05/05/2026
የአርባ ምንጭ ከተማ አስተዳደር ለ85ኛው የአርበኞች መታሰቢያ ቀን (የድል በዓል) የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላለፈ
**********
አርባምንጭ፦ ሚያዚያ 27/2018 ዓ.ም (አርባምንጭ ከተማ መንግስት ኮሙኒኬሽን )
መስፍን መንዛ (ዶ/ር) የአርባ ምንጭ ከተማ አስተዳደር 85ኛውን የአርበኞች መታሰቢያ ቀን (የድል በዓል) አስመልክተው የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል።
ከንቲባው በመልዕክታቸው "የአርበኞች ቀን" የሚያላብሰን ተምሳሌታዊ ትጋት እና ወኔ በልዩነት እና በከፍታ የሚታይ ነውና እኛም የጀግኖች አርበኞች ልጆች በህብረት ተግተን ድህነትን በመቀልበስ ልዕልናዋ የጠነከረ የብልፅግና ተምሳሌት ሀገር በማኖር የዘመኑን አርበኝነት መወጣት ይጠበቅብናል ብለዋል።
የከንቲባው ሙሉ መልዕክት እንደሚከተለው ቀርቧል፡-
***************
ዘንድሮ ለ85ኛ ዓመት የምንዘክረው #የአርበኞች ቀን በዓል ሀገራችን ኢትዮጵያን ዳግም በኃይል በመውረር ዘመናዊ የጦር መሳሪያዎችን ታጥቆ ሰፊ ወታደራዊ ዝግጅት በማድረግ የቆየውን የፋሺስት ኢጣልያ ወራሪ ኃይል በ1928 ዓ.ም ያደረገውን ወረራ በአምስት ዓመታት ፍጹም የአርበኞች ተጋድሎ የተሸነፈበትን የአርበኞች ድል የምናከብርበት የኢትዮጵያዊነታችን የኩራት በዓላችን ነው ።
የፋሺስት ኢጣልያ ወራሪ ኃይል ኢትዮጵያን በቅኝ ለመግዛት የዓድዋ ጦርነት ሽንፈቱን ለመበቀል የዓድዋ ጦርነት ከተካሄደ ከ40 ዓመት በኋላ የምዕራቡ ዓለም የደረሰበትን ስልጣኔ በመጠቀም የተፈበረኩ በዓለም አቀፍ ሕግ የተከለከለውን መርዛማ ጋዝ በመጠቀም ጭምር ነበር ኢትዮጵያውያንን ለማንበርከክ የወረረው።
ይህም ማለት ፋሺስት ኢጣሊያ ኢትዮጵያን ዳግም ለመውረር የመጣው በ1888 ዓ.ም በዓድዋ ጦርነት የደረሰበትን አሳፋሪ የወታደራዊ፣ ፖለቲካዊና ስነ-ልቦናዊ ሽንፈት በድል ለመቀየር ለ40 ዓመታት በመዘጋጀት ኢትዮጵያን ለመበቀል፣ ሕዝቦቿን በዓለም አደባባይ ለማዋረድ እና በምስራቅ አፍሪካ የቅኝ ግዛቱ አካል ለማድረግ በእብሪትና በፋሺስታዊ እሳቤ በማቀድ ነበር።
ፋሺስት ኢጣሊያ ኢትዮጵያዊያንን በግፍና በጭቆና ለመግዛት ዳግም ወረራ በማድረግ አርበኞች በሀገር ፍቅር ወኔና ጽኑ ትግል ለአምስት ዓመታት ሲያደርጉት በነበረ ተጋድሎ ባይሸነፍ ኖሮ እንደሀገር አንገት የሚያስደፋ የቅኝ ግዛት ታሪክ ይኖረን ነበር።
ፋሺስት ኢጣሊያ በአምስት ዓመት ቆይታው ኢትዮጵያዊያንን ለማንበርከክና ነፃነታቸውን ለመውሰድ የሚችለውን ሁሉ ቢያደርግም የቅኝ ግዛት ህልሙ ሊሳካ አልቻለም፡፡
እናት አባት ኢትዮጵያዊያን አርበኞች ዱር ቤቴ ብለው በዱር በገደል ነፍጥ አንግበው፤ ጎራዴ ስለው፣ በዱር በገደሉ እየተዋደቁ፣ ረሀብ፣ ቸነፈር መከራው ሳይበግራቸው ፋሺስት ኢጣሊያን መግቢያና መውጫ በማሳጣት የአምስት ዓመታት መሪር ተጋድሎ ፈጽመዋል።
እናት አባቶቻችን ዘመኑ የጠየቃቸውን ሁለንተናዊ መሥዋዕትነት ከፍለው ከቅኝ ተገዥነት ውርደት ነፃ የሆነች፤ የግዛት አንድነቷ የተጠበቀ ነፃ ሀገር በክብር ለቀጣዩ ትውልድ አስረክበው አልፈዋል፡፡
የቀደሙ ጀግኖች አርበኞቻችንን የድል አድራጊነት ታሪክ፤ ዘመኑ በሚጠይቀን የትግል አውድ ላይ መድገም አስፈላጊ በመሆኑ እኛ የዛሬው ትውልድ ኢትዮጵያዊያን የአያት አባቶቻችን ታሪክ ወራሽ ብቻም ሳንሆን ድህነትን በመቀልበስ ልዕልናዋ የጠነከረ የብልፅግና ተምሳሌት ሀገር በማኖር የዘመኑን አርበኝነት መወጣት የራሳችንን የአርበኛነት ታሪክ በደማቁ ልንፅፍ ይገባል፡፡
የአርበኞች ቀን" የሚያላብሰን ተምሳሌታዊ ትጋት እና ወኔ በልዩነት እና በከፍታ የሚታይ ነውና ለከተማው ማህበራዊ መሠረትና የኢኮኖሚ ምንጭ የሆኑ የተጀመሩ
የልማት እንቅስቃሴዎችን በማስቀጠል የለውጥ ትልሞቻችን እውን እንዲሆኑ ሁላችንም በልማቱ ተሰናስለን በመትጋትና በተሰማራንባቸው መስክ የበኩላችንን ልንወጣ ይገባል።
ዘላለማዊ ክብር ለእናት አባት አርበኞች! እንኳን አደረሳችሁ! አደረሰን! መልካም የድል በዓል ቀን!
መስፍን መንዛ(ዶ/ር)
የአርባምንጭ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ
ሚያዚያ 27፣2018 ዓ፣ም
አርባምንጭ|| ኢትዮጵያ