸው መሠረታዊ አቋሞቹ መካከል አንዱና ዋነኛው ሀገራችንን ከግጭት እና የኋላቀርነት አዙሪት ማውጣት የሚቻለው በሰለጠነ ምክክር ብቻ ነው የሚለው እውነት ነው።
ኢዜማ ሀገራዊ ምክክር ሀሳቡ ከተጠነሰሰበት ቀን ጀምሮ በከፍተኛ ሀገራዊ ኃላፊነት፣ በንቃት እና በሙሉ ቁርጠኝነት ሲሳተፍ ቆይቷል። የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን የማቋቋሚያ አዋጁ ሲዘጋጅ የሕጉ መንፈስና ይዘት የምንመኘውን ሀገራዊ ግብ ማሳካት በሚችል ጥልቀት እንዲቀርፅ የምክረ-ሐሳብ በማቅረብ በንቃት ተሳታፊ ነበርን። አዋጁ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሲፀድቅና ኮሚሽነሮች ሲሰየሙ፣ ገለልተኛና ብቁ የሆኑ አካላት ወደ ኃላፊነት እንዲመጡ ኢዜማ የራሱን አዎንታዊ ድርሻ አበርክቷል።
የሀገራዊ ምክክሩ ጉባኤ ከመካሄዱ ቀደም ብሎ፣ ሀገራዊ ችግሮቻችንን ለመፍታት ያስችላሉ ያልናቸውን የምክክር አጀንዳዎች በማዘጋጀት ለሕዝብ ያሳወቅን ሲሆን፣ ለሀገራዊ ምክክር ኮሚሽኑም በይፋ አስረክበናል። ኢዜማ ሀገራዊ ምክክሩን በሚመለከት የጋራ ግንዛቤ ለማዳበር እንዲረዳ ያዘጋጀው ሰነድ ውስጥ የሀገር ሕልውና እና ቀጣይነት አደጋ፣ የዜጎች ሰብዓዊና ዜጋዊ ደህንነታቸው መከበር አለመቻል፣ ከድህነትና ከኋላቀርነት መላቀቅ አለመቻል፣ እንዲሁም የጋራ ማንነት፣ ጥቅም፣ ፍላጎትና ስሜት አለመዳበር የሚሉ አንኳር ነጥቦችን ያካተተ ነበር።
ሀገራችን ኢትዮጵያ በርካታ ማንነቶች፣ ጥቅሞች፣ ፍላጎቶች እና ስሜቶች በሚንጸባረቁበት ውስብስብ ሀገራዊ ሁኔታ ውስጥ የምትገኝ በመሆኑ፣ ይህንን ፈታኝ ሁኔታ መወጣት የምንችለው በአርቆ አሳቢነት፣ በሆደ-ሰፊነት፣ በከፍተኛ እውቀት እና ብልሃት የታገዘ ንቁ ተሳትፎ ከማድረግ ውጪ ሌላ ለሀገር የሚበጅ የተሻለ አማራጭ እንደሌለን ታሳቢ አድርገናል። በሀገራዊ ምክክሩ በተመለከተ የምናቀርበው ምክረ ሃሳብና የምንወስነው ውሳኔ ከኛ ከራሳችን የቡድንም ሆነ የግል ጥቅምና ፍላጎት ይልቅ የሀገራችን የኢትዮጵያን ዘላቂ ጥቅምና ፍላጎት የሚያስቀድም ሊሆን ይገባል ብለን በምንችለው ሁሉ ሠርተናል።
ሀገራዊ ምክክሩ በይፋ ከተጀመረበት ሐምሌ 08 ቀን 2018 ዓ.ም. ጀምሮ ባለው ረጅም እና እልህ አስጨራሽ ሂደት ውስጥ በርካታ ስልታዊ ማነቆዎችና አሠራርን ያላከበሩ ችግሮች ባጋጠሙን ወቅት፣ ሂደቱ እንዳይበላሽ በማሰብ ጉዳዩን ወደ አደባባይ ከማውጣት ይልቅ ለኮሚሽኑ ምክር ቤት ቅሬታዎቻችንን በተደጋጋሚ ያቀረብን ሲሆን፣ በአካልም ከኮሚሽኑ ከፍተኛ አመራሮች ጋር በመወያየት የማረሚያ ሀሳቦችን አቅርበናል። በርካታ ችግሮችንም በዚሁ መንገድ ፈትተናል።
እንደማሳያም አንዳንድ በኤክስፐርትነት እና በአስተባባሪነት ስም የተመደቡ አካላት በምክክሩ ሂደት ያንጸባርቁት የነበረውን ግልጽ ወገንተኛነት እና የተዛባ አካሄድ በጽናት እየተከላከልን፣ ሂደቱ ሀገራዊ ተስፋን እንዳያከስም በሚል እምነት እስከ ፍጻሜው ለማድረስ ከፍ ያለ ዋጋ ከፍለናል።
