14/04/2026
ዜና ዕረፍት
------------------------
የውሀና ኢነርጂ ሚኒስቴር የማናጀመንት አባልና የክቡር ሚኒስቴር አማካሪ የነበሩት ወ/ሮ ገበያነሽ ነጋሽ ከዚህ አለም በሞት ተለዩ ።
ወ/ሮ ገበያነሽ ነጋሽ ከአባታቸው ከአቶ ነጋሽ በየነ እና ከእናታቸው ከወይዘሮ አለሚቱ ሞገስ ግንቦት 14፣ 1972 ዓ.ም. በጂማ ዞን በጌራ ወረዳ ተወለዱ። ዕድሜያቸው ለትምህርት ሲደርስም የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርታቸውን በጌራ አንደኛና መለስተኛ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት፣ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን ደግሞ በአጋሮ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት ተከታትለዋል። ወ/ሮ ገበያነሽ በመጋቢት ወር 2000 ዓ.ም፣ ከኦሮሚያ ፐብሊክ ሰርቪስ ኮሌጅ በግብርና ቢዝነስ ማኔጅምንት ዲፕሎማ፤ በሐምሌ 12 ቀን 2006 ዓ.ም፣ ከሲቪል ሰርቪስ ዩኒቨርስቲ በህዝብ ስራ አመራር የመጀመሪያ ድግሪ እና በነሐሴ 13 ቀን 2008 ዓ.ም፣ ከሪፍት ቫሊ ዩኒቨርስቲ በሶሾሎጂ ሁለተኛ ዲግሪያቸዉን አግኝተዋል፡፡
ከመስከረም 01 ቀን 1992 ዓ.ም ጀምሮ እስከ መስከረም 28 ቀን 2003 ዓ.ም ድረስ በተለያዩ የባለሙያና የሃላፊነት የስራ መደቦች ላይ በኦሮምያ ክልላዊ መንግስት ጅማ ዞን ጌራ ወረዳ አስተዳደር ም/ቤት አገልግለዋል፡፡ ከጥቅምት 01 ቀን 2003 ዓ.ም ጀምሮ እስከ መስከረም 21 ቀን 2014 ዓ.ም. ድረስ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባል በመሆን ወረዳቸዉን በመወከል በተለያዩ የቋሚ ኮሚቴዎች አባልነት ሀገራቸዉንና ህዝባቸዉን ሲያገለግሉ የነበረ ሲሆን፣ በዉሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር በአማካሪነት ከመስከረም 22 ቀን 2014 ዓ.ም ጀምሮ ህይወታቸዉ እስካለፈበት ቀን ድረስ መ/ቤቱን በታማኝነትና በቅንነት ሲያገልግሉ ቆይተዋል፡፡ በስራ ዘመናቸውም ለተተኪ ባለሙያዎች አርአያ በመሆን እና ተቋማዊ ለውጥ በማምጣት ይታወቃሉ።
ወ/ሮ ገበያነሽ ነጋሽ ከባለቤታቸዉ ከዶ/ር ሀብቴ ጅፋር ጋር ትዳር መስርተው የአንድ ወንድና የአንድ ሴት ልጆች እናት ነበሩ። በነበራቸው ማህበራዊ ህይወትም በደግነታቸው፣ በታታሪነታቸውና ሰውን በመርዳት የሚታወቁ የአካባቢው እና የሀገር ባለውለታ ነበሩ።
ባጋጠማቸዉ ድንገተኛ ህመም ሚያዚያ 05 ቀን 2018 ዓ.ም በተወለዱ በ46 ዓመታቸው ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል። ወ/ሮ ገበያነሽ ነጋሽ በነበራቸዉ የህይወት ታሪክ ዉስጥ ስራቸዉን አክባሪና ትጉህ፣ ታታሪ ፣ ቅን አገልጋይ ፣ ከስራ ባልደረቦቻቸዉ ጋር ተግባቢ፣ ሳቂታ ምንም አይነት መከፋት የማይታይባቸው ለሰዉ አዛኝና ሩህሩህ ነበሩ፡፡
የቀብር ስነ-ስርዓታቸዉ ሚያዚያ 6 ቀን 2018 ዓ.ም በትውልድ ቦታቸው በጅማ ዞን ጌራ ወረዳ ከቀኑ 8:00 ሰዓት የሚፈፀም ይሆናል።
የታላቁ ህዳሴ ግድብ ማስተባበሪያ ፕሮጀክት ጽ/ቤት ከውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር ጋር በቅርበት የሚሰራ ተቋም ነው፤ በዚሁ አጋጣሚ ሁሉ ባለው የሥራ ግንኙነት ወ/ሮ ገበያነሽ ነጋሽ ተባባሪ፣ ቅን፣ ታታሪ እና መልካም ተግባቦት የነበራቸው አመራር ነበሩ፡፡
የታላቁ ህዳሴ ግድብ ማስተባበሪያ ፕሮጀክት ጽ/ቤት አመራርና ሠራተኞች በወ/ሮ ገበያነሽ ነጋሽ ሞት የተሰማውን ሀዘን እየገለፀ ለቤተሰቦቻቸው እና ለወዳጅ ዘመዶቻቸው መፅናናትን ይመኛል።
ምንጭ፡- (የውሀና ኢነርጂ ሚኒስቴር የፌስ ቡክ ገፅ)