05/09/2026
''ጎቤና ሺኖዬ'' የወጣቶች የባህላዊ ጭፈራ መርሃ ግብር በጉለሌ ክፍለ ከተማ አስተዳደር ተካሄደ።
በክፍለ ከተማው ''ጎቤና ሺኖዬ'' የወጣቶች የባህላዊ ጭፈራ መርሃ ግብር የባህሉ ባለቤት የሆኑ ወጣቶች ፣ የክፍለ ከተማው አመራሮች ሌሎች እንግዶች በተገኙበት በደመቀ ሁኔታ ተከብሯል።
የክረምቱ ዝናብ አልፎ መሬቱ በአበቦችና በለመለሙ ተክሎች ይሸፈናል። ወጣቶችም ከክረምቱ የሥራ ጊዜ ዕረፍት አግኝተው፣ ተፈጥሮ ይዞት የመጣውን አዲስ ተስፋ ይቀበላሉ።
በዚህም አዲስ ተስፋ፣ ደስታና ብሩህ ፊት ይዘው ወደ ሜዳ በመውጣት በዓል ያከብራሉ። ይህንን ባህላዊ በዓል ጎቤ እና ሺኖዬ ብለው ይጠሩታል።
ጎቤ እና ሺኖዬ በኦሮሚያ ክልል በተለያዩ አካባቢዎች የሚከበሩ ሲሆን፤ አከባበራቸውም እንደ የአካባቢው በተለያየ መልኩ ይከናወናል።
በኦሮሞ ባህል ከትውልድ ወደ ትውልድ ሲተላለፍ የመጣው ጎቤ እና ሺኖዬ፣ በተለይም በበልግ ወቅት ወጣቶች ባህላዊ ልብስ በመልበስ፣ በባህላዊ ዘፈንና ጨዋታ በመሳተፍ ደስታቸውንና መልካም ምኞታቸውን የሚገልጹበት ሥርዓት ነው።
እነዚህ ባህላዊ ጨዋታዎች የኦሮሞን ታሪክና ማንነት ለአዲሱ ትውልድ ከማስተላለፍ ባለፈ፤ እየተረሳ የመጣውን ባህል ለመመለስ፣ ማኅበራዊ ትስስርን ለማጠናከርና የኦሮሚያን የቱሪዝም ማራኪነት ለማሳደግ ከፍተኛ ሚና አላቸው።
ወጣት ወንዶችና ሴቶች የወረሃ መስከረም መጥባትን በምስጋና፣ በልዩ ልዩ ዜማዎችና ዘፈኖች ይቀበላሉ።
ሴቶች ወረሃ መስከረምን በሺኖዬ፣ ወንዶች ደግሞ በጎቤ በመግለጽ፣ ለፈጣሪና ለተፈጥሮ ያላቸውን ምስጋና፣ ተስፋና ደስታ ያሳያሉ።
የጎቤ ሥርዓት ከክረምቱ ዝናብ ወደ ብራ ወቅት የሚደረገውን ሽግግር የሚያመለክት ሲሆን፣ ይህም ከክረምት ወደ በጋ ለሚደረገው ሽግግር ፈጣሪን የሚያመሰግኑበት ሥርዓት ነው።