05/06/2026
“የማር ምርታማነትን ለማሳደግ የንብ ማነብ ሥራን ማዘመንና የከተማ ግብርናን ማጠናከር ወሳኝ ነው”
ፓዌ - ግንቦት 28/2018 ዓ.ም
የፓዌ ግብርና ምርምር ማዕከል የማር ምርታማነትን ለማሳደግ የንብ ማነብ ሥራን ማዘመን፣ እንዲሁም የከተማ ግብርናን አካቶ በዘርፉ መሥራት ወሳኝ መፍትሔ መሆኑን አስታወቀ።
ምርምር ማዕከሉ በመተከል ዞን ፓዌ ከተማ 02 ቀበሌ ለሚገኙ አዲስ የተደራጁ አርሶ አደሮች እና የግብርና ባለሙያዎች የአቅም ግንባታ ሥልጠና ሰጥቷል። ሥልጠናው የንብ ማነብ ዕውቀትና ክህሎትን በማሳደግ፣ ባህላዊ አሠራርን ወደ ዘመናዊ ቴክኖሎጂ ለመቀየር እና የከተማ ግብርናን ለማጎልበት ያለመ ነው።
የፓዌ ግብርና ምርምር ማዕከል ዳይሬክተር አቶ ደስታ አበበ እንደገለጹት፣ ንብ ማነብ ለዜጎች ተጨማሪ የገቢ ምንጭ ከመሆኑ ባሻገር ለምግብ ዋስትና፣ ለሰብል ምርታማነት መጨመር እና ለአየር ንብረት ጥበቃ ከፍተኛ ሚና አለው ብለዋል። በተለይም የከተማ ግብርናን በንብ ማነብ ስራ በማቀናጀት፣ የከተማ ነዋሪዎች ባላቸው ውስን ቦታ ሳይቀር ምርታማ መሆን እንደሚችሉና ለምግብ ዋስትናው ትልቅ አስተዋጽኦ ማበርከት እንደሚችሉ አጽንኦት ሰጥተዋል።
የእንስሳት ዝርያ ማሻሻል ከፍተኛ ተመራማሪ አቶ ሀብቴ አረጋ በበኩላቸው፣ ማዕከሉ ያለውን ክፍተት በመለየት ዘላቂ መፍትሔ ለመስጠት እየሠራ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም መሰረት ምርታማነትንና ጥራትን ለማሳደግ የተሻሻሉ ዘመናዊ የቀርከሃ ቀፎዎች እና የንብ ቀሰም እፅዋት ቴክኖሎጂዎችን ምርምር ማዕከሉ በማስተዋወቅ ማህበረሰቡን ተጠቃሚ እያደረገ እንደሚገኝም አስረድቶል።
እነዚህ ቴክኖሎጂዎች በገጠር ብቻ ሳይሆን በከተማ ግብርና መዋቅር ውስጥም በቀላሉ ተግባራዊ የሚደረጉ ናቸው ብለዋል።
የፓዌ ወረዳ ግብርና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ አይቸው ሞገስ እንደገለጹት፣ አርሶ አደሮች እና የከተማ ግብርና ተሳታፊዎች የቴክኖሎጂ ድጋፉን ተቀብለው ወደ ተግባር እንዲገቡ ከቀበሌ እስከ ወረዳ ባሉ የግብርና ባለሙያዎች በኩል አስፈላጊው ክትትልና ድጋፍ ይደረጋል ብለዋል።
በመጨረሻም ምርምር ማዕከሉ ከዘርፉ ተገቢውን ጥቅም ለማግኘት፣ ከንብ አናቢዎች፣ ማኅበራት፣ ተቋማት እና የከተማ ግብርና ተሳታፊዎች ጋር በቅንጅት እንደሚሠራ አረጋግጧል።