FDRE Ministry of Justice/ የኢ.ፌ.ዲ.ሪ. ፍትሕ ሚኒስቴር

FDRE Ministry of Justice/ የኢ.ፌ.ዲ.ሪ. ፍትሕ ሚኒስቴር Contact information, map and directions, contact form, opening hours, services, ratings, photos, videos and announcements from FDRE Ministry of Justice/ የኢ.ፌ.ዲ.ሪ. ፍትሕ ሚኒስቴር, Government Organization, Bambis, Jomo Kenyatta Avenue, Addis Ababa.
(1)

Our mission is to ensure that quality laws are enacted and implemented in order to build an effective and efficient criminal, civil, and administrative justice system that protects the interests of the Ethiopian government and people.

በአገራት መካከል የሚፈፀሙ ዓለም ዓቀፍ ስምምነቶች******************              መግቢያአገራት ከሌሎች አገሮች ጋር የሚኖራቸውን የተለያዩ ግንኙነቶች ለማስተዳደር የሁለትዮሽ...
20/08/2026

በአገራት መካከል የሚፈፀሙ ዓለም ዓቀፍ ስምምነቶች
******************
መግቢያ
አገራት ከሌሎች አገሮች ጋር የሚኖራቸውን የተለያዩ ግንኙነቶች ለማስተዳደር የሁለትዮሽ ስምምነቶች (Bilateral Agreements) ወይም በብዙ አገራት መካከል የሚደረጉ ስምምነቶች (Multilateral Agreements) ሊያደርጉ ይችላሉ። እነዚህ ስምምነቶች በሰላም፣ በንግድ፣ በሰብዓዊ መብቶች፣ በአካባቢ ጥበቃ እንዲሁም ሌሎች ዘርፈ-ብዙ ጉዳዮች ላይ ሊያተኩሩ ይችላሉ። በተጨማሪም አገራት በፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ መስኮች የሚያደርጓቸውን ግንኙነቶች በዓለም ዓቀፍ ሕግ በመምራት የጋራ ጥቅምና ፍላጎቶቻቸውን ይጠብቃሉ። ለዓለም ዓቀፍ ስምምነቶች መሠረት የሆነው እ.ኤ.አ በ1969 ዓ.ም በቪየና በተካሄደው የተባበሩት መንግሥታት ኮንፈረንስ የወጣው የቪየና የስምምነቶች ሕግ (Vienna Convention on the Law of Treaties) ሲሆን ይህ ሕግ የዓለም ዓቀፍ ስምምነቶችን ትርጓሜ፣ የሚቋቋሙበትን ሁኔታ፣ ሥነ-ሥርዓት እንዲም የተፈፃሚነት ውጤት በሚመለከት በርካታ ድንጋጌዎችን አካቷል። በዚህ ጽሑፍ የዓለም ዓቀፍ ስምምነቶች ምንነት፣ የዓለም ዓቀፍ ስምምነት ዓይነቶች፣ የስምምነቶች አተረጓጎም (Interpretation of Treaties) ፣ የስምምነቶች ዋጋ ማጣት (መሰረዝ)፣ መቅረት፣ መቋረጥ እና አለም አቀፍ ስምምነትን የብሔራዊ ሕግ አካል የማድረግ ሥርዓትን የሚመለከቱ ጉዳዮች በአጭሩ ይዳሰሳሉ።

የአለም አቀፍ ስምምነቶች ምንነት
በቪየናው የዓለም ዓቀፍ ስምምነቶች ሕግ (1969) አንቀጽ 2(1)(ሀ) በተሰጠው ትርጉም መሠረት “treaty” means an international agreement concluded between States in written form and governed by international law, whether embodied in a single instrument or in two or more related instruments and whatever its particular designation”. ይህ ወደ አማርኛ ሲመለስ “አለም አቀፍ ስምምነት” ማለት በአንድ ነጠላ ሰነድ ወይም ተያያዥነት ባላቸው ሁለት ወይም ከዚያ በላይ ሰነዶች የሚካተት፣ በመንግሥታት መካከል በጽሑፍ የሚደረገና በዓለም አቀፍ ሕግ የሚገዛ ስምምነት ሲሆን፣ የተሰጠው ልዩ ስያሜ ምንም ይሁን ምን እንደዚሁ ይቆጠራል።” የሚል ትርጉም ይሰጠናል።

ከዚህ ድንጋጌ በተጨማሪ እንደምንረዳው በተግባርም እንደሚታየው አለም አቀፍ ስምምነቶች በተለያዩ ስያሜዎች ማለትም የውል ስምምነት (Treaty)፣ ኮንቬንሽን (Convention)፣ ፓክት (Pact)፣ ፕሮቶኮል (Protocol) ወይም ቻርተር (Charter) ተብሎ ሊጠሩ ይችላሉ።
በአገራችን በአለም አቀፍ ስምምነቶች መዋዋያ እና ማጽደቂያ ሥነ-ሥርዓት አዋጅ ቁጥር 1024/2009 አንቀጽ 2(7) መሠረት አለም አቀፍ ስምምነት ማለት በአለም አቀፍ ሕግ የሚገዛ በኢትዮጵያ እና በሌላ አገር መካከል የተፈፀመ የሁለትዮሽ ስምምት፣ በኢትዮጵያና በሁለት ወይም ከዚያ በላይ በሆኑ አገራት መካከል የተፈፀመ የባለብዙ ወገን ስምምነት ወይም በኢትዮጵያና እና በአለም አቀፍ ድርጅት ወይም ድርጅቶች መካከል የተፈፀመ የሁለትዮሽ ወይም የባለብዙ ወገን ስምምነት ነው፡፡ ይህ ትርጉም ከቪየናው ስምምነት ትርጉም ጋር ተቀራራቢነት ያለው ሲሆን አለም አቀፍ ድርጅቶች ጋር የሚደረገውንም ስምምነት አካቶ ይገኛል፡፡

የአለም አቀፍ ስምምነት ዓይነቶች
አለም አቀፍ ስምምነቶች በተለያዩ መስፈርቶች የተለያዩ ክፍፍሎች ቢኖራቸውም እንደ ተሳታፊዎቻቸው ብዛት በሁለት ዋና ዋና ክፍሎች ይከፈላሉ፡-
• የሁለትዮሽ ስምምነቶች (Bilateral Treaties):- በሁለት አገራት መካከል ብቻ የሚደረጉ ስምምነቶች ናቸው። ለምሳሌ በሁለት አገራት መካከል የተደረገ የድንበር ወይም የሁለትዮሽ የንግድ ስምምነት።
• ባለብዙ ወገን ስምምነቶች (Multilateral Treaties):- ከሁለት በላይ በሆኑ በርካታ አገራት መካከል የሚደረጉ ስምምነቶች ናቸው። ለምሳሌ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ቻርተር ወይም የፓሪስ የአየር ንብረት ስምምነት።

የስምምነቶች አተረጓጎም (Interpretation of Treaties)
አለም አቀፍ ስምምነቶች የሚፈፀሙባቸው ወይም የሚተረጎምባቸው መንገዶች በቪየናው የስምምነቶች ሕግ ከአንቀጽ 31 እስከ 33 የተደነገጉ ሲሆን የአለም አቀፍ ስምምነቶችን የሚመለከቱ ክርክሮች ወይም ልዩነቶች የሚዳኙት ከነዚህ ድንጋጌዎች አንፃር ይሆናል። በዚህም በተጠቀሰው ስምምነት አንቀጽ 31 መሠረት ማንኛውም ስምምነት በቅን ልቦና (Good Faith) መተርጎም እንዳለበት በግልፅ ተመላክቷል፡፡ በመሆኑም በስምምነቱ ቃላት ለሚሰጣቸው መደበኛ (ተራ) ትርጉም፣ በአውዱ (Context) ውስጥ እንዲሁም የስምምነቱን ዓላማና ግብ (Object and Purpose) ከግምት ውስጥ በማስገባት መፈጸም ይኖርበታል። ይህም አጠቃላይ የትርጓሜን ደንብ (General rule of interpretation) መሠረት ያደረገ ነው።

