01/08/2026
"አረንጓዴ ከተሞች ለነገዋ ኢትዮጵያ የማይተካ የዘላቂ ልማት መሠረቶች ናቸው"
አቶ ብርሃኑ ዘውዴ
********************************
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ከተማና መሠረተ ልማት ቢሮ ሀላፊ አቶ ብርሃኑ ዘውዴ የዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ እና የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር አስመልክቶ መልዕክት አስተላልፈዋል።
አርባ ምንጭ ሐምሌ 25/2018 ዓ.ም (ከመልቢ)
የመልዕክቱ ሙሉ ቃል ከዚህ እንደሚከተለው ቀርቧል፤
ኢትዮጵያ የጀመረችው የአረንጓዴ አሻራ ተነሳሽነት የአካባቢ ጥበቃ ፕሮግራም ብቻ ሳይሆን ለትውልድ የሚተላለፍ የልማት፣ የኢኮኖሚ እና የአካባቢ ዘላቂነት መሠረት
መሆኑን ገልጸዋል።
በተለይም ከከተማ ልማት አንጻር የአረንጓዴ አሻራ እንቅስቃሴ ከተሞች ውብ፣ ንጹህ፣ ተወዳዳሪ እና ለነዋሪዎቻቸው ምቹ እንዲሆኑ ወሳኝ ሚና እንደሚኖረው የገለፁት ቢሮ ሀላፊው፣ ዛፎችን መትከል ብቻ ሳይሆን መርሃ ግብሩ የአካባቢ ጥበቃን ለማጠናከር፣ የአየር ጥራትን ለማሻሻል፣ የከተሞችን ሙቀት ለመቀነስ፣ የጎርፍ አደጋን ለመከላከልና የተፈጥሮ ሀብቶችን በመጠበቅ ለመጪው ትውልድ ጤናማ አካባቢን ለመተው ከፍተኛ አስተዋጽኦ አለው ብለዋል።
በክልሉ እየተካሄዱ ያሉ የኮሪደር ልማት፣ የወንዝ ዳርቻ ልማት፣ የመናፈሻዎች ግንባታና ማስዋብ ሥራዎች ከብሔራዊው የአረንጓዴ አሻራ እንቅስቃሴ ጋር ተቀናጅተው እየተተገበሩ እንደሚገኙ ያነሱት አቶ ብርሃኑ ይህም ከተሞችን ውብ፣ ንጹህ እና ለነዋሪዎች ምቹ ከማድረግ ባለፈ ለቱሪዝምና ለኢንቨስትመንት ሳቢ ያደርጋቸዋል ብለዋል በመልዕክታቸው።
ነገር ግን የአረንጓዴ አሻራ ስኬት በሚተከሉት ችግኞች ብዛት ብቻ አይለካም፤ በሚጸድቁትና በሚያድጉት ዛፎች ይለካል ሲሉም አክለዋል።
በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በመሳተፋችን፣ ለአካባቢያችን ብቻ ሳይሆን ለልጆቻችንና ለመጪው ትውልድ የማይረሳ አሻራ እያኖርን ነው ያሉት ቢሮ ሀላፊው አንድ ችግኝ መትከል አንድን ዛፍ ከመትከል በላይ የሕይወት ተስፋ፣ የንጹህ አየር ዋስትና እና የዘላቂ ልማት መሠረት መጣል ነው ብለዋል።
በመሆኑም ሁሉም የክልሉ ከተሞች ነዋሪዎች፣ ተቋማት፣ ወጣቶች፣ ሴቶች፣ የግሉ ዘርፍ እና የማህበረሰብ አባላት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በንቃት እንዲሳተፉ፣ የተተከሉትንም ችግኞች በአግባቡ እንዲንከባከቡ ጥሪ አቅርበዋል።
በሀገራችን የተጀመረውን የለውጥ ጉዞ ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር በመጪው ሐምሌ 27 ቀን 2018 ዓ.ም በሚከናወነው ታሪካዊ ሀገራዊ ዘመቻ በአንድ ቀን ብቻ 800 ሚሊዮን ችግኞችን ለመትከል በታቀደው ግብ ከክልላችን 69 ሚሊዮን ላይ 9.7 ሚሊየኑ በከተማና መሠረተ ልማት ቢሮ አስተባባሪነት የሚተከሉ ሲሆን ለዚህም ስኬት እውን መሆን መላው የክልላችን ከተሞች ነዋሪዎች፣ አመራሮችና ባለሙያዎች በጋራ እንዲነሱ ጥሪ አስተላልፈዋል።
ብርሃኑ ዘውዴ ዘታ
ቢሮ ኃላፊ
ሐምሌ 25/2018 ዓ.ም
አርባ ምንጭ