እንደ ኢዜማ ሀገራዊ ምክክሩ በይፋ ከተጀመረበት እለት አንስቶ በይፋ እስከተጠናቀቀበት እለት ድረስ በከፍተኛ ሀገራዊ ኃላፊነት ንቁ ተሳትፎ ስናደርግ የቆየን ሲሆን ችግሮች ተከስተዋል ብለን ባመንንበት ግዜ ሁሉ ለኮሚሽኑ የእርምት እርምጃዎች እንዲወሰዱ በማሳሰብ እና መተግበራቸውን ጭምር በመከታተል ሂደቱ ትርጉም እንዲኖረው የበኩላችንን አስተዋፅኦ ተወጥተናል ብለን እናምናለን።
በምክክሩ ማጠናቀቂያ እለት ማለትም ነሐሴ 13 ቀን 2018 ዓ.ም. ለሁሉም የሥራ ቡድኖች (ለ4000 ተመካካሪዎች) የስምንቱም አጀንዳዎች ምክረ-ሐሳቦች በንባብ የቀረቡ ሲሆን፣ ኢዜማ በ8ቱ የምክክር ቡድኖች በጥቅሉ ተመካካሪዎች በውይይት አጎልብተውት፣ በሙሉ ድጋፍ ፈርመውበት ለጠቅላላው ጉባኤ ያቀረቧቸውን ምክረ-ሐሳቦች ብቻ የሚቀበላቸው መሆኑን እንገልጻለን።
በአጠቃላይ ሀገራዊ ምክክሩ የነበረው ሐደት ከነጉድለቶቹም ቢሆን እንደ መልካም ጅምር የምንወስደው እና ወደፊትም በሀገራችን ያሉትን ቀሪ ችግሮች በተመሳሳይ ከጠብመንጃ አፈሙዝ ውጪ በሆነ መልኩ በጠረጴዛ ዙሪያ ብቻ መፍታትን ልማድ እንድናዳብር አዲስ በር የሚከፍት መልካም ጅማሬ አድርገንም እንወስደዋለን።
የምክክር ሒደቱ የመመካከሪያ ምዕራፉ ቢጠናቀቅም የሒደቱ ወሳኝ ምዕራፍ የሆኑት በኮሚሽኑ የመጨረሻውን ምክረ ሀሳቦች ለመንግሥትና ለህዝብ የሚያቀርቡበት ሂደት እና የትግበራ ሂደት ገና ይቀራል። እነዚህ ሁለት ዋና ምዕራፎችም በጥንቃቄ እንዲያዙ ኢዜማ የሚከተሉትን አምስት ማሳሰቢያዎች መስጠት ይወዳል፡፡
1. የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ለመንግሥትና ለሕዝብ የመጨረሻ ምክረ ሀሳቦችን በሚያቀርብበት ወቅት በአጠቃላይ የምክክሩን መንፈስ እና የተመካካሪዎችን በንባብ የቀረበውን የመጨረሻ ምክረ-ሀሳብ ብቻ ባከበረ መልኩ እንዲሆን፤
2. ኮሚሽኑ በተመካካሪዎች የቀረቡትን 400 ምክረ ሀሳቦች ለህዝብ ይፋ እንዲያደርግ ፤
3. በምክክሩ ሒደት ከጥቃቅን ቡድኖች ጀምሮ ያደረግናቸውን ውይይቶች ቃለጉባዔዎች በማገናዘብ እንዲከወን፤ እንዲሁም በማቋቋሚያ አዋጁ መሰረት የምክረ ሀሳቦቹን አፈፃፀም እንዲከታተል፤
4. መንግሥት የሀገራዊ ምክክሩ ሂደት ውጤታማ የሚሆነው የቀረቡት ምክረ ሀሳቦች ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ ሲደረጉ እንደመሆኑ አፈፃፀሙም ከተገቢው በላይ ግዜ እንዳይወስድ በፍጥነት እንዲፈፀም እንዲያደርግ ፤
5. የሀገራዊ ምክክሩ ምክረ ሃሳቦችን አተገባበር የሚከታተል ገለልተኛ እና ሕጋዊ አካል አንዲቋቋም እንጠይቃለን።
በመጨረሻም ሀገራዊ ምክክሮችን በማድረግ ልዩነቶቻችንን በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት የምናደርገው ሒደት ተጠናክሮ መቀጠል ያለበት መሆኑን፤ በዚህ ረጅም ሀገራዊ ምክክር ውስጥ የተስተዋሉ የሒደት ጉድለቶች ቢኖሩም እንኳን በመጨረሻ የመጣው ውጤት የሚያበረታታ፤ ተስፋ ሰጪ እና የመመካከርን አስፈላጊነት በጉልህ ያሳየ፣ እንደ ሀገርም በጣም ጠቃሚ ፣ እንደ ፓርቲም ብዙ የተማርንበት መሆኑን ለመግለፅ እንወዳለን።
የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ)
ነሐሴ 20 ቀን 2018 ዓ.ም.