ሌላው በአንቀጽ 32 መሠረት በተጨማሪ የትርጓሜ ዘዴዎች (Supplementary means of interpretation) የሚደረግ ትርጉም ሲሆን የስምምነት ድንጋጌ ትርጉም በቅን-ልቦና አተረጓጎም መሠረት ከተተረጎመ በኋላም ግልጽ ካልሆነ ወይም አሻሚ ከሆነ ትክክለኛውን ትርጉም ለማግኘት የምንጠቀምባቸው ዘዴዎች ናቸው። ይህም የስምምነቱን ዝግጅት ሥራ (preparatory work of the treaty) እና ስምምነቱ የተደረገበትን ሁኔታ (Circumstances of its conclusion) ያካትታል። በመጨረሻም በሁለቱ የአተረጓጎም ዘዴዎች መሠረት ከተተረጎመ በኋላም ግልጽ ካልሆነ ወይም አሻሚ ከሆነ በሁለት ወይም ከዚያ በላይ ቋንቋዎች በይፋ የተረጋገጡ ስምምነቶች ትርጓሜ በመጠቀም ትክክለኛውን ትርጉም ለማግኘት ጥቅም ላይ የሚውል ዘዴ ተደንግጎ እናገኛለን። ይህም በአንቀጽ 33 የተደነገገ መርህ ሲሆን አንድ ስምምነት በሁለት ወይም ከዚያ በላይ ቋንቋዎች በእኩል ሕጋዊ ኃይል የተረጋገጠ (authenticated) ከሆነ ሁሉም የቋንቋ ጽሑፎች በእኩል ዋጋ ይታያሉ። በቋንቋዎች መካከል የትርጉም ልዩነት ከተፈጠረ የስምምነቱን ዓላማና ግብ በተሻለ ሁኔታ የሚያሳካው ትርጉም ይመረጣል።

የስምምነቶች ዋጋ ማጣት (invalidity of treaties)
የስምምነት ዋጋ ማጣት (invalidity of treaties) ስምምነቱ በአለም አቀፍ ሕግ የተቀመጡ መስፈርቶችን ባለማሟላቱ ወይም በሕጋዊ ጉድለቶች ምክንያት ሕጋዊ ኃይሉን ማጣቱን የሚያመላክት ነው። አንድን ስምምነት ዋጋ ቢስ የሚያደርጉ ምክንያቶች በቪየናው የስምምነቶች ሕግ ከአንቀጽ 46 እስከ 53 ባሉት ድንጋጌዎች የተካተቱ ሲሆን እነርሱም፡-
o ሥምምነቱ የተደረገው የአገር ውስጥ ሕግን በመጣስ ከሆነ (Violation of internal law regarding competence to conclude treaties)(አንቀጽ 46)
o ስምምነቱ የተደረገው የተወካይን ሥልጣን ገደብ በመጣስ ከሆነ (Specific restrictions on authority) (አንቀጽ 47)
o በፍሬ ነገር ወይም በሁኔታ ላይ ስህተት ሲኖር (Error)(አንቀጽ 48)
o በተደራዳሪ ወገን የተፈፀመ ማጭበርበር ሲኖር (Fraud)(አንቀጽ 49)
o ስምምነቱን የፈረመው ተወካይ ሥምምነቱን የፈረመው ከሌላ ተደራዳሪ ጋር በተፈፀመ ሙስና ከሆነ (Corruption of a representative)(አንቀጽ 50)
o ስምምነቱ የተፈረመው በአገር ተወካይ ላይ በተደረገ ማስገደድ ከሆነ (Coercion of state representative)(አንቀጽ 51)
o ስምምነቱ የተደረገው የአለም አቀፍ ሕግን በመጣስ በሌላ አገር ላይ ኃይል ለመጠቀም በተደረገ ማስፈራራት ከሆነ (Coercion of a State by the threat or use of force) (አንቀጽ 52)እና
o ስምምነቱ ከአጠቃላይ ዓለም ዓቀፍ ሕግ አስገዳጅ መርሆዎች ጋር የሚጋጭ ከሆነ (Treaties conflicting with a peremptory norm of general international law (“jus cogens”)( አንቀጽ 53) ናቸው።

የስምምነቶች መቅረትና ለጊዜው መቋረጥ (Termination and suspension of the operation of treaties)
የስምምነቶች መቅረትና መቋረጥ የሚፈፀመው አንድ አዓለም አዓቀፍ ስምምነት ስለመቅረቱና ስለመቋረጡ ስምምነቱ ራሱ በሚደነግገው መሠረት ወይም ደግሞ ሁሉም ተዋዋይ አገሮች እንዲቀር ወይም እንዲቋረጥ በሚስማሙበት ጊዜ ነው። ምንጊዜም ቢሆን አንድ ስምምነት የተቋቋመበት ዓላማ ሲያበቃ ወይም ስምምነቱ የጊዜ ገደብ ያለው ሲሆን የተወሰነው ጊዜ ካለፈ ስምምነቱ ቀሪ ይሆናል።

ከሁለት በላይ የሆኑ አገራት ስምምነት ሲያደርጉ ተዋዋዮቹ ወገኖች የተወሰኑ ድንጋጌዎችን አፈጻጸም ለጊዜው ለማቋረጥ ሊስማሙ ይችላሉ። ይህ ዓይነቱ ስምምነት ሕጋዊ የሚሆነው በጉዳዩ በተስማሙበት አገራት መካከል ነው። ስምምነትን ማቋረጥ የሚቻለው ፈቃጅየሚፈቅድ ድንጋጌ በሚኖርብት ጊዜ፣ የስምምነቱ መቋረጥ የሌሎችን አባል አገራት መብት የማይጥስ ወይም ግዴታቸውን ከመፈፀም የማያግዳቸው ሲሆንና አጠቃላይ የስምምነቱን ዓላማና ተግባር የማይፃረር ሲሆን ነው።

አለም አቀፍ ስምምነትን የብሔራዊ ሕግ አካል የማድረግ ሥርዓት
አለም አቀፍ ስምምነቶች የአንድ አገር የብሔራዊ ሕግ አካል ለመሆን የሕግ ማዕቀፍ ማግኘት እና የተለያዩ ሥርዓቶችን ማለፍ ይጠበቅባቸዋል። እንደማሳያ በየአገሮቹ የሥራ አስፈፃሚው አካል ድርድር እና ውይይት መደረግ፣ በተዋዋይ አገሮች እንደራሴዎች ተፈርመው እና የሕግ አውጪ ምክር ቤቶችን ይሁንታ አግኝተው መጽደቅ ይኖርባቸዋል።

በቪየናው የስምምነቶች ሕግ አንቀጽ 11 ስር እንደተደነገገው የአገራት በስምምነቱ ለመገዛት ፍቃደኛ መሆን ፊርማቸውን በማኖር፣ የስምምነት ሰነዱን በመለዋወጥ፣ በማጽደቅ፣ በመቀበል፣ ወይም በመቀላቀል ወይም ከተስማሙ በማንኛውም ሌላ መንገድ ሊገለጽ ይችላል።

በአገራችንም አለም አቀፍ ስምምነቶች የሚፀኑት በማጽደቅ ሥነ- ሥርዓት ሲሆን በኢ.ፌ.ዲ.ሪ ሕገ-መንግሥት አንቀጽ 55(12) ስር እንደተደነገገው የሕግ አስፈፃሚው አካል የሚዋዋላቸውን አለም አቀፍ ስምምነቶች የማፅደቅ ሥልጣን የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ነው። በዚህ ድንጋጌ መሠረት በአለም አቀፍ ስምምነቶች ዙሪያ የመደራደር፣ የመፈረምና የመዋዋል ሥልጣን የሥራ አስፈፃሚው አካል መሆኑን መገንዘብ ይቻላል። ይህ የሥራ አስፈፃሚው ኃላፊነት በሕገ-መንግሥቱ አንቀጽ 77 የሚኒስትሮች ምክር ቤት ሥልጣንን በሚደነግገው ክፍል ሥር በግልጽ የተቀመጠ አይደለም። ነገር ግን በአስፈጻሚ አካላት ሥልጣንና ተግባር መወሰኛ አዋጅ ቁጥር 1263/2014 አንቀጽ 39(1)(ሐ) ላይ በግልጽ እንደተደነገገው የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ኢትዮጵያ ከሌሎች መንግሥታትና አለም አቀፍ ድርጅቶች ጋር የምታደርጋቸውን ዓለም ዓቀፍ ስምምነቶች ጉዳዩ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመመካከር ለመደራደርና ለመፈረም ሥልጣን ተሰጥቶታል። እንዲሁም ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ አለም አቀፍ ውሎች እንዲጸድቁ ለማድረግ የሚያስፈልጉትን ፎርማሊቲዎች ሁሉ ያከናውናል።

አስፈፃሚው አካል የፈረመውን ስምምነት የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ስምምነቱን ያጸደቀው ከሆነ የጸደቀው ስምምነት በሪፐብሊኩ ፕሬዚዳንት በተፈረመ ጊዜ ወይም ለፕሬዚዳንቱ ከደረሰ ከ15 ቀናት በኋላ በነጋሪት ጋዜጣ ታትሞ እንዲወጣ ይደረጋል። በዚህ መልኩ ኢትዮጵያ ያጸደቀቻቸው አለም አቀፍ ስምምነቶችም በኢ.ፌ.ዲ.ሪ ሕገ-መንግሥት አንቀጽ 9(4) መሠረት የአገሪቱ ሕግ አካል ይሆናሉ።

ማጠቃለያ
በአጠቃላይ አገራት የተለያዩ ጉዳዮችን ለማከናወን ስምምነቶችን የሚፈራረሙ ሲሆን ስምምነቶቹ የሚፈፀሙት በዓለም ዓቀፍ ስምምነቶች ሕግ መሠረት ነው። ስምምነቶች የተለያዩ ሁኔታዎችን አሟልተው እንደሚቋቋሙ ሁሉ በሕግ የተቀመጡ ሁኔታዎችን ያላሟሉ እንደሆነ ዋጋ ቢስ ይሆናሉ። የስምምነቶች መሰረዝ እና መቋረጥም በአለም አቀፍ ስምምነቶች ሕግ መሠረት የሚከናወን ነው። እንዲሁም ዓለም ዓቀፍ ስምምነቶችን የአንድ አገር ሕግ አካል ለማድረግ በሕግ የተቀመጡ ሁኔታዎች መሟላት ያለባቸው ሲሆን በኢትዮጵያ የኢ.ፈ.ዲ.ሪ. ሕገ መንግሥት አለም አቀፍ ስምምነቶች የአገሪቱ ሕግ አካል የሚሆኑበትን ሁኔታ ደንግጎ ይገኛል።

በንቃተ ሕግና ሥልጠና ዳይሬክቶሬት የተዘጋጀ

የፍትሕ ሚኒስቴርን የማህበራዊ ሚዲያ ትስስር ገፆችን እና ድረ-ገፅን ይቀላቀሉ
Website
https://www.justice.gov.et
Facebook
https://web.facebook.com/MOJEthiopia/
(x) Twitter
https://x.com/MOJEthiopia
YouTube channel
https://youtube.com/...3701...
Telegram
https://t.me/fdreattorneyGeneral_externa

የዘረፋ ወንጀል ምንነት እና የሚያስከትለው የሕግ ተጠያቂነት *************************        መግቢያወንጀል በማሕበረሰቡ የእለት ከእለት ሰላማዊ እንቅስቃሴ ላይ እክል የሚፈ...
18/08/2026

የዘረፋ ወንጀል ምንነት እና የሚያስከትለው የሕግ ተጠያቂነት
*************************
መግቢያ
ወንጀል በማሕበረሰቡ የእለት ከእለት ሰላማዊ እንቅስቃሴ ላይ እክል የሚፈጥር እኩይ ተግባር ነው። ይኸውም ወንጀል በሰው ንብረት፣ አካል፣ ጤናና ሕይወት ላይ አሉታዊ ተጽእኖ የሚሳያድር ተግባር ከመሆኑም አልፎ የአንድን አገር ሰላም፣ ደህንነት እና ማኅበራዊ ሥርዓት የሚያናጋ ድርጊት ነው። ከእነዚህ እኩይ ድርጊቶች ውስጥ የዘረፋ ወንጀል ተጠቃሽ ነው። በማኅበረሰቡ ዘንድ የውንብድና፣ ከባድ ውንብድናና ዘረፋ ወንጀሎች ምንነት ሲያምታቱ ይስተዋላል። ስለሆነም የውንብድና፣ ከባድ ውንብድና እና ዘረፋ ወንጀሎችን አንድነት እና ልዩነት ለይቶ ማወቅ የወንጀሉን ምንነት ለመረዳት እንዲሁም ወንጀሉን ለመከላከል አስፈላጊ ነው። የኢ.ፌ.ዴ.ሪ የወንጀል ሕግ በንብረት ላይ የሚፈጸሙ ወንጀሎችን በተከታታይ አንቀጾች ሥር የደነገገ ሲሆን ከእነዚህም መካከል ውንብድና፣ ከባድ ውንብድና እንዲሁም ዘረፋ /አንቀጽ 670፣ 671፣ 672/ ተጠቃሽ ናቸው፡፡ የእነዚህ ድንጋጌዎች ተመሳሳይ ግብ የግለሰብን/ድርጅትን/ የህዝብን ንብረት ከሕገወጥ ጣልቃ ገብነት መጠበቅ ቢሆንም ወንጀሎቹ የሚፈፀሙበት ሁኔታ እና ክብደት ግን ይለያያል፡፡ በዚህ ጽሑፍም የዘረፋ ወንጀል ምንነት፣ ዘረፋ ከውንብድና እና ከባድ ውንብድና የሚለይባቸው ሁኔታዎች እና የዘረፋ ወንጀል የሚያስከለትለው ተጠያቂነት በአጭሩ ይዳሰሳሉ።

የዘረፋ ወንጀል ምንነት
ዐውደ-ጥበባዊ የሕግ መዝገበ ቃላት (2016) ደግሞ ዘረፋ በባሕር ወይም በአየር በሚመጣ እንደመኪና አደጋ፣ እንደ አውሮፕላን ድንገት የመገደድ ማረፍ ወይም እንደ መርከብ መስጠም የመሳሰሉ አጋጣሚዎችን በመጠቀም ለሕዝብ ሕይወት፣ ለአገር ኢኮኖሚ ወይም እድገት ከፍተኛ ጥቅም ያላቸው ስንቆች፣ ዕቃዎች፣ መሣሪያዎች ወይም ሌሎች ንብረቶች በባእድ አካል ወይም በሌቦች መወሰድ፣ በተለይም በሥርዓት አልበኝነት ወቅት ማለትም እንደ የተፈጥሮ አደጋ፣ ጦርነት ወይም ሕዝባዊ አመጽ ባሉ ጊዜያት ንብረትን ወይም ሸቀጥን የመስረቅ ድርጊቶችን እንደሚያመለክት እና ብዙውን ጊዜ ሱቆችን፣ ቤቶችን እና ሌሎች ሕንጻዎችን መስበርና መዝረፍን እንደሚያካትት ትርጉም ሰጥቶታል። በዚህ ትርጉም የተካተቱ ነጥቦች በወንጀል ሕጉ ከተጠቀሱት ፍሬ ነገሮች ጋር ተመሳሳይነት ያላቸው ናቸው።

ይኸውም የወንጀል ሕጉ አንቀጽ 672 ለዘረፋ ቀጥተኛ ትርጉም ባይሰጠውም ከድንጋጌው ፍሬ ነገር በመነሳት የዘረፋ ወንጀል ለህዝብ ሕይወት፣ ለአገር ኢኮኒሚ ወይም ዕድገት ከፍተኛ ጥቅም የሚሰጡ ምግቦች፣ ስንቆች፣ የሚታደሉ ዕቃዎች፣ መሳሪያዎች ወይም ሌሎች ነብረቶችን ወይም በመሬት፣ በባህር ወይም በአየር በሚመጣ እንደመኪና አደጋ እንደ አውሮፕላን ድንገተኛ የመገደድ ማረፍ ወይም እንደመርከብ መስጠም የመሳሰሉ አደጋዎችን ምክንያት በማድረግ የመውሰድ ተግባር አንደሆነ መረዳት ይቻላል፡፡

ዘረፋ ከውንብድና እና ከከባድ ውንብድና ያለው ልዩነት
ውንብድና በሰው ላይ ኃይል ወይም ከባድ ማስፈራራት በመጠቀም የግል ተንቀሳቃሽ ንብረትን መውሰድ ሲሆን ዘረፋ ደግሞ በተለይ ለሕዝብ ሕይወት ወይም ለአገር ኢኮኖሚ አስፈላጊ ንብረቶችን (ምግብ፣ አቅርቦት፣ መሣሪያ ወዘተ) በመውሰድ ወይም አደጋዎችን እንደአጋጣሚ በመጠቀም ንብረት በመውሰድ የሚፈጸም ነው። ከባድ ውንብድና የውንብድና ወንጀል ልዩ ማክበጃ ሁኔታዎች ተጨምረውበት የሚፈጸም ወንጀል ሲሆን እነዚህም ሁኔታዎች ወንጀል ለመፈጸም የተቋቋመ ቡድን አባል መሆን፣ በጦር መሳሪያ ወይም በተለይ አደገኛ በሆነ ሌላ መሳሪያ በመጠቀም በተበዳይ ላይ ከባድ ስቃይ በሚያደርስ ሁኔታ በማንገላታት ወይም ከባድ ወይም ዘላቂ የአካል ጉዳት ማድረስ ወይም የተፈጸመው የኃይል ተግባር ሞትን ማስከተል ናቸው። የውንብድና በአብዛኛው የግል ንብረት ላይ የሚያተኩርና ትኩረቱን በተጎጂው ተቃውሞ ላይ ሲሆን ይህም ማለትም ወንጀለኛው ተጎጂው እንዳይቃወመው ወይም ተቃውሞው ውጤት እንዳይኖረው ለማድረግ ሀይል የመጠቀም ተግባር ነው።

በአንጻሩ የዘረፋ ወንጀል ደግሞ የሕብረተሰቡን መሠረታዊ ፍላጎት የሚጎዳ ሲሆን የህዝብ ሁከትን ወይም አደጋን እንደአጋጣሚ በመጠቀም ወይም ለሕዝብ ሕይወት ወይም ለአገር ኢኮኖሚ አስፈላጊ በሆኑ ዕቃዎች ላይ የሚፈፀም ወንጀል ነው፡፡ (የወንጀል ሕግ አንቀጽ 670፣ 671 እና 672)

የዘረፋ ወንጀል የሚያስከትለው ቅጣት
በወንጀል ሕጉ አንቀጽ 672 ሥር የዘረፋ ወንጀል እንደነገሩ ሁኔታ ለተራ ውንብድና ወይም ለከባድ ወንብድና በተደነገጉት ቅጣቶች መሠረት እንደሚያስቀጣ ተደንግጓል። ይኸውም ከ15 ዓመት በማይበልጥ ጽኑ እስራት የሚያስቀጣ ሲሆን አፈፃፀሙ ከባድ በሆነ ጊዜ ማለትም ጥቅም ላይ የዋለው ዘዴ ለምሳሌ የጦር መሳሪያ፣ የጉዳቱ መጠን (ከባድ የአካል ጉዳት)፣ የተደራጀ የወንበዴ ቡድን አባል መሆን፣ ወዘተ… የሚያሟላ ከሆነ ደግሞ ከ5 ዓመት እስከ 25 ዓመት በሚደርስ ጽኑ እስራት የሚያስቀጣ ይሆናል፡፡ ወንጀሉ የህዝብን ፀጥታ አደጋ ላይ የሚጥል ወይም የተለየ ጨካኝነትን የሚያሳይ ወይም የተፈፀመው ተግባር ዘላቂ የአካል ጉዳትን ወይም ሞትን ያስከተለ ከሆነ በእድሜ ልክ ጽኑ እስራት ወይም ነገሩ እጅግ ከባድ በሆነ ጊዜ በሞት የሚያስቀጣ ይሆናል።

ማጠቃለያ
የዘረፋ ወንጀል ለህዝብ ሕይወት ወይም ለአገር ኢኮኖሚ አስፈላጊ የሆኑ ንብረቶችን በመውሰድ
ወይም በአለመረጋጋት ወይም በአደጋ ጊዜ ንብረቶችን በመውሰድ በንብረት አለፍ ሲልም በሰው ሕይወት ላይ ከፍተኛ ጉዳት የሚያደርስ ድርጊት ሲሆን ቅጣቱም እንደ አፈፃፀሙ ክብደት ከ5 ዓመት ጽኑ እስራት ጀምሮ እስከ ሞት በሚደርስ ቅጣት ሊያስቀጣ የሚችል ድርጊት ነው።
በንቃተ ሕግና ሥልጠና ዳይሬክቶሬት የተዘጋጀ

የፍትሕ ሚኒስቴርን የማህበራዊ ሚዲያ ትስስር ገፆችን እና ድረ-ገፅን ይቀላቀሉ
Website
https://www.justice.gov.et
Facebook
https://web.facebook.com/MOJEthiopia/
(x) Twitter
https://x.com/MOJEthiopia
YouTube channel
https://youtube.com/...3701...
Telegram
https://t.me/fdreattorneyGeneral_external

የክፍት ሥራ ቦታ ማስታወቂያ ማስተካከያ******************የፍትህ ሚኒስቴር በሀምሌ 17 ቀን 2018 ዓ.ም ባወጣው እና በነሐሴ 03 ቀን 2018 ዓ.ም በማስተካከያ በወጣው ክፍት የሥ...
18/08/2026

የክፍት ሥራ ቦታ ማስታወቂያ ማስተካከያ
******************
የፍትህ ሚኒስቴር በሀምሌ 17 ቀን 2018 ዓ.ም ባወጣው እና በነሐሴ 03 ቀን 2018 ዓ.ም በማስተካከያ በወጣው ክፍት የሥራ ማስታወቂያ ላይ ለአካል ጉዳተኛ ተወዳዳሪዎች የተቀመጠው አጠቃላይ የትምህርት ውጤት (CGPA) መስፈርት ማስተካከያ ተደርጎበታል።

በዚሁ መሠረት የሚፈለገው ውጤት፦

* ለወንድ አካል ጉዳተኛ አመልካቾች፡ 3.25 እና ከዚያ በላይ

* ለሴት አካል ጉዳተኛ አመልካቾች፡ 3.00 እና ከዚያ በላይ

ተደርጎ የተሻሻለ መሆኑን እየገለጽን፤ ተወዳዳሪዎች ይህንኑ አውቃችሁ ማመልከት የምትችሉ መሆኑን እናሳውቃለን።

የፍትሕ ሚኒስቴርን የማህበራዊ ሚዲያ ትስስር ገፆችን እና ድረ-ገፅን ይቀላቀሉ
Website
https://www.justice.gov.et
Facebook
https://web.facebook.com/MOJEthiopia/
(x) Twitter
https://x.com/MOJEthiopia
YouTube channel
https://youtube.com/...3701...
Telegram
https://t.me/fdreattorneyGeneral_external

የፍትሕ ሚኒስቴር፣ ተጠሪ ተቋማቱ እና የሰላም ሚኒስቴር በጋራ ያከናወኗቸውን የክረምት በጎ አድራጎት ተግባራት አፈፃፀም ገመገሙ****************የፍትሕ ሚኒስቴር፣ ተጠሪ ተቋማቱ እና የ...
17/08/2026

የፍትሕ ሚኒስቴር፣ ተጠሪ ተቋማቱ እና የሰላም ሚኒስቴር በጋራ ያከናወኗቸውን የክረምት በጎ አድራጎት ተግባራት አፈፃፀም ገመገሙ
****************
የፍትሕ ሚኒስቴር፣ ተጠሪ ተቋማቱ እና የሰላም ሚኒስቴር በጋራ ያከናወኗቸውን የ2018/19 የክረምት በጎ አድራጎት ተግባራት እና የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር አፈፃፀም በዛሬው ዕለት በፍትሕ ሚኒስቴር በመገኘት ገምግመዋል፡፡

ተቋማቱ "ተስፋን እንትከል" በሚል መሪ ቃል በአገር አቀፍ ደረጃ የተካሄደውን የአንድ ጀንበር የችግኝ ተከላ መርሐ ግብር በተሳካ ሁኔታ ያከናወኑ ሲሆን፣ የዚሁ መርሐ ግብር አካል በመሆንም በተለያዩ የክልል ከተሞች በጋራ በመገኘት የችግኝ ተከላ አካሂደዋል፡፡

በጥቅሉ ተቋማቱ በክረምት በጎ አድራጎት መርሐ ግብር በአረንጓዴ አሻራ፣ በደም ልገሳ፣ በመኖሪያ ቤት እና በመዋዕለ ሕፃናት ግንባታ፣ በተማሪዎች መማሪያ ቁሳቁስ ድጋፍ፣ እንዲሁም በወጣቶች ግንዛቤ ማስጨበጫ ዋና ዋና ተግባራትን ለማከናወን አቅደው ሁሉንም ተግባራት መፈፀም መቻላቸውን እና የመኖሪያ ቤት ግንባታው ተግባርም በጥሩ ሂደት ላይ እንደሚገኝ አንስተዋል፡፡

ይህ የተቀናጀ የክረምት የበጎ አድራጎት እና የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር ከአመት ወደ አመት እየተጠናከረ የመጣ ተግባር ሲሆን፣ የበጎ አድራጎት የስራ ባህልን በማዳበር እና የማህበረሰብ ትስስርን በመፍጠር ረገድ ያለው ሚና የጎላ እንደሆነ በግምገማው ወቅት ተገልጿል፡፡

የፍትሕ ሚኒስቴርን የማህበራዊ ሚዲያ ትስስር ገፆችን እና ድረ-ገፅን ይቀላቀሉ
Website
https://www.justice.gov.et
Facebook
https://web.facebook.com/MOJEthiopia/
(x) Twitter
https://x.com/MOJEthiopia
YouTube channel
https://youtube.com/...3701...
Telegram
https://t.me/fdreattorneyGeneral_external

የኢትዮጵያና የማላዊ የመግባቢያ ስምምነት በደቡብ የፍልሰት መስመር ጠንካራ የወንጀል ተጠያቂነትን ይዘረጋል!**********************በኢትዮጵያና በማላዊ መካከል መደበኛ ያልሆነ ፍልሰ...
15/08/2026

የኢትዮጵያና የማላዊ የመግባቢያ ስምምነት በደቡብ የፍልሰት መስመር ጠንካራ የወንጀል ተጠያቂነትን ይዘረጋል!
**********************
በኢትዮጵያና በማላዊ መካከል መደበኛ ያልሆነ ፍልሰትን ለመከላከልና ለመቆጣጠር የተፈረመው የመግባቢያ ስምምነት በደቡብ የፍልሰት መስመር ጠንካራ የወንጀል ተጠያቂነት ስርዓትን ለመዘርጋት እንደሚያስችል የፍትህ ሚኒስቴር ገለጸ፡፡

​በጋዜጣዊ መግለጫው እንደተመለከተው ሚኒስቴሩ በሰው የመነገድና ሰውን በሕገ-ወጥ መንገድ ድንበር የማሻገር ወንጀሎችን ለመከላከል በወጣው አዋጅ ቁጥር 1178/12 በተሰጠው ኃላፊነት መሠረት፣ በትብብር ጥምረቱ ማዕቀፍ የመግባቢያ ስምምነቱ እንዲዘጋጅና እንዲፈረም አድርጓል፡፡

​ስምምነቱ አምስት የጋራ የትብብር ዓምዶች ያሉት ሲሆን፤ በሁለቱ አገራት መካከል የሕገ-ወጥ የሰዎች ዝውውር የወንጀል መረብን በጋራ ለመበጣጠስ የሚያስችሉ ማዕቀፎች እንዲዘረጉ መሰረት ይጥላል፡፡ በተለይም የጋራ የወንጀል ምርመራ ቡድን ለማቋቋም፣ በሕግ ጉዳዮች ትብብር ለማድረግ፣ ተጠርጣሪዎችንና ፍርደኞችን አሳልፎ ለመስጠት የሚያስችሉ የሁለትዮሽ ማዕቀፎች እንዲጠናከሩ ያደርጋል፡፡ ይህም በሰዎች ንግድ ላይ የተሰማሩ ዓለም አቀፍ ወንጀለኞችን ለፍርድ ለማቅረብ የተጀመሩ ሥራዎችን ወደ ላቀ ደረጃ ያሸጋግራል፡፡

​ስምምነቱ በአፍሪካ በተለይም መደበኛ ባልሆነው የደቡብ የፍልሰት መስመር በዓይነቱ የመጀመሪያ የሆነ ድንበር ተሻጋሪ የትብብር ማዕቀፍ ሲሆን፤ ለተግባራዊነቱ የሁለቱ አገራት የጋራ ኮሚቴ ተቋቁሞ የትግበራ ዕቅድ የሚያዘጋጁ ይሆናል፡፡

​የወንጀል መረቦችን መበጣጠስ ላይ የሚያተኩረው ይህ የሕግ ማስከበር ተግባር በሁለተኛው ብሔራዊ የፍልሰት አስተዳደር ስትራቴጂክ ዕቅድ (2019-2023) ልዩ ትኩረት የተሰጠው ሲሆን፤ የፍትህ ሚኒስቴርም ከመተላለፊያና መዳረሻ አገራት ጋር ተመሳሳይ የትብብር ማዕቀፍ ስምምነቶችን አጠናክሮ የሚቀጥል ይሆናል፡፡

የፍትሕ ሚኒስቴርን የማህበራዊ ሚዲያ ትስስር ገፆችን እና ድረ-ገፅን ይቀላቀሉ
Website
https://www.justice.gov.et
Facebook
https://web.facebook.com/MOJEthiopia/
(x) Twitter
https://x.com/MOJEthiopia
YouTube channel
https://youtube.com/...3701...
Telegram
https://t.me/fdreattorneyGeneral_external

በቤተሰብ ፍትሕ እና መሬት ጉዳዮች መምሪያ ዙሪያ ለክልል የፍትሕ አካላት የአሰልጣኞች ሥልጠና በመሰጠት ላይ ነው*****************የፍትሕ ሚኒስቴር የሪፎርምና ተቋም ግንባታ ዘርፍ ከዴ...
14/08/2026

በቤተሰብ ፍትሕ እና መሬት ጉዳዮች መምሪያ ዙሪያ ለክልል የፍትሕ አካላት የአሰልጣኞች ሥልጠና በመሰጠት ላይ ነው
*****************
የፍትሕ ሚኒስቴር የሪፎርምና ተቋም ግንባታ ዘርፍ ከዴስቲኒ ኢትዮጵያ ጋር በመተባበር በቤተሰብ እና በመሬት ጉዳዮች አለመግባባት መፍቻ መመሪያዎች ዙሪያ የሁለት ቀን የአሰልጣኞች ሥልጠና ለክልል ፍትሕ አካላት መስጠት ጀምሯል።

ሥልጠናው ተደራሽ፣ ተአማኒ እና ህዝብን የሚያረካ የፍትሕ አገልግሎት ለመስጠት የሚደረገውን ጥረት የሚያግዝ ሲሆን፤ በዋናነት የማህበረሰብ አቀፍ የፍትሕ ማዕከላትን ማስፋፋት፣ እንዲሁም ባህላዊ ፍርድ ቤቶችንና የሽምግልና ሥርዓቶችን በግብዓት በመደገፍ ማጠናከር ላይ ያተኮረ ነው።

የቤተሰብ ጉዳዮች ከአጠቃላይ የፍርድ ቤት ክርክሮች 11% የሚሆነውን ድርሻ የሚይዙና ለግጭት መንስኤ ሊሆኑ የሚችሉ በመሆናቸው፣ በእነዚህና በመሬት ጉዳዮች ላይ የሚነሱ አለመግባባቶችን በቀልጣፋ አማራጭ የሙግት መፍቻ ዘዴዎች ለመፍታት እየተሰራ ይገኛል።
እነዚህ መመሪያዎች ለማህበረሰብ አቀፍ የፍትሕ ማዕከላት በግብአትነት የሚያገለግሉ ሲሆን፤ ዘላቂ ሰላምን ለማስፈን፣ የልጆችን ደህንነት ለመጠበቅ፣ የሴቶችን መብት ለማስከበር እና በሀገር ግንባታ ላይ የጎላ ሚና ይኖራቸዋል። በእነዚህ ነጥቦች ላይም በየቀኑ ተከታታይ ውይይቶች ይካሄዳሉ።

የፍትሕ ሚኒስቴርን የማህበራዊ ሚዲያ ትስስር ገፆችን እና ድረ-ገፅን ይቀላቀሉ
Website
https://www.justice.gov.et
Facebook
https://web.facebook.com/MOJEthiopia/
(x) Twitter
https://x.com/MOJEthiopia
YouTube channel
https://youtube.com/...3701...
Telegram
https://t.me/fdreattorneyGeneral_external

ኢትዮጵያና ማላዊ በፍልሰት አስተዳደርና ህገ-ወጥ የሰዎች ዝውውርን በመከላከል ዙሪያ በጋራ ለመስራት የሚያስችላቸውን ስምምነት ተፈራረሙ*******************ኢትዮጵያና የማላዊ ሪፐብሊክ...
14/08/2026

ኢትዮጵያና ማላዊ በፍልሰት አስተዳደርና ህገ-ወጥ የሰዎች ዝውውርን በመከላከል ዙሪያ በጋራ ለመስራት የሚያስችላቸውን ስምምነት ተፈራረሙ
*******************
ኢትዮጵያና የማላዊ ሪፐብሊክ መንግሥት በፍልሰት አስተዳደር፣ በሕገ-ወጥ መንገድ ድንበር ማሻገር ወንጀሎችን በጋራ ለመከላከልና ለመቆጣጠር የሚያስችላቸውን የመግባቢያ ስምምነት በዛሬው ዕለት በፍትሕ ሚኒስቴር ተፈራርመዋል።

ስምምነቱን የኢፌዴሪ የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ሚኒስትር ዶ/ር ኤርጌጎ ተስፋዬ እና የማላዊ ሪፐብሊክ የሀገር ውስጥ ደህንነት ሚኒስትር ክቡር ፒተር ሙኪቶ (Hon. Peter Mukhito) ተፈራርመውታል።

ይህ ስምምነት እንዲጀመርና የድርድር ሂደቱ ውጤታማ እንዲሆን የተደረገው በብሔራዊ ትብብር ጥምረቱ አማካኝነት ሲሆን፣ ሁለቱ ሀገራት ለዘመናት የቆየውን ወዳጅነት ወደ ላቀ ደረጃ በማሸጋገር በፍልሰት አስተዳደርና በህገ-ወጥ መንገድ ድንበር ማሻገር ወንጀልን የመከላከል እንዲሁም ህገ-ወጥ አዘዋዋሪዎችን በህግ ተጠያቂ የማድረግ ስራዎችን በጋራ ያከናውናሉ።

ማላዊ «የደቡብ የፍልሰት መስመር» በመባል በሚታወቀውና ከኢትዮጵያ የሚወጡ ፍልሰተኞች መተላለፊያ ሀገር በመሆኗ፣ የፍልሰተኞች ሰብዓዊ መብትና ክብራቸው ተጠብቆ ወደ ሀገራቸው እንዲመለሱ ለማድረግና ህገ-ወጥ ዝውውርን ለመግታት የዚህ የሁለትዮሽ ስምምነት ሚና እጅጉን የጎላ ነው።

በሁለቱ ሀገራት መካከል የተደረገው ይህ ስምምነት ለሌሎች ሀገራትም አርአያ የሚሆን ልምድ የሚቀስምበት እንደሆነ የተገለፀ ሲሆን፣ በቀጣይም ስምምነቱን ወደ ተግባር ለመቀየር የጋራ ኮሚቴዎችን ከማቋቋም ጀምሮ መደበኛ የሆኑ የሕግ ስምምነቶችን የመፈራረም ስራዎች እንደሚከናወኑ ተጠቅሷል።

Ethiopia and Malawi Sign Bilateral Agreement on Migration Governance and Combating Human Trafficking
******************
Ethiopia and the Republic of Malawi signed a Memorandum of Understanding (MoU) today at the Ministry of Justice to strengthen joint cooperation in migration governance and in preventing and combating human trafficking and cross-border crimes.

The agreement was signed by H.E. Dr. Ergoge Tesfaye, Minister of Women and Social Affairs of the Federal Democratic Republic of Ethiopia, and Hon. Peter Mukhito, Minister of Internal Security of the Republic of Malawi.

Initiated and negotiated under the framework of the National Coalition, this agreement elevates the longstanding relations between the two nations to a higher strategic level. It provides a formal basis for joint action to manage migration, combat human trafficking, and ensure the prosecution and legal accountability of traffickers.

Given Malawi's critical positioning along the "Southern Migration Route" a primary transit country for Ethiopian migrants the bilateral agreement plays a pivotal role in curbing illegal trafficking, protecting the human rights and dignity of migrants, and facilitating their safe and dignified return.

The agreement was highlighted as an exemplary model of regional partnership for other nations. To ensure seamless implementation and translate the commitments into action, both governments agreed to establish joint technical committees and prepare additional formal legal frameworks moving forward.

የፍትሕ ሚኒስቴርን የማህበራዊ ሚዲያ ትስስር ገፆችን እና ድረ-ገፅን ይቀላቀሉ
Website
https://www.justice.gov.et
Facebook
https://web.facebook.com/MOJEthiopia/
(x) Twitter
https://x.com/MOJEthiopia
YouTube channel
https://youtube.com/...3701...
Telegram
https://t.me/fdreattorneyGeneral_external

የማላዊ የሀገር ውስጥ ደህንነት ሚኒስትር ክቡር ፒተር ሙኪሂቶ አዲስ አበባ ገቡ************************የማላዊ ሪፐብሊክ የሀገር ውስጥ ደህንነት ሚኒስትር ክቡር ፒተር ሙኪሂቶ (H...
14/08/2026

የማላዊ የሀገር ውስጥ ደህንነት ሚኒስትር ክቡር ፒተር ሙኪሂቶ አዲስ አበባ ገቡ
************************
የማላዊ ሪፐብሊክ የሀገር ውስጥ ደህንነት ሚኒስትር ክቡር ፒተር ሙኪሂቶ (Hon. Peter Mukhito) የተመራው ከፍተኛ ልዑክ ለኦፊሴላዊ የስራ ጉብኝት አዲስ አበባ ገብቷል።

ልዑካን ቡድኑ ቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ሲደርስ የፍትህ ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ክቡር አቶ በላይሁን ይርጋ አቀባበል አድርገውላቸዋል።

በጉብኝታቸው ወቅት በኢትዮጵያ እና በማላዊ መንግስታት መካከል በሰው የመነገድ እና ሰውን በሕገ-ወጥ መንገድ ድንበር የማሻገር ወንጀሎችን በጋራ ለመከላከል እና ለመቆጣጠር የሚያስችል ታሪካዊ የመግባቢያ ስምምነት (MoU) ይፈረማል ተብሎ ይጠበቃል።

Malawian Minister of Homeland Security Hon. Peter Mukhito Arrives in Addis Ababa

A high-level Malawian delegation led by the Minister of Homeland Security, Hon. Peter Mukhito, has arrived in Addis Ababa for an official working visit.

Upon arrival at Bole International Airport, the delegation was warmly welcomed by the State Minister of Justice, H.E. Belayhun Yirga.

During the visit, the governments of Ethiopia and Malawi are expected to sign a Memorandum of Understanding (MoU) aimed at strengthening bilateral cooperation to prevent and combat human trafficking and the illegal smuggling of migrants.

የፍትሕ ሚኒስቴርን የማህበራዊ ሚዲያ ትስስር ገፆችን እና ድረ-ገፅን ይቀላቀሉ
Website
https://www.justice.gov.et
Facebook
https://web.facebook.com/MOJEthiopia/
(x) Twitter
https://x.com/MOJEthiopia
YouTube channel
https://youtube.com/...3701...
Telegram
https://t.me/fdreattorneyGeneral_external

የወንጀል ቅጣት ገደብ በኢ.ፌ.ዲ.ሪ የወንጀል ሕግ********************              መግቢያበመርህ ደረጃ ቅጣት የተወሰነበት ወንጀለኛ የተላለፈበትን ቅጣት በአግባቡ  መፈፀም...
13/08/2026

የወንጀል ቅጣት ገደብ በኢ.ፌ.ዲ.ሪ የወንጀል ሕግ
********************
መግቢያ
በመርህ ደረጃ ቅጣት የተወሰነበት ወንጀለኛ የተላለፈበትን ቅጣት በአግባቡ መፈፀም ይጠበቅበታል፡፡ ሆኖም ለጥፋቱ መነሻ የሆኑትን ምክንያቶች በመመልከት የወንጀለኛውን ጠባይ ለማረም፣ ለማሻሻል እና ወደ መደበኛ ማኅበራዊ ኑሮው ለመመለስ ጠቃሚ ሊሆን የሚችል መሆኑን ፍርድ ቤት ያረጋገጠ እንደሆነ ቅጣቱን ገድቦ የፈተና ጊዜ ሊሰጥ ይችላል። ይሁን እንጂ በሕጉ መሠረት የሚሰጡት ውሳኔዎች የወንጀለኛውን የመታረም መልካም ፈቃድ የሚፈልጉ ስለሆነ መልካም ውጤትን ለማምጣት አለመቻላቸው ሲታወቅ በማናቸውም ጊዜ የሚሻሩ ናቸው። በዚህ ጽሑፍ የቅጣት ገደብን ምንነት፣ ገደብ የሚሰጥባቸውን ሁኔታዎች፣ የገደብ (የፈተና ጊዜው) መሳካት የሚያስከትለው ውጤት፣ ገደብ የሚከለከልባቸውንና የሚሻርባቸውን ሁኔታዎች እንዲሁም የገደቡ ፍሬ አለማስገኘት የሚያስከትለውን ውጤት በአጭሩ እንመለከታለን፡፡

የቅጣት ገደብ ምንነት
ገደብ በወንጀል ጥፋተኛ የተባለ ሰው የተፈረደበትን ቅጣት ከመፈፀሙ በፊት ለተወሰነ ጊዜ ቅጣቱ ታግዶለት አመሉ ቢፈተን ሁለተኛ ጥፋት ከማድረግ የሚታገድ መሆኑንና ለጠባዩ መሻሻል አንድ ጽኑ ማስጠንቀቂ ብቻ የሚበቃ መሆኑን ፍርድ ቤት ሲያምንበት ቅጣቱን በመወሰን እና የፈተና ጊዜ በመስጠት አፈፃፀሙ ታግዶ እንዲቆይ የሚያደርግበት ስርዓት ስለመሆኑ ከወንጀል ሕጉ አንቀጽ 192 መረዳት ይቻላል፡፡ ለመልካም ጠባይ የሚሰጠው የፈተና ጊዜ የሚወሰነው የወንጀሉን ከባድነት፣ የወንጀል ድርጊት መደጋገም ሊያደርስ የሚችለውን ጉዳት እና በጥፋተኛው ላይ ሊጣልበት የሚቻለውን እምነት ከግምት ውስጥ በማስገባት ሲሆን የፈተናው ጊዜ የመጨረሻ ፍርድ ከተሰጠበት ቀን ጀምሮ የሚቆጠር ሆኖ ከ2 ዓመት ሊያንስ ከ5 ዓመት ሊበልጥ እንደማይችል በወንጀል ሕጉ አንቀጽ 196 ተደንግጓል፡፡ ሆኖም ከቅጣቱ ጋር የጥንቃቄ እርምጃዎች ተወስነው ከሆነ እንዚህ የጥንቃቄ እርምጃዎች አይታገዱም፡፡

ፈተና የሚሰጥባቸው ሁኔታዎች
በወንጀል ሕጉ አንቀጽ 197 መሠረት ፍርድ ቤት በወንጀል አድራጊው ላይ የተወሰነበት ቅጣት እንዳይፈፀምበት የሚያግድለት ጥፋተኛው በመልካም ጠባይ እንደሚመራ፣ እንዲፈጽም የተሰጠውን ግዴታ እንደሚቀበል፣ በሚቻለው መንገድ ሁሉ በጥፋቱ ያደረሰውን ጉዳት እንደሚክስ ወይም ለተበዳዩ እንደሚከፍልና ለዚሁ ጉዳይ በተወሰነ ጊዜ ውስጥ የፍርድ ቤቱን ወጪ እንደሚከፍል ማረጋገጫ ከሰጠ በኋላ ነው። ፍርድ ቤቱ ጥፋተኛው ለገባበት ግዴታ አፈፃፀም አንድ መተማመኛ ዋስትና እንዲሰጥ የሚያስገድደው ሲሆን ይህ መተማመኛ ፍርድ ቤቱ እንደነገሩ ሁኔታና እንደ ጥፋተኛው ችሎታ በሚወስነው መጠን ልክ የሚቀርብ የሰው ዋስትና ወይም የንብረትና የገንዘብ መያዣ ነው።

የገደብ (የፈተና ጊዜው) መሳካት የሚያስከትለው ውጤት
ፍርድ ቤት የሰጠው የፈተና ጊዜ መልካም ፍሬ ካስገኘ ጥፋተኛው የተወሰነበትን ቅጣት መፈፀም አይጠበቅበትም፡፡ ሆኖም የፍርድ ውሳኔው በወንጀለኞች መዝገብ ላይ ተመዝግቦ ከሌላው ውጤት ጋር ነዋሪ እንደሚሆን በወንጀል ሕጉ አንቀጽ 192 ተመልክቷል።

የቅጣት ገደብ የማይሰጥበት ሁኔታ
በወንጀል ሕጉ አንቀጽ 194 መሠረት
1. ስለደጋጋሚነት የተፃፉት ድንጋጌዎች እንደተጠበቁ ሆኖ ጥፋተኛው ከዚህ በፊት የጽኑ እስራት ቅጣት ወይም ከ3 ዓመት የሚበልጥ የቀላል እስራት ቅጣት ተፈርዶበት እንደሆነና እንደገናም በተከሰሰበት ወንጀል ከእነዚህ ቅጣቶች አንዱ የሚወሰንበት ከሆነ ወይም
2. ከዚህ ቀደም ያልተቀጣ ሆኖ አሁን በተከሰሰበት ወንጀል ከ5 ዓመት የበለጠ የጽኑ እስራት ቅጣት የሚፈረድበት ከሆነ የቅጣት አፈፃፀም ሊገደብ አይችልም፡፡

የቅጣት ገደብ የሚሻርበት ሁኔታ
የቅጣቱ አፈፃፀም ከመታገዱ በፊት ጥፋተኛው ሌላ ወንጀል ፈጽሞ እንደነበረ የተደረሰበት ሲሆንና በዚሁ ወንጀል ምክንያት የሚፈረድበት የቅጣት ዓይነትና መጠን ከላይ በተራ ቁጥር 1 የተመለከተውን ሁኔታ የሚያሟላ ሲሆን ወይም ወንጀለኛው ቅጣቱ ታግዶለት ለፈተና በተለቀቀበት ጊዜ ውስጥ አስቦ አንድን ወንጀል ያደረገ እንደሆነ ወይም የቅጣት አፈፃፀሙ በታገደለት ጉዳይ የተሰጠው የፈተና ጊዜ መልካም ፍሬ የሚያስገኝ አለመሆኑን ፍርድ ቤቱ ከተረዳ የቅጣት ማገድ ውሳኔውን ሊሽር ይችላል፡፡

የገደቡ (የፈተናው) ፍሬ አለማስገኘት የሚያስከትለው ውጤት
ቅጣት የታገደለት ጥፋተኛ በፈተና ጊዜው የተጣሉበትን ግዴታዎች ከጣሰ ፍርድ ቤት በወንጀል ሕጉ አንቀጽ 200(2) መሠረት እግዱን በመሻር ተወስኖ የነበረው ቅጣት እንዲፈፀምበት ያደርጋል፡፡ ጥፋተኛው ለፈተና በተሰጠው ጊዜ ውስጥ አስቦ አዲስ ወንጀል ሰርቶ የተፈረደበት ከሆነ ደግሞ ዳግመኛ የቅጣት ማገድ ትዕዛዝ ሊሰጠው አይችልም፡፡

የቅጣቱ ማገድ የሚሻረው አዲስ ታስቦ ወንጀል በመደረጉ ምክንያት በሆነ ጊዜ ስለደጋጋሚነት የተመለከቱት ድንጋጌዎች እንደተጠበቁ ሆኖ አስቀድሞ ለተፈረደበት ወንጀል ከተወሰነው ቅጣት ጋር የአዲሱ ወንጀል ቅጣት ተደምሮ ተፈፃሚ ይሆናል።

ማጠቃለያ
ወንጀል የፈፀመ ሰው ጥፋተኝነቱ በፍርድ ቤት ሲረጋገጥ የወንጀል ቅጣት የሚወሰንበት ሲሆን ስለጠባዩ መሻሻል አንድ ጽኑ ማስጠንቀቂያ ቢሰጠው ሊታረም እንደሚችል ፍርድ ቤት ባመነ ጊዜ በሕግ በተፈቀደው መሠረት ቅጣቱን ሊገድብ ይችላል፡፡ ይህም ወንጀል ፈፃሚው ከቤተሰብና የማኅበራዊሕይወት ሳይስተጓጎል የመታረም እድል የሚሰጥ ነው፡፡

በንቃተ ሕግና ሥልጠና ዳይሬክቶሬት የተዘጋጀ

የፍትሕ ሚኒስቴርን የማህበራዊ ሚዲያ ትስስር ገፆችን እና ድረ-ገፅን ይቀላቀሉ
Website
https://www.justice.gov.et
Facebook
https://web.facebook.com/MOJEthiopia/
(x) Twitter
https://x.com/MOJEthiopia
YouTube channel
https://youtube.com/...3701...
Telegram
https://t.me/fdreattorneyGeneral_external

የኢትዮጵያ የቤተሰብ ፍትሕ መምሪያ ይፋ ሆነ*******************የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ፍትሕ ሚኒስቴር ከአጋር አካላት ጋር በመተባበር ያዘጋጀው የኢትዮጵያ የቤተሰብ ፍትሕ መምሪያ (Ethio...
13/08/2026

የኢትዮጵያ የቤተሰብ ፍትሕ መምሪያ ይፋ ሆነ
*******************

የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ፍትሕ ሚኒስቴር ከአጋር አካላት ጋር በመተባበር ያዘጋጀው የኢትዮጵያ የቤተሰብ ፍትሕ መምሪያ (Ethiopian Family Justice Guideline) የማብሰሪያ መርሃ ግብር በፍትሕ ሚኒስቴር ከፍተኛና መካከለኛ አመራሮች፣የዳኝነት አካላት አመራሮች እና የተለያዩ ባለድርሻ አካላትና ተጋባዥ እንግዶች በተገኙበት ተካሄደ።

መምሪያው የቤተሰብ ጉዳዮችን በቀላል፣ ተደራሽ፣ ወጪ ቆጣቢና ማኀበረሰብ ተኮር በሆነ መንገድ ለመፍታት የሚያግዝ እና በተለይም በማኅበረሰብ አቀፍ የፍትሕ ማዕከላት የሚሰጠውን የፍትሕ አገልግሎት ይበልጥ ወጥና ተጠቃሚ ለማድረግ የተዘጋጀ አስገዳጅ ያልሆነ የአሠራር መምሪያ ነው።

በመርሃ ግብሩ መክፈቻ ወቅት እንደተገለጸው፣ የመምሪያው ዋና ዓላማ የፍትሕ ተደራሽነትን በማሻሻል የሕብረተሰቡን የፍትሕ ጥያቄ በተገቢው መንገድ መመለስ እና ለዜጎች ቅርብ፣ ምቹና ተደራሽ የሆነ የፍትሕ ሥርዓት ለመገንባት የሚደረገውን ሥራ ማጠናከር ነው።

የቤተሰብ ፍትሕ መምሪያው በቤተሰብ መካከል ከሚፈጠሩ አለመግባባቶች ጋር ተያይዘው የሚነሱ የቀለብ፣ የልጆች አስተዳደግና የጥበቃ ጉዳዮች፣ የንብረት አስተዳደር፣ የፍቺ እና የንብረት ክፍፍል ጉዳዮችን በተቻለ መጠን ቀላል፣ ፈጣንና ተገቢ በሆነ አሠራር ለመፍታት የሚያግዙ አማራጮችን ያመላክታል።

መምሪያው በአዲስ አበባ፣ በአማራ እና በሲዳማ ክልሎች የተገኙ የተግባር ልምድና ተሞክሮዎችን መነሻ በማድረግ የተዘጋጀ ሲሆን፣ ከአካባቢያዊ እውነታዎች ጋር የሚጣጣሙ እና በተግባር ሊውሉ የሚችሉ የጉዳይ መፍቻ አማራጮችን ያካተተ ነው።
የቤተሰብ ፍትሕ ጉዳዮች ከሰዎች ሕይወት፣ ስሜትና ክብር ጋር በቀጥታ የተያያዙ በመሆናቸው መምሪያው የሰው ልጅን ክብር፣ ስሜትና ባህል በማክበር ሰው ተኮር የፍትሕ አገልግሎት እንዲሰጥ ልዩ ትኩረት ይሰጣል።

በተለይም የሕፃናትና የሴቶች መብትና ደህንነት፣ እንዲሁም የአካል ጉዳተኞችና በማኅበረሰቡ የተገለሉ ቡድኖች ፍትሕ የማግኘት እድል በልዩ ጥንቃቄ እንዲጠበቅ የሚያስችሉ መርሆዎችንና አሠራሮችን አካቷል።

ፍትሕ ሚኒስቴር የቤተሰብ ፍትሕ መምሪያውን ከ The Hague Institute for Innovation of Law (HiiL) እና Destiny Ethiopia ጋር በመተባበር አዘጋጅቷል። በሂደቱም አካባቢያዊ እውነታዎችንና የኢትዮጵያ የቤተሰብ ሕግ ሥርዓትን ከአለም አቀፍ ልምድና በተግባር ከተፈተኑ የቤተሰብ ፍትሕ አሠራሮች ጋር በማጣመር ተዘጋጅቷል።

በዚህም መሠረት መምሪያው በተለይ ለሕፃናት፣ ለሴቶች፣ ለአካል ጉዳተኞችና ለሌሎች ተጋላጭ የማኅበረሰብ ክፍሎች የፍትሕ ተደራሽነትን ለማስፋት ጠቃሚ መሣሪያ ሆኖ ያገለግላል።

የኢትዮጵያ የቤተሰብ ፍትሕ መምሪያ በአገሪቱ እየተቋቋሙ ባሉና በቀጣይነት በሚደራጁ የማኅበረሰብ አቀፍ የፍትሕ ማዕከላት የሚሰጡ የቤተሰብ ፍትሕ አገልግሎቶችን ይበልጥ ወጥ፣ ጥራት ያለው፣ ተደራሽና ተጠቃሚ ተኮር ለማድረግ አስተዋጾው የጎላ ነው ተብሏል።

ፍትሕ ሚኒስቴር የፍትሕ አገልግሎትን ለዜጎች ይበልጥ ቅርብ፣ ምቹ፣ ፈጣንና ወጪ ቆጣቢ ለማድረግ ከተለያዩ ባለድርሻና አጋር አካላት ጋር በመተባበር አዲስ አበባን ጨምሮ በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች የማኅበረሰብ አቀፍ የፍትሕ ማዕከላትን እያቋቋመ ይገኛል።

የፍትሕ ሚኒስቴርን የማህበራዊ ሚዲያ ትስስር ገፆችን እና ድረ-ገፅን ይቀላቀሉ
Website
https://www.justice.gov.et
Facebook
https://web.facebook.com/MOJEthiopia/
(x) Twitter
https://x.com/MOJEthiopia
YouTube channel
https://youtube.com/...3701...
Telegram
https://t.me/fdreattorneyGeneral_external

Address

Bambis, Jomo Kenyatta Avenue
Addis Ababa
P.O.BOX1370

Opening Hours

Monday 09:00 - 17:00
Tuesday 02:30 - 17:30
Wednesday 09:00 - 17:30
Thursday 09:00 - 17:30
Friday 02:30 - 17:00

Telephone

+251115515099

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when FDRE Ministry of Justice/ የኢ.ፌ.ዲ.ሪ. ፍትሕ ሚኒስቴር posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Contact The Organization

Send a message to FDRE Ministry of Justice/ የኢ.ፌ.ዲ.ሪ. ፍትሕ ሚኒስቴር:

Shortcuts

